ጸሎተ ሶምሶን
ለቤተሰቤ ብርቅ ነበርሁ ፣ የኋላ ወርቅ ተብዬ የተጠራሁ ፣ “ሰማኸኝ ጌታዬ” ተብዬ ስእለት የተከፈለብኝ ፣ ሳልፀነስ የተናፈቅሁ ነኝ ፤ የመኳንንት ዘር አይደለሁም ፣ የፍቅር ጌትነት ባለበት ቤት ፣ በሚጸልይ ቤተሰብ ውስጥ የተወለድሁ ነኝ ። ጌታዬ ሆይ ! በመንፈስ ጀምሬ በሥጋ እንዳልጨርስ እባክህን አንድ ጊዜ አስበኝ ። “ነበርሁ” ብሎ መናገር ለኃጢአት እንጂ ለጽድቅ የሚዘገንን ነው ። ከቤተሰቤ በፊት አንተ አይተኸኛል ። ደም በማኅፀን ሳይረጋ የእኔን ከፍታ አብስረሃል ። የመረጥህልኝ ቤተሰቤን ብቻ ሳይሆን የምኖረውንም የኑሮ ዓይነት ነው ። ዛሬ ግን ካየህልኝ ኑሮ ወጥቻለሁና አንድ ጊዜ አስበኝ ። ያንተ ምርጫ እንደማያጸጽት ተረድቻለሁ ።
ቤተሰቤ ስለ እኔ እንዲጠነቀቅ የናዝራዊነትን ወግ አስተምረሃል ። ከማኅፀን ሳልወጣ ጭቃ ላይ እንዳላርፍ ተጨንቀህልኛል ። በማኅፀን ዓለም ብቸኛ ወዳጅ ሆነኸኛል ፤ ቤተሰቦቼም እንዳዘዝካቸው ስለ እኔ አልተሳሳቱም ። ወላጅ ራሱ ይረክስ ይሆናል ፣ በልጅ ጉዳይ ግን ፍጹም ነው ። ወላጆቼ ለእኔ የሆኑትን እኔ ለእነርሱ መሆን አልቻልኩም ፤ ውኃ ሽቅብ የመፍሰስን ያህል ተስኖኛል ። እኔ ለእኔ ደግ ከሆንሁት ቤተሰቤ ያሳየኝ ቸርነት ይበልጣል ። እኔ ፣ ለእኔ ክፉ ባልንጀራው ፣ ጨካኝ ባላንጣው ነኝ ። የሄድኩበት መንገድ ቢርቅም አንድ ጊዜ አስበኝ ። የእኔንም የአገሬንም ትንሣኤ አሳየኝ ።
በናዝራዊነት ጀምሬ በዘማዊነት ስጨርስ ፣ መጠጥን እንዳልተጸየፍሁ ዛሬ ግን ሳጣጥም ፣ ከርኵስ ነገር ስርቅ ኖሬ ዛሬ ግን ስረክስ ፣ ፍጻሜዬ አላማረምና የፍጻሜ አምላክ ፍጻሜዬን አሳምርልኝ።
በኑሮዬ ላከብርህ ጊዜ ቢያልቅ ፣ በሞቴ እንዳከብርህ አንድ ጊዜ አስበኝ ። ለንስሐ ሞት አብቃኝ እያልሁ ፣ የመዳን ቀን ዛሬ መሆኑን ዘንግቻለሁና አቤቱ አንቃኝ ።
ዓለም ደልላ ሸጠችኝ ፣ ዓለም አስብታ አረደችኝ ፣ ዓለም ስማ ነከሰችኝ ፣ ዓለም ዳብሳ ቀለደችብኝ ፣ ዓለም በጓዳ አባብላ በአደባባይ አዋረደችኝ ። የመውደቅ ዘመን በትንሣኤ እንዲለወጥ አንድ ጊዜ አስበኝ ። ሕፃን ልጅ ሲቆሽሽም የሚሮጠው ወደ አባቱ ነውና ተቀበለኝ ። አገሬን ብዬ ወጥቼ አንድ ራሴን ማዳን አቃተኝ ። በተአምራትህ ድልን እንዳላየሁ አሁን ግን በደረቅ ጣቢያ ተቀመጥሁ ። የደስታዬን ምሥጢር አንተን አሳልፌ ሰጠሁህ ። ለመኖር አቅም አጥቻለሁና ፣ ላልኖርኩለት እውነት በግርግር ለመሞት “ምነው በተደባለቀ” እላለሁና አንድ ጊዜ አስበኝ ። ጠላት ጠላትነቱን ላይረሳ ፣ ሰይፉን ወደ ኋላ ፣ ቆንጆን ወደ ፊት አድርጎ ማረከኝ ። ያ ሁሉ ዘፈን በመታወር ፣ ያ ሁሉ መፈራት በመሳለቂያነት አበቃ ። ገዳይ ደብቃ ከምታጎርስ ከዚህች ደላላ ዓለም አድነኝ ።
ዓለም ልብዋን አስቀምጣ በአፍዋ አጫወተችኝ ፣ ሃይማኖት ሃይማኖት ስል ዘመኔን እንዳባከንሁ ነገረችኝ ፣ በቤተ እግዚአብሔር ያለው ጦርነት ነው ፣ እዚህ ግን መዝናናት ነው አለችኝ ። ታስሮ እንደ ተፈታ ጥጃ ስዘልል ተሰበርኩኝ ። በስብራቴ ውስጥ ነኝና አንድ ጊዜ አስበኝ ። የምናገረው የሚያስቃት ፣ የምትናገረው የማያስቀኝ የዓለም እጮኛ ነኝና መሳቂያ የሆንሁትን ልጅህን አንድ ጊዜ አስበኝ ። ይህን የምልህ ከቤተ ክርስቲያን ቆሜ ፣ ከምእመናን መካከል ተገኝቼ አይደለም ። ፊት ለፊቴ ሰርቀው የደለቡ ባለጠጎች እየጠጡ ይታዩኛል ፣ የሴረኞች ሸንጎ በዙሪያዬ ይሰማኛል ። ከመቃብር ስፍራ እጠራሃለሁ ። እንደ አንበሳ ኖሬ እንደ ውሻ ተዋርጄአለሁ ። ያንን የልጅነት ፍቅሬን ፣ በእኔ ላይ የደከምከውን አስብና አንድ ጊዜ ድል ስጠኝ ።
የተንሸራተትኩበትም የወደቅሁበትም ቦታ ጠፍቶኛል ። እንደ ሞኝ የወንዙን ጥልቀት በሁለት እግሬ ለክቼ ሰጥሜአለሁ ። ራሴንም ቃል ኪዳኔንም አዋርጄአለሁ ። ያላንተ ከመኖር ባንተ መሞት ብፅዕና ነው ። እንደ ፈላስፋ ፣ እንደ ጀብደኛ ኖሬአለሁ ፤ እንደ አማኝ መሞትን እሻለሁ ። በእኔ ማፈርህ ይብቃና ዛሬ በእኔ ታፈር ። ድል ስጦታህ ስለሆነ አመሰግንሃለሁ ። እኔም ቀን ስለወጣልኝ አደንቅሃለሁ ። ለፍላጎቴ ሞቼ ላንተ እነሣለሁ ። አሜን ። “እግዚአብሔር አምላክ ሆይ፥ እባክህ፥ አስበኝ አምላክ ሆይ፥ ይህን አንድ ጊዜ ብቻ፥ እባክህ፥ አበርታኝ ።” አሜን!!!
መነሻ መጽሐፈ መሳፍ. ምዕ. 16
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ተጻፈ ነሐሴ 11 ቀን 2015 ዓ.ም