መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » እንዳይደክመኝ

የትምህርቱ ርዕስ | እንዳይደክመኝ

ክፋት ሲያድግ ፣ ደግነት ሲያንስ ፣ አጋጣሚዎች ማር ሳይሆን መርዝ ሲረጭባቸው ፣ ያውቃል የተባለው ካላወቀው በላይ ሲዋዥቅ ፣ ሙሉ ያሉት ጭላጭ ሲሆን ፣ የሚሰጠው መቀበል ሲሳነው ፣ ምግቡ ሲገኝ ጠኔ የያዘው ሰው ሞት ሲወስደው ፣ ይበልጣል ያሉት ከሁሉ ኋላ ሲሆን ፣ የመራ ከሰልፉ ወጥቶ ሲንከላወስ ፣ አመኔታ የተጣለበት ለማነስ ሲቸኩል እንዳይደክመኝ ያህዌ እባክህ አግዘኝ ። የምፈልገውን ሳገኝ እንደ ገና ሌላ ፍላጎት ሲያድርብኝ ፣ ፍለጋ አያልቅም ብዬ ስጨነቅ ፣ አተርፋለሁ ካልኩት ነገር ራሴን ስከስር ፣ ኑሮን ቀብቼ ሕይወትን ሳፈርስ ፣ ዘላለማዊውን በወቅታዊ ስለውጥ ፣ የመለኮትን ሙላት በፍጡር ጉድለት ስለካ እንዳይደክመኝ ኤልሻዳይ ሆይ እባክህ ለውጠኝ ። የሠዋሁት ሲነሣ ፣ ሞቻለሁ ብዬ መኖር ስጀምር ፣ መስቀሉን ኋላ ዓለምን ከፊት ሳደርግ ፣ እንግዳ ነኝ ብዬ ዘምሬ ተደላድዬ ስቀመጥ ፣ ብዙዎችን ቀብሬ እኔ እንደ ሐውልት ቆሜ የምቀር ሲመስለኝ ፣ የሚያብራራ የሚያበራ መሆኑን ዘንግቼ ታግሼ መስማት ሲያቅተኝ ፣ የአንድ ደቂቃ ቁም ነገርን ስፈልግ ፣ ቁርጥራጭ እውነትን ሳስስ ፣ በኪራይ ዓለም ላይ ተከራይ ብዬ ሌላውን ስናገር ፣ እኔነቴ አናቴ ላይ ወጥቶ ሲያሰክረኝ ፣ ራስን መሸጥ ዘመናዊ ንግድ ሲመስለኝ እንዳይደክመኝ እባክህ አዶናይ ሆይ ከዚህ ሕይወት አስመልጠኝ ።

የማለን ሳምን ፣ ለሚያለቅስ ብቻ ስፈርድ ፣ ሥጋዊ ቅንዓት ሃይማኖታዊ ቅንዓት ሲመስለኝ ፣ የሚመቸኝን አስተማሪ እየፈለግሁ የሚመክረኝን ስጠላ ፣ የሚመለከተኝን ትቼ የማይመለከተኝን ኳስ ስናደድበት ፣ በራ ስለው ሲጨልም ፣ ወጣሁ ስል ስዳክር ፣ ወሬኛን ወድጄ ሠራተኛን ስንቅ ፣ ሌባን አፍሬ ልፋተኛን ሳሳድድ ፣ ድህነትን ሳይሆን ድሀን ሳስወግድ ፣ ዘፈንን አድንቄ መዝሙር ላይ ሳኮርፍ እንዳይደክመኝ እባክህን በቀኝህ ደግፈኝ ።

ወጭና ወራጁ ልቤን ሲያዝለው ፣ ቆንጆው መልኩ ሲጠፋብኝ ፣ የትላንት ሰጪ እጁ ጉንድሽ ሲሆን ፣ አላማጁ ለማጅ ፣ ሁሉም እንግዳ ሲሆን ፣ ዓለምን ለመቀየር ተነሣሁ ያሉ ኑሮአቸውን በመቀየር ሲፈጽሙ ፣ የከፋው አትኩሮ የሚያየው ሲያጣ ፣ ለትላንት አጽናኝ እንባውን የሚጠርግለት ሲጠፋ ፣ የቃል ትምህርት ቤት በዝቶ የተግባር ትምህርት ሲጠፋ ፣ ነገረ እግዚአብሔር ቀሎ ነገረ ሰብእ ሲከብር ፣ የመጽሐፉ ትንቢት ተንቆ አዲስ ባለ ራእይ ሲታሰስ ፣ በመዘጋጃው ቀን ሰርግ ሲደገስ ፣ ምሕረትህ ሳይማርከኝ ወይ ፍርድህ ሳያስፈራኝ ስንኖር ፣ ማስተዋል ጠፍቶ ወድቆ ማሰብ ሲጀመር እንዳይደክመኝ ወልድ ሆይ በኪዳንህ አስበኝ ።

የተማሩ እንዳልተማረ ሲሆኑ ፣ ንጹሕ ምንጭ ተንቆ የጎርፍ ውኃ ለመጠጥ ሲውል ፣ ውስጡ ፈርሶ ሰው ላዩን ሲያሳምር ፣ ተራራ ስህተቱን ችላ ብሎ የሌሎችን ነቍጥ ሲቆጥር ፣ እንዴት ልመለስ ለሚለው ምስኪን የገደል መንገድ ሲያሳይ ፣ አደራ ተበልቶ መንጋው ላይ አውሬ ሲሰማራበት ፣ ሕሊናም ሕግም ሲተወን ፣ አብረን በልተን ስንጋደል ፣ አብረን ዘርተን አብረን ማጨድ ሲሳነን ፣ የጋራን ምድር የግሌ ስንል እንዳይደክመኝ እባክህ ለልቤ ልብ ስጠኝ ።

ሥራ ሰጥቶ የሚቆጣጠር ፣ አዝዞ የሚከታተል የበላይ ሲጠፋ ፣ ቁጭት መክኖ ስንፍና ሲበረታ ፣ ነገን ለመግደል ስንራወጥ ፣ ትልቅነትን ከትልቅ ሥራ መጠበቅ ስናቆም ፣ መልእክት ይዘን ስንረሳ ፣ ለሩቅ ተጠርተን ቅርብ ስናድር ፣ በሽታ አስተኝተን የመንገድ ጨዋታ ሲያስቀረን ፣ ወደ ላይ መላእክት እንዲስቡን ቀርቶ ወደ ታች አጋንንት እንዲጎትቱን ወደን ስንማረክ እንዳይደክመን እባክህ አግዘን ።

እየበላሁ ረሀብ ሲሰማኝ ፣ አግኝቼ እጦት ሲያሰቃየኝ ፣ የልመናዬ መልስ ምስጋና ቢስ ሲያደርገኝ ፣ አልቅስ አልቅስ እያለ ጠላቴ ሆድ ሲያስብሰኝ ፣ መዳኔ አንሶብኝ ምሬት ሲያነጋግረን ፣ የሌላቸውን እያጽናናሁ ፣ መቻልን እየነገርሁ እኔ ባለኝ ነገር ማመስገን ሲሳነኝ ፣ ትላንትን አልፌ ዛሬ ሲያስፈራኝ ፣ ማፍቀር ደክሞኝ መጣላት ሲቀለኝ ፣ መዝራት ተስኖኝ መንቀል ሥራ ሲሆንብኝ ፣ ዛሬን ሳልኖረው ነገ ሲያስፈራኝ እንዳይደክመኝ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ ሆይ እባክህ አግዘኝ ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መስከረም 13 ቀን 2017 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም