መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » እንኳን ለ2016 ዓ.ም. ለጌታችንና ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል አደረሳችሁ !

የትምህርቱ ርዕስ | እንኳን ለ2016 ዓ.ም. ለጌታችንና ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል አደረሳችሁ !

ድንግል ሆይ !

ሰው አምላክ መሆን አይችልም ። ሰው አምላክ ለመሆን ፈለገ ፣ ነገር ግን ሞትን አመጣ ። አምላክ ግን ሰው መሆን ይችላል ። አምላክ ሰው ሆኖ ሰውን አምላክ አደረገው ። ሰው በዕፀ በለስ አምላክ ለመሆን ፈለገ ። በዕፅ ያልተገኘን አምላክነት በዕፅ ፈለገው ። አዳም በዕፀ በለስ አምላክነትን ሲፈልግ ፣ አምላክ አምላክነትን ያገኘው በቅጠል ነው ብሎ ማመኑ ነው ። በዚህም እግዚአብሔርን ተዳፈረ ። በቅጠል ያልተገኘ አምላክነትን በቅጠል መፈለግ ትርፉ ውርደት ነው ። ቅጠል ሐሰተኛ ትልቅነትን ያመጣል ። ዛሬም አደንዛዥ ዕፁ ያልሆኑትን እንደሆኑ እንዲሰማቸው ያደርጋል ። ድንግል ሆይ አምላክነት የባሕርይ ገንዘቡ የሆነ ፣ በኃይል የሚነጥቀው የሌለ ፣ በፈቃዱ ለሰው አምላክነትን የሰጠ እርሱ ቡሩክ ነው ። ቃል ሥጋ ሆነ ። አምላክ ሰው ሆነ ። አምላክ ሰው ነው አይባልም ። በሁነት/በመሆን ግን አምላክ ሰው ሆነ ። አምላክ ሰው በመሆኑም ሰው አምላክ ሆነ ። ድንግል ሆይ ይህን ባየሽ ጊዜ የሰው ሩጫ በልብስ እሳትን ለመጫር ፣ በዋሻ ፀሐይን ለማሰር መሞከር አይደለም ወይ 

አምላክ የእርሱ ያልሆነውን ሰውነት ገንዘብ ባደረገ ጊዜ ፣ ሰውም ከተዋሕዶ የተነሣ የእርሱ ያልሆነውን አምላክነት ገንዘብ አደረገ ። የምድር ገዥው አዳም ፣ በበደሉ እርሱንም አጣ ። በተዋሕዶ ግን በሰማይና በምድር ሥልጣን አገኘ ። የከበረው ጥቁር ወይም ነጭ የሰው ዘር ሳይሆን መለኮት የተዋሐደው ባሕርየ ሰብእ ነውና ሰው የአምላክ ዘመድ ሆነ ። ዛሬ በመቃብር ሥጋችንን ብናየው ፣ በሥላሴ ዙፋንም እያየነው ነው ። “ትንሽ ሥጋ ከመርፌ ትወጋ” እንዲሉ መለኮትም ሥጋን ለዘላለም በመቃብር አይተወዉም ። ሙሴ ከቤተ መንግሥት ተሰድዶ ልዑል መባልን አስቀምጦ በኮሬብ ተገኘ ። የልዑል አብ ልጅም ክብሩን ትቶ መጣ ። ክብሩን አላጣም ። ክብሩን ሸፍኖ በሥጋ ትሕትና ተገለጠ ። ልዑል በዚህ ምድር ተሰደደ ፣ ሙሴ በወገኑ ቅንዓት ክርስቶስም በሰው ልጆች ቅንዓት ይህን አደረገ ። ሙሴ በደብረ ኮሬን ለቀናለት ሕዝብ የነጻነት ዜና ሰማ ፣ ክርስቶስም በደብረ ቀራንዮ ለቀናለት የሰው ልጅ ድኅነት አመጣ ። እርሱ በዚህ ልክ ዝቅ ካላለ እኛ ከፍ ማለት አንችልም ። የሰው ብልሽት አያል ነውና የሠራው እጅ ካልሆነ ማንም አያበጀውም ። ሰው ዘመደ አምላክ በመሆን ዳነ ። ድንግል ሆይ ለዚህም ድልድይ እንድትሆኚ የተመረጥሽ አንቺ ነሽ !

ምስጋና በመቅደስ ፣ ምስጋና በሰማይ ይሰማ ነበር ። አሁን ግን በማኅፀንሽ የምስጋና አደባባይ ተሠራ ። ሰማይን ለማየት ቀድሞ ቀና ማለት ይገባ ነበር ፣ አሁን ግን ዝቅ ብለሽ የመላእክትን ምስጋና ሰማሽ ። ሊቀ ካህኑ በዓመት አንድ ጊዜ የሚገባባት ኅቱም መቅደስ አንቺ ነሽ ። ሊቀ ካህናት ክርስቶስ በገባበት ማኅፀንም ፍጡር ሊቀመጥ አይችልም ። የወልድ እናቱ ፣ ወላዲተ አምላክ ተብለሽ የምትጠሪ ፣ ሁሉን አጥተሸ ሁሉን ያገኘሽ ፣ በነፍስሽ ሰይፍ አልፎ እሞሙ ለሰማዕታት የተባልሽ አንቺ ነሽ ። ድንግል ሆይ ልጅሽን በወለድሽ ጊዜ የተሰማሽ ደስታ በእኛም በምንወድሽ ይደርብን ! አሜን !

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 28 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም