መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » እንዲህ ቢሆንስ » እንዲህ ቢሆንስ …? /5/

የትምህርቱ ርዕስ | እንዲህ ቢሆንስ …? /5/

“በምን መስፈርት ይሁን አላውቅም ሰዎች እኔን ለማማከር ይመርጡኛል ። እኔም ሳላስበው የሰዎችን ችግር በመፍታት ሥራ ተጠምጄ ራሴን አገኘዋለሁ።ነገር ግን በምሰማው ነገር እንዳልፈተን እሰጋለሁ” እያልህ ይሆን ? ሰዎች በሥጋዊ ፣ በሥነ ልቡናዊና በመንፈሳዊ ችግሮች ውስጥ ያልፋሉ ። ሥጋዊ ችግር ማጣት ፣ ሕመም ፣ ስደት ፣ እስራት … ነው ። ሥጋዊ ችግሮች የሥጋ ብቻ ሁነው የሚቀሩ አይደሉም ። መፍትሔ ካላገኙ የሥነ ልቡናና የመንፈሳዊ ጫናን ያስከትላሉ ። በችግር ምክንያት ጭንቀት ይፈጠራል ፣ ይህ የሥነ ልቡና ጉዳት ነው ። በችግሩ ምክንያት ወንጀል ውስጥ ሲገባ ደግሞ መንፈሳዊ ችግር ነው ። ሥነ ልቡናዊ ችግር የተለያየ ነው ። ጭንቀት ፣ ፍርሃት ፣ ከመጠን ያለፈ ድፍረት ፣ ይሉኝታ ፣ ጭካኔ ፣ ለመጀመር መፍራት ፣ ከትላንት ኑሮ ጋር መተሳሰር ፣ … ነው ። የሥነ ልቡና ችግር ሥጋዊ ችግር ያመጣል ። በጭንቀት ምክንያት አካል ይደክማል ። የምግብ ፍላጎት ይቀንሳል ፣ ወይም የምግብ ፍላጎት ይጨምራል ። የተጨነቀ ሰው ይህችን ካልጎረስኩ እሞታለሁ ብሎ ሲፈራ በጣም ይመገባል ። ከእንቅልፉ እየነቃም ሊበላ ይችላል ። አንዳንድ ሰው ጭንቀቱን ምግብ ላይ ይወጣዋል ። ፍርሃትም ከቤት እንዳይወጣ ፣ ሥራ እንዳይሠራ ምክንያት ሲሆን በዚህም የኑሮ መናጋት ይመጣል ። የሥነ ልቡና ችግር መንፈሳዊ ችግርም ያመጣል። ሰው መጨነቅ ሲጀምር እምነቱን እያጣ ይመጣል ። ሲፈራም ከእግዚአብሔር በላይ ሌላ ነገር እያከበረ ነው ማለት ነው ። ሰዎች ሁሉ ለእኔ መልካም አመለካከት የላቸውም ስለሚል የማያውቀውን ሰው ሳይቀር ለመበቀል ይነሣል።
መንፈሳዊ ችግር እግዚአብሔርን በአምልኮት ፣ ወንድምን በጥላቻ መበደል ነው ። መንፈሳዊ ችግር በመንፈሳዊ ነገር ካልሆነ በሌላ ነገር የማይደለል እውነት ፈላጊ ነው ። መንፈሳዊ ችግር ውስጥ የገባ ሰው ከእግዚአብሔር ቃል ይልቅ የነቢይና የመነኩሴ ቃል ይፈልጋል ። ሲያልፍም ወደ ጠንቋይ ይሄዳል። እግዚአብሔርን ቢያገለግል እንኳ ሙያውን እንጂ እግዚአብሔርን ስለማይወድ ፍቅር የሌለው አገልግሎት ያገለግላል ። አንድ አገልጋይ ሲናገር የሰማነው ፡- “አገልግሎቴ ይበላሻል ብዬ እንጂ እገሌን መግደል እፈልግ ነበር” ብሏል ። ይህ ሰው የፈራው ዜናውን እንጂ ሥላሴን አይደለም ። ያለ መንፈሳዊነት ማገልገል ይቻላል ። እንደውም አገልግሎት ታክስ የማይከፈልበት ንግድ የሆነላቸው ብዙዎች ናቸው ። መንፈሳዊ ችግር ለቃሉ ፣ ለጸሎት ፣ ለኅብረት ጊዜና ልብ ማጣት ነው ። መንፈሳዊ ሕይወት ካነከሰ የማያነክስ የሕይወት ክፍል የለም ። መንፈሳዊ ችግር ለሥጋ ፈቃድ መገዛት ፣ በኃላፊ ዓለም ፍቅር መነደፍ ፣ በኃጢአት ኳስ መጫወት ነው ።
ሰዎች ወደ እኛ ለማማከር የሚመጡት እነዚህን ሁሉ ችግሮች ይዘው ነው ። ለማማከር ለምን መረጡን ? ብለን መጠየቅ ጥሩ ነው ። መጠነኛ ዝምታችንን ሲያዩ ምሥጢሬን አያወጡም ብለው ነው ። መንፈሳዊ ምክር ስንሰጥ ሲያዩን የእኔ መፍትሔ እዚያ ይገኛል ብለው ነው ። ጥሩ ሰላምታ ስንሰጣቸው ጥሩ ሕይወት ያሳዩናል ብለው ነው ። በአጠቃላይ በትንሹ ስንታመን በብዙ አምነውን ነው ። የሚያማክሩን ሰዎች በዓለም ላይ ካሉት አክባሪዎቻችን የመጀመሪያዎቹ ናቸው ። ስለዚህ ልናከብራቸው ይገባል ። ምሥጢራቸውን ልንጠብቅ ፣ የተሻለ መንገድን ልናሳያቸው ፣ የሕይወት ሸክማቸውን ልንጋራላቸው ይገባል ። በአሳብ ብቻ ሳይሆን በገንዘብም ልንደግፋቸው ይገባል ። ምክንያቱም እኛ የተፈጠርነው ለዚህ ቀን ሊሆን ይችላልና ።
በማማከር ሂደት ውስጥ ከእኛ የሚጠበቀው የመጀመሪያውና ትልቁ ነገር ማዳመጥ ነው ። ሰዎች ሲናገሩ ከግማሽ በላይ እፎይታ ያገኛሉ ። ሲናገሩ መንገዱ እየታያቸው ይመጣል ። ሰው አፉን ሲዘጋ አፉ መጥፎ ጠረን ይይዛል ፣ ሲከፍት ግን አዲስ አየር ይገባል ። በመናገራቸው ውስጥ የጠፋቸውን ውል ሊያገኙት ይችላሉ ። ለተጨነቁ ሰዎች ትልቁ እርዳታ ጆሮ ማዋስ ነው ። ችግራቸውን እያጋነንን መስማትና መግለጽ በፍጹም አይገባም።ከእግዚአብሔር በላይ የሆነ ችግርና ኃጢአት የለምና ። ተራችን ደርሶ ስናናግራቸው አንዳች የፍርድ ቃል መጠቀም የለብንም ። የሚያጽናና ቃልን ከእግዚአብሔር ቃል ፣ ከኑሮ ልምዳችን ልናካፍላቸው ይገባል ። በመጨረሻ አብረን መጸለይ ሁለታችንንም ይፈውሳል ። ከዚያ በኋላ ክትትል ማድረግ ተገቢ ነው ። ችግሩን እየረሱት ከሆነ መቀስቀስ የለብንም ። ሌላ ነገር መጨዋወት ይገባል ። መናገር ከፈለጉ ግን መስማት ይገባናል ። የተቸገረ ሰው ተናግሮ አይረካምና ።
ሌላውን ሰው ስናማክር ራሳችንን ከፈተና ለመጠበቅ እንደ መርማሪ ፖሊስ መጠየቅ የለብንም ። የነገሩን ላይ ተመሥርቶ ማጽናናት ብቻ ተገቢ ነው ። የፍርድና በልብ የመታዘብ ስሜት ሊኖረን አይገባም ። እኛም ከቆምን የቆምነው በራሳችን አይደለምና ። ካማከርን በኋላ አብረን መጸለይ ሸክሙን እዚያው ለመጣል ይረዳል ። የአማካሪዎች አማካሪ ከሌለ አማካሪ እየተጎዳ ይመጣልና እኛ ደግሞ የምናማክረው የበላይ ሰው ያስፈልገናል ። ሌሎችን ለማማከር ጸጋ እንዳለን የምናውቀው ሰዎች ምርጫ እያደረጉን ወደ እኛ ሲመጡ ነው ። ያለንበት ዘመን የበዛ ችግር ሳይሆን ያነሰ አማካሪ ስላለ ችግሮች ገንነው ይታያሉ ። አማካሪ ከተገኘ ሕይወት ቀላል ነው ። ተፈጥሮአዊ በሆነ መንገድ ደግሞም ሕይወት ያለው የምክክር አገልግሎት እየጠፋ የቢሮ ሥራ ስለሆነ ፣ የክፍያ ምክርም ያን ያህል ስለማይረዳ ብዙ ሰዎች እየተቸገሩ ነው ።
አንተ ግን ብዙ ችግር ቢኖርብህም የሰዎችን ችግር ለመፍታት ስትጥር እግዚአብሔር ያንተን ፈተና እያራቀ ይመጣል ። መስጠት ብዙ መቀበል ነው።
ወደ ክርስቶስ መገስገስ 10
ጥቅምት 5 ቀን 2011 ዓ.ም.
ተጻፈ በአዲስ አበባ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም