መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » እንዳለ ያለ

የትምህርቱ ርዕስ | እንዳለ ያለ

“አንተ ግን ያው አንተ ነህ ፥ ዓመቶችህም ከቶ አያልቁም ።”

መዝ. 101 ፡ 27 ።

ከሳ ደረቴ መነመነ ፣
የድሮ መልኬ ምንድን ሆነ ?
የድሮ መልኬ ጠፋኝ ወይ ?
ሰው ኑሮውን መሳይ ።

በ1977 ዓ.ም. በኢትዮጵያ በተነሣው ታላቅ ረሀብ አንዲት የተጎዳች ሴት መልኳን በመስተዋት አይታ ድሮና ዘንድሮ ሲምታታባት የገጠመችው ግጥም ነው ይባላል ። ለሰዎች ብቻ ሳይሆን ራስዋ ለራስዋ እንደ ጠፋት የገለጠችበት ነው ። ቆንጆ ነኝ ማለት ሐሰት ነው ። የጨበጡት የሚመስል ነገር ገና በፍለጋ ላይ ያለ ነው ። “ሰው ማንን ይመስላል ?” ቢሉ “ኑሮውን” ይባላል ። ይህች ሴት በደህና ዘመን መልኳ ደህና ነበር ፣ በረሀብ ዘመን ደግሞ ቅላቷ ጠቁሮ ፣ ውፍረቷ ከስቶ ፣ ወዟ ደርቆ ፣ ደም ግባቷ ርቆ ፣ ውበቷ ረግፎ ፣ ማማሯ አስፈሪ ሁኖ አየችው ። በጥጋብ ዘመን የሕይወት መልክ ፣ በረሀብ ዘመን የሞት መልክ ይዛለች ። በቁም ፈርሳ ፣ ሳትቀበር የሙታን አምሳያ ሁናለች ። ስለዚህም ይህን ልብ የሚነካ ግጥም ገጠመች ። ውበት ሐሰት ፣ ደም ግባትም ከንቱ መሆኑን ለመናገር ታሪክ ማጣቀስ ፣ መጽሐፍ ማንበብ ፣ ፎቶ መፈለግ አያሻም ። ረሀብተኞች ጋ መሄድ ፣ ሕመምተኞችን መጎብኘት በቂ ነው ። ዓለም የተሠሩትን ቆንጆዎች ለማፍረስ ዛሬም አልደከማትም ። በመቃብር የሚፈርሱ የአንድ ጊዜ ዕዳ አለባቸው ። በቁም እየተሠሩ መፍረስ የሚገጥማቸው ብዙ ናቸው ። እኛም ብዙ መልክ የያዝነው በዚህች ትንሽ ዕድሜአችን መሆኑ ይገርማል ። መልክ አድራሻ አይሆንም ። ቆሞ የማይጠብቅ በራሪ ነገር ነው ። እንዳማሩ ያሉ ፣ እንዳማሩ የሞቱ ጥቂቶች ናቸው ። ሰው ኑሮውን ሲመስል መልኩ ይጠፋዋል ፤ እግዚአብሔርን ሲመስል ግን መልኩን ያገኘዋል ። እግዚአብሔር ግን በማይጠፋ ውበት ፣ በማይደፈር ግርማ ፣ በማይናወጥ ዙፋን ፣ በማይጎድል ጌትነት ፣ በማይነጥፍ ምስጋና ፣ በማይለወጥ ባሕርይ ፣ መገዛት በሌለበት መለኮት ፣ በማይፋለስ አንድነት ፣ በማይጣፋ ሦስትነት ለዘላለም ይኖራል ። አንተ ግን ያው አንተ ነህ ይላል ።

ረጅም መቀነት ሳይስቡት ይጠብቃል ፣
የዘመኑ ፍቅር ሳይጀምሩት ያልቃል ።
አሁን ምን ይባላል ሐተታ መናገር ፣
እየሰሙ መቻል ሳለ ደግ ነገር ፤
ከዚያም ከዚያም አትበይ እንደ ቆዳ ገድጋጅ ፣
አምላክ ከወደደው ይበቃል አንድ ወዳጅ ።

የድሮ ዘፈን ነው ። ዓለም ዓለምን የታዘበችበት ግጥም ነው ። ሰዎች በተዋወቁ ቅጽበት በቁልጫ የሚጠራሩበት ፣ ካልተገባበዝን ብለው ሸብ ረብ የሚሉበት ፣ የኑሮአቸውን ምሥጢር ዘክዝከው የሚናገሩበት ይህ ዘመን ነው ። ቁልምጫም ፣ ግብዣውም ፣ ምሥጢር መካፈሉም መልካም ነበር ። ያ ሰው ዞር ሲል ግን ህልውናውን ለመርሳት መቸኮል ምን የሚሉት ፍቅር ነው ? ፍቅር ካለበት ሰዓት ይልቅ የሚታወቀው መለያያው ሲደርስ ነው ። ሲለያዩ መረሳሳት ይህ ፍቅር አይደለም ። ፍቅር በአካል ሲርቁ በልብ መጨዋወት፣ በመንፈስ መስመር መገናኘት ነው ። በእኛው ዘመን በፌስ ቡክ ፍቅር ይጀመራል ፣ ድምፅ ሰምቶ ሰው በፍቅር አበድኩ ይላል ። ሲገናኝ ግን አንድ ቀን ለመቆየት አቅም ያጣል ። ድምፁ የውሸት ፣ መልኩ የውሸት ፣ ፎቶው የውሸት ነው ። አንድ አባባል እውነት ከሆነ ልጥቀሰው፡- “የውሸት ፀጉር ይዘሽ የእውነት ወንድ አትፈልጊ” የሚል ነው ። በዚህ የእነ ቶሎ ቶሎ ቤት ግድግዳው ሰንበሌጥ በሆነ ዘመን ፍቅር ከጃንሆይ ጋር ተቀብሯል የሚሉ ብዙዎች ናቸው ። ፍቅርን ብቻ ሳይሆን አምላክንም ድሮ ቀርቷል የሚሉ እየበዙ ነው። “የጃንሆይ ጊዜ እግዜር አንተ ታውቃለህ” የሚሉ አሉ ። እግዚአብሔር ግን ፍቅሩን ወረት ፣ አባትነቱን ክዳት ሳይጎበኘው አለ ። ፈተና ያልገጠመው ፍቅር ፣ ሞት እንቅፋት ያልሆነው መውደድ የእግዚአብሔር ብቻ ነው ። አንተ ግን ያው አንተ ነህ ተብሎለታል ።

ጠማማውን እንጨት እየቆረጣችሁ ፣
ወልጋዳውን እንጨት እየቆረጣችሁ
ይህም ማገር ሁኖ ቤት ትሠራላችሁ

የሚል ቅኔም አስታውሳለሁ ። ሌላም ግጥም አለ፡-

ምን ያስመርጣል ጥሩ እንጨት ፣
ለመሰንበቻ ቤት ።

በዚህ ዓለም ላይ እያለፍን እንጂ እየኖርን አይደለም ፣ እያቋረጥን እንጂ መሠረት እየጣልን አይደለም ። የዛሬ ሰው የነገ አፈር ነን ። ለራሳችን የሰሰትነው ሀብት ንብረት ፣ ጤናችንን አደጋ ላይ የጣልንበት ቤት ለማንም ይሆናል ። እኔም አለሁ ማለት በማይቻልበት ዓለም አንድ የጸና አለ ። ሁሉም ነገር ሲወዛወዝ ትክል የሆነ ነገር መፈለግ ግድ ነው ። ሁሉም ነገር ሲፈናቀል አድራሻ ያለው የሰማይ መቅደስ ብቻ ነው ። የሐጊያ ሶፊያ ድንቅ ቤተ ክርስቲያን ዛሬ ኢስታንቡል ውስጥ የእስላም መስጊድ ሁኗል ። ዓለምን የምትገዛ የነበረች ሮም ዛሬ ኢኮኖሚዋ ይዋዥቃል ። በግዛቷ ፀሐይ አይጠልቅም የተባለች እንግሊዝ ዛሬ ደሴት ሁናለች ። ሶቅራጥስ ፣ ፕሌቶ ፣ አሪስቶትል ዛሬ የሉም ። ቄሣር ፣ ፈርዖን ፣ ታላቁ እስክንድር ስማቸው አይጠራም ። እኛ ግን እኛ አይደለንም ። አንተ ግን ያው አንተ ነህ ብለን እናመሰግናለን ።

ሁሉም ነገር በሚለዋወጥበት ዓለም የማይለወጠውንና የማይናወጠውን አምላክ ያዙ ።

የጸናው ክርስቶስ ያጽናችሁ ።

ዲያቆን አሸናፊ መኮንን
ሐምሌ 21 ቀን 2012 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም