የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

እርስ በርሳችሁ/18/


በየጸጋችሁ አገልግሉ
“ልዩ ልዩን የእግዚአብሔርን ጸጋ ደጋግ መጋቢዎች እንደ መሆናችሁ፣ እያንዳንዳችሁ የጸጋን ስጦታ እንደ ተቀበላችሁ መጠን በዚያው ጸጋ እርስ በርሳችሁ አገልግሉ” /1ጴጥ. 4፡10/፡፡
መጋቢ ማለት አስተዳዳሪ፣ ባለ አደራ፣ አደላዳይ፣ የጌታውን ንብረት ጠባቂ፣ ጌታው አንድ ቀን መጥቶ ሂሳብ የሚተሳሰበው፣ ሽልማት አሊያም ወቀሳ የሚጠብቀው ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር ጸጋን የሰጠው ለባለ አደራዎች ነው፡፡ አንድ መንግሥት ወታደሮቹን ያስታጥቃል፡፡ እግዚአብሔርም ለአገልጋዮቹ ጸጋን ያስታጥቃል፡፡ አገልግሎት በጸጋ ካልሆነ በራስ መሣሪያ የማይሰምር ነው፡፡ አገልግሎት በምድራዊ እሴት ወይም ክብር የሚቀጥል አይደለም፡፡ መንግሥት ወታደሮቹን የሚያስታጥቀው ለአገርና ለወገን ክብር ነው፡፡ እግዚአብሔርም ጸጋን የሚሰጠው ለቤተ ክርስቲያን ዕድገት፣ ለመንግሥቱ መስፋፋት ነው፡፡ ጸጋ ራስን ለማስከበር አይሰጥም፡፡ አንድ ወታደር ቆርጦ በወጣ መጠን ትጥቁ እየጨመረ ይመጣል፡፡ እግዚአብሔርም ቆርጠው ለወጡት ጸጋውን ያበዛል፡፡
ዝናብ ደመናን አያረካም፣ ወተትም መልሶ ለላሟ ምግብ አይሆንም፡፡ ጸጋም ከእኛ ይልቅ የሚጠቅመው ሌሎችን ነው፡፡ የሌሎች ጸጋ ደግሞ ለእኛ ይጠቅመናል፡፡ የሌላውን ጸጋ ማክበር ጥቅሙ ለራሳችን ነው፡፡ ምክንያቱም የእኛ ጸጋ ከእኛ ይልቅ የሚጠቅመው ለሌሎች ሲሆን የሌሎችም ለእኛ ይጠቅማልና፡፡ ደጋግ መጋቢዎች በተሰጣችው ስፍራ ይገኛሉ፡፡ ደግ ማለት እውነተኛ ማለት ነው፡፡ “አቤቱ፣ አድነኝ፤ ደግ ሰው አልቆአልና፣ ከሰው ልጆችም መተማመን ጎድሎአልና…” /መዝ. 11፡1/ ሲል ደግ ማለት እውነት የሚናገር ማለት ነው፡፡ ደጋግ መጋቢ መሆንም የራስን ጸጋ ማወቅና የሌሎችን ጸጋ ማክበር ነው፡፡ የሌሎችን ጸጋ ማክበርም የራስን ጸጋ ማክበር ነው፡፡እግዚአብሔር ጸጋን ለአንድ ሰው በጅምላ አልሰጠም፡፡ እኔ ጋ በችርቻሮ ግዙ፣ ጅምላ አከፋፋይ ነኝ፣ እኔ ጋ ካልመጣችሁ አትድኑም የሚሉ አገልጋዮች ሊኖሩ አይገባም፡፡ የጸጋ ምንጩ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡
በጸጋችን ማገልገል ከመገፋፋትያድናል፡፡ እግዚአብሔር የቤቱ አስተዳዳሪ እንደ መሆኑ የሾመን በጎደለው በኩል ነው፡፡ በጎደለው በኩል ሲሾምን በደስታ መቀበል አለብን እንጂ የሌሎች ጸጋ ሊያስቀናን አይገባም፡፡ ባልተሰጠን ቦታ ትርፍ ነን፤ በተሰጠን ቦታ ዋና ነን፡፡ ባልተሰጠንመሮጥ መክሰር ብቻ ነው፡፡
ሐዋርያው ሁሉም ረድፉን ጠብቆ በጸጋው እንዲያገለግል ከመከረ በኋላ ሁለት ነገሮችን ያነሣል፡፡ እነዚህምጸጋን የሚጠብቁ ናቸው፡፡እንደ እግዚአብሔር ቃል መናገርና ትምክሕትን መስበር ናቸው፡፡ ስናገለግል እንደ ቃሉ ብቻ ሊሆን ይገባል፡፡ ትምክሕትም መልአክንሰይጣን ያደረገ ነውና ማራቅ ይገባል፡፡ ትምክሕትእኔ ትልቅ ነኝ ማለት ብቻ ሳይሆን እገሌ ትንሽ ነው ማለትም ትምክሕት ነው፡፡ የንጽጽር ኑሮ ተዘዋዋሪትዕቢት ነው፡፡ ዛሬ ያሉት አገልጋዮች እጅግ በጣም ትንሽ ናቸው፡፡እንኳን እነርሱ አይደለምየራስ ፀጉራቸው ቢከፋፈልእንኳ ላለው ክፍተት አይሞላም፡፡ከአባ ቁፋሮ ላይ እሸት ተበልቶለትአንዲሉ ከዚህ ቁጥር ላይም እርስ በርስ መጠፋፋት አይገባም፡፡ የሌሎችንጸጋ እንድናከብር እግዚአብሔር ይርዳን!
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ