መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » እንዲህ ቢሆንስ » እንዲህ ቢሆንስ …?

የትምህርቱ ርዕስ | እንዲህ ቢሆንስ …?

“መማር እፈልግ ነበር ፣ ነገር አእምሮዬ በብዙ ነገሮች ተይዟል ። ትምህርቱን ጀምሬ ባቆመውስ ?” እያልህ ይሆን ? አንተ ስለ አሁን እንጂ ስለሚመጣው የማታውቅና የማትጠየቅ ነህ ። አንተ የዛሬ ሳይሆን አንተ የአሁን ሰው ነህ ።በጀቱን በትክክል ያልተጠቀመ ተቋም በጀቱ ይመለስበታል ። ዕድሜህንም በትክክል ካልተጠቀምህ ተመላሽ ይሆናል ። ማቱሳላ በዚህ ዓለም ተገኘ ፣ እንጂ ይህን ሠራ አልተባለም ። 969 ዓመት ኖረ እንጂ ይህን በጎ ነገር ፈጸመ ተብሎ አልተጻፈለትም ። በዚህ ዓለም ላይ ዛፎችም ዓለቶችም ተገኝተዋል።አንተ ግን የተገኘህ ብቻ ሳይሆን የኖርህም ልትሆን ይገባሃል ። ሞቶ መኖርና ኑሮ መሞት ልዩነት አለው ። የቀረህ አንድ ቀን ቢሆንም ትምህርት ቤት አትቅር ። ትምህርት በራሱ ዋጋ ነውና ዋጋ አገኝበታለሁ ብለህ አትማር  ። ትምህርት በራሱ ምግብ ነውና እበላበታለሁ ብለህ አትማር ። ትምህርት ብዙ አሳብህን ይወስድልሃል ። አሳብህን ለመርሳት መሞከር የበለጠ ማስታወስ ነው። ሌላ ማሰብ ግን መርሳት ነው ። ትምህርት ሌላው አሳብ ነው ። ትምህርት በጠባዩ ልጅ ያደርጋልና ለመታደስ ከፈለግህ ተማር ።
ደግሞም ትምህርት የዕድሜ ገደብ የለውም ። ለትምህርት ብለህም የምትበላው ተጨማሪ ምግብ የለም ። ለመኖር የምትበላው ለትምህርት ይሆናል ። ፍርሃትህ በእግዚአብሔር ጸጋ አንተን ይፍራህ እንጂ ፍርሃትን አትፍራው ። ለልጅ ከሳቁለት ፣ ለውሻ ከሮጡለት ፣ ለውኃ መንገድ ከለቀቁለት ፣ ለባለጌ ፊት ካሳዩት ፣ ለሌባ ከሰጡት መቆሚያ የለውምና ደፍረህ ቁም።
በአገራችን ሰው ቤት ሲገዛ ስላማረው አይገዛውም ፣ ወደፊት ዋጋ ያወጣ ይሆን ወይ ? ብሎ ነው ። መኪና ሲገዛ ደስ ስላለው አይገዛውም ወደፊት ከእጄ ይወጣ ይሆን ወይ ? ብሎ ነው ። ገና አንድ ቀን ሳታድርበት ስለ መሸጥ ለምን ታስባለህ ? ገና አንድ ቀን ሳትሳፈርበት ስለ መሸኘት ለምን ትጨነቃለህ ። መቼ ነው የምትኖረው ? ሁሌ አውታታ ፣ ሁሌ መንገደኛ ነህ። ከአገር ውጭ የሚያምር የአንገት መስቀል አየሁና ወደድኩት ። አጠገቤ የነበሩትን ትልቅ አባት ፡- “ብፁዕ አባታችን ወድጄው ነበረ ፣ ቢለቅስ ብዬ ፈራሁ” አልኳቸው ። እርሳቸውም፡- “ካማረህ ግዛው ፣ እንኳን እርሱ እኛም እንለቃለን” አሉኝ ። ይህ መልስ ከዚያን ቀን ጀምሮ ለብዙ የሕይወት ገጠመኜና ለማዘገየው ደስታዬ መልስ ሁኖልኛል ። አዎ ስለሚፈርሱ ቤቶች ስናስብ እኛም እናልፋለን ፣ ስለሚለቁ ጌጦች ስናስብ እኛም መልካችንን እንጥላለን ብለን ማሰብ መልካም ነው ። ያለቀ ነገር ሁሉ የተጀመረ ነውና ያሰብከውን በጎ ነገር ጀምረው ። እግዚአብሔር ይረዳኛል በል ። አምላክህ ባታየውም ሊረዳህ በአጠገብህ ቁሟል ። ጉዳዩን በጥልቅ አስበው ፣ ጸልይበት ፣ ፈጽመው ። መለኮት ያግዝህ !
ይቀጥላል
ወደ ክርስቶስ መገስገስ 6
መስከረም 21 ቀን 2011 ዓ.ም.
ተጻፈ አዲስ አበባ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም