መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » እኮ እንዴት ?!

የትምህርቱ ርዕስ | እኮ እንዴት ?!

ባለፈው ዘመን ተደርጎ ነበር ወይ ? ተደርጎስ ከሆነ የሰለጠነው ዘመን እንዴት ሊደግመው ደፈረ? ማወቅ በድንቁርና ፣ ዘመናዊነት በአራዊትነት እንዴት ተለወጠ ? እኮ እንዴት ?! ዘርን አጠፋለሁ ብሎ ፈርዖን ተነሥቶ ነበር ፣ የቅርብ ዘመን ጨካኞችም ይህን ፈጽመዋል ። እስራኤል ግን አልጠፋችም ። በመቃብር ላይ ነፍስ ዘርታ የዓለም ጥያቄ ሆናለች ። እግዚአብሔር የፈጠረውን አጨርሳለሁ ብሎ ማሰብ እኮ እንዴት ?! ሌላው ሲፈተን እኔ አልፈተንም ፣ ሌላው ሲቀብር የእኔ አይሞትም ብሎ ማሰብ እኮ እንዴት ?! የልደት መጨረሻ ሞት አይደለም ወይ ?

በመከራ ዓለም በመከራ መደንገጥ ፣ ሞተ ነፍስን አስቀምጦ በሞተ ሥጋ ጉድ ማለት እኮ እንዴት ?! በስደት ምድር ላይ ተደላድሎ መቀመጥ ፣ ለእነዚያ ያለፈች ዓለም ለእኔ አታልፍም ብሎ መረጋጋት እኮ እንዴት ?! በሌሎች ክፉ ቃላት ተሰብረን የእኔ ክፉ ቃል አይሰብርም ማለት ፣ የሌላውን እንደ ጦር የራስን ቃል እንደ መጦር ማሰብ እኮ እንዴት ?! መብል እየወደዱ ሥራን መጥላት ፣ ከሴት ተወልዶ ሴትን ማስጨነቅ እኮ እንዴት ?!

ጠብታው ውኃ ዓለትን ይሰነጥቃል ፣ የተኛውም በሬ ከቆሰቆሱት አውሬ ይሆናል ፣ ግለሰብ ሲጠቃ ቀጥሎ ሕዝብ ይጠቃል ። መጽሐፍ ሲቃጠል ቀጥሎ ሰው ይቃጠላል ። ክፋት በጥቂቱ ተጀምሮ በብዙ ያድጋል ። ወንዙም ከምንጭ ይጀምራል ። ክፉ ነገር በጽንሱ ካልቆመ ልደቱ ሞት ይሆናል ። የዘራውን ያህል የሚያጭድ ገበሬ የለም ፣ ከዘራው በላይ ግን ስለ አንዱ ሠላሳ ፣ ስድሳ ፣ መቶ ፍሬ ያጭዳል ። በእንቁላሉ ያልቀጡት ልጅ በሬ ሰርቆ ይመጣል ። የዘራነውን ለማጨድ መማረራችን እኮ እንዴት?!

ያሳደጉት ልጅ ሽማግሌ ሲገርፍ ፣ ያጎረሱት ወዳጅ እጅ ሲነክስ ፣ ጥግ የሆኑት ጥግን ሲያፈርስ ፣ አብሮ የኖረ ገዳይ ሲመጣ አሳልፎ ሲሰጥ ፣ ተማሪ ወንበዴ ሁኖ ሽፍታ እየመራ ሲመጣ እኮ እንዴት ?! ክርስቶስን በጭካኔ የተቀበለች ዓለም ለእኔ ትራራ ማለት እኮ እንዴት ?! ማስተማር የሚቀጥለው በመማር ነው ። የእናት ጡት የሚመነጨው እናቲቱ ስትመገብ ነው ። ምድር ፍሬ የምትሰጠው ዘር ሲጥሉባት ነው ። በአንድ እውቀት ለማርጀት ማሰብ እኮ እንዴት ?! እረኝነት በግ መሆን ፣ መሪነትም መመራት ያሻዋል ። ምንም ቢፈረጥም የሜዳ አህያ ጭነት አይችልም ። ትከሻው ቢያምርም አንበሳ ቀንበር አይሸከምም ። አባት የሚሆን ፣ ልጅ የነበረ ነው ። የሰው ችግር የሚያሳዝነው በችግር ያለፈ ጨዋ ሰው ነው ። አስቀድመህ ሳትታዘዝ ለማዘዝ መሞከር እኮ እንዴት?! ያልተማረ መምህር ተማሪ ያውር ። ያልተማረ ቄስ ሁሉን ያረክስ ። የተማረ ቄስ ርኵስ ይቀድስ ፣ ሕዝብ ይመልስ ! እኮ እንዴት ?!

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ተጻፈ ሐምሌ 13 ቀን 2015 ዓ.ም

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም