የትምህርቱ ርዕስ | እኛን ይወደናል

“ገና ደካሞች ሳለን ክርስቶስ ዘመኑ ሲደርስ ስለ ኃጢአተኞች ሞቶአልና።” ሮሜ. 5፡6 ።

አንዳንድ ሰዎች ደስተኞች ናቸው ። ሳቃቸው ያስቃል ፣ ደስታቸው ይማርካል ። የተመቻቸው ባይሆንም ለመደሰት ግን ቁሳዊ ዋስትና አልፈለጉም ። የሕሊና ነጻነት የናፈቃቸው ሰዎች እነዚህን ሰዎች ማግኘትና አብሮ ማሳለፍ ይፈልጋሉ ። እነዚህ ሰዎች የባለጠጎች አጫዋች ሆነው አብረው አገር ካገር የሚዞሩ ፣ በአጫዋችነት ብዙ ገንዘብ የሚያከማቹ ሆነው ይሆናል ። ኮሜድያንም ከተለመደው ሕይወት ወጣ ብሎ ለመሳቅ መድረክ አዘጋጅተው ፣ አስከፍለው ያስቁናል ። የኑሮ ማደንዘዣ የሚሆኑ ጨዋታዎችን እንናፍቃለን ። ለደቂቃም ቢሆን ይህን ዓለም መርሳት እንደ ዕድል እንቆጥረዋለን ። አዎ ለደቂቃም ቢሆን ። የተወለድነው በደቂቃ ፣ የምንሞተውም በቅጽበት ነው ። ደቂቃ ዋጋ አላት ። ተጨንቆ ለሚያውቅ የደቂቃ እፎይታ በብዙ ገንዘብ አትገዛም ። ነጻነት ባይሰጡንም ነጻ የሚያደርጉንን ደስተኛ ሰዎች እጅግ እንወዳቸዋለን ። ውድ ሆነውብን እንደ ፈለግን ባናገኛቸውም ፣ ከአጠገባችን ባይርቁ እንመርጣለን ። የወደድነው ግን ሰብእናቸውን ሳይሆን ደስታቸውን ነው ።

መልከ ቀናን የሚጠላ ፣ ጥሩ አቋም ያለውን የማያደንቅ ጥቂት ሊሆን ይችላል ። መልክ የተሰጠ ቢሆንም ጥበቃ ይፈልጋል ፣ ቁመናም ግንባታና ዲሲፕሊን ይሻል ። ወንዶች ቆንጆ ሴትን ማግባት ይፈልጋሉ ። ጥበቃው እንደሚያደክም ግን አያውቁትም ። ሴቶችም ቁመናው ያማረ ወንድ ባል ቢሆናቸው ይመኙ ይሆናል ። እንዲህ ያለ ወንድ ግን ልቡ ቤት የሚያድረው ጥቂት ነው ። መልክና ቁመና ረጋፊ ቢሆኑም የሰዎችን ጠባይ ግን ይቀይራሉ ። መልክ ያላቸው ጠባያቸው እንደ ሳማ የሚለበልብ ሊሆን ይችላል ። ቁመናቸው ላይ ጊዜ ሲያጠፉ ጠባያቸውን ይረሱታል ። እነዚህን ሰዎች የወደድናቸው ራሳቸውን ሰዎቹን ሳይሆን መልክና ቁመናቸውን ነው ።

ታማኝ ሰዎች ፣ ታማኝ ያልሆኑ ነገሥታትና ባለጠጎች በመብራት ይፈልጉአቸዋል ። በፈርዖን ቤት ሙሴ ፣ በአክአብ ቤተ መንግሥት ነቢዩ አብድዩ ፣ በአርጤክስስ መንግሥት አስቴርና መርዶክዮስ ፣ በቂሮስ አገዛዝ ነህምያ ነበሩ ። የነገሥታት የቅርብ ሰዎች አማንያን ናቸው ። “ታማኝ ሰው ፈልጉልን” እያሉ ባለጠጎች ደጅ ይጠናሉ ። ታማኝነት በመብራት የሚፈለግበት ዘመን ላይ እንዳለንም ምስክሮች ነን ። እነዚህን ታማኞች የምንወዳቸው ስለማይጎዱን ፣ ሕይወታችንንና ንብረታችንን ስለሚንከባከቡ ነው ። ራሳቸውን ሰዎቹን ግን ላንወዳቸው እንችላለን ።

እግዚአብሔር ግን የወደደው ተጫዋችነታችንን ፣ መልከ ቀናነታችንን አሊያም ጥሩ ስማችንን አይደለም ። እግዚአብሔር የወደደው እኛን ነው ። የወደደንም ገና ደካሞች ሳለን ነው ። የሚገርመው የሞተልንም ገና እንደምንበድለው እያወቀ ነው ። ያሉን ነገሮች በዜሮ ሲባዙ የወደዱን ሰዎች ይጠሉናል ። እግዚአብሔር ግን ለዘላለም ይወደናል ። እርሱ የሚወደው እኛን ነውና ። በድለን ንስሐ ስንገባ እግዚአብሔር እንዲወደን እያደረግን አይደለም ። እርሱ ለዘላለም ይወደናል ። እኛ ከቤት ባንወጣም ፀሐይ ትወጣለች ። እኛን ሳይጠብቅ እግዚአብሔር ወዶናል ። ብዙ ፍቅሮች ይፈተናሉ ፣ መንገድ ላይ ይቀራሉ ። ገና ደካሞች ሳለን የወደደን ግን ደከሙ ብሎ አይጠላንም ። “ምሕረቱ ለዘላለም ነውና” ትርጉሙ “ፍቅሩ ለዘላለም ነውና” ማለት ነው ። እስከ ዘላለም የቃል ኪዳን አጋሮቻችንና ልጆቻችንም አይወዱንም ። አንዲት ድሀ አሮጊት ልጆቻቸው ትልልቅ ቦታ ነበሩና “አይረዱዎትም ወይ?” ብላቸው “አይ ልጄ ዕድሜ ሲረዝም ልጅ አይወድም” አሉኝ።

ጠጪዎችና ሱሰኞች ተግባራቸው መልካም አይደለም ። እነርሱን ከተግባራቸው ነጥለን መውደድ ግን አንችልም ። እግዚአብሔር ኃጢአትን እየጠላ ኃጢአተኞችን ይወድዳል ፤ እኛ ደግሞ ኃጢአትን እየወደድን ኃጢአተኞችን እንጠላለን ። በዘማውያን ላይ ስንፈርድ እንውላለን ። መንገድ ላይ የሚቆሙትን ሴቶች እንደ አገር ጥራጊ እናያቸዋለን ። ክርስቶስ ግን እንደሚወዳቸው ለእነርሱም እንደ ሞተ ዘንግተናል ። የእርሱን የፍቅር ፀሐይ ለማስተላለፍ መስተዋት ልባችን ቆሽሾአል። ካልወደድናቸው እንዴት እግዚአብሔር ይወዳችኋል ብለን መናገር እንችላለን ? ሰውን ከክፋቱ የምንመልሰው በመውደድ እንጂ በመጥላት አይደለም ። እግዚአብሔር በደለኞች በኃይል ሳይሆን በፍቅር መማረክ ይሻል ። እኛ ደግሞ ፍቅርን ትተን በጥላቻ ሰዎችን ለመቀደስ እንፈልጋለን ። እነርሱ በሱስ ወድቀዋል ፣ እኛ ደግሞ በጥላቻ ወድቀናል ።

አዎ እግዚአብሔር የሚወደው እኛን ነው ። ይህ ፍቅር ፍጹም ነውና መጨመርና መቀነስ የለበትም ። በዚህ ፍቅር እባካችሁ ተመሰጡ! የተሰቀለው ክርስቶስ ፍቅሩ ይብዛልን ! አሜን ።

ዕለተ ብርሃን 8

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

መስከረም 10 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም