የትምህርቱ ርዕስ | እውነተኛ ጌጥ

 “እንዲሁም ደግሞ ሴቶች በሚገባ ልብስ ከእፍረትና ራሳቸውን ከመግዛት ጋር ሰውነታቸውን ይሸልሙ ፤ እግዚአብሔርን እንፈራለን ለሚሉት ሴቶች እንደሚገባ ፥ መልካም በማድረግ እንጂ በሽሩባና በወርቅ ወይም በዕንቍ ወይም ዋጋው እጅግ በከበረ ልብስ አይሸለሙ ።” 1ጢሞ. 2፡9-10
የወንዶች ትልቁ ፈተና አለመጸለይ ነው ። ሁሉን በጉልበቴ አደርገዋለሁ በማለት ከቤት አልፎ በዓለም ላይ ጦርነትን እየለኮሱ ሕይወትን ጭንቅ እያደረጓት ነው ። ወንዶች ጌጥ ፈተናቸው አይደለም ። የተጨማደደ በመልበስ ፣ ያልተጠረገ ጫማ በማጥለቅ የታወቁ ናቸው ። ጌጥን ለመውደድ በረቂቅ ማየት ይፈልጋል ። ከአጠቃላይ አንጻር የሚያዩና ቸልታን የሚመርጡ ወንዶች የጌጥ ፈተና የለባቸውም ። ብዙ ጊዜ ሴቶች ጌጥን በመውደድ ይፈተናሉ ።

ቤተ ክርስቲያን ለየጾታው የሚሆን አምላካዊ ምክር አላት ። ወንዶችና ሴቶችን አድራሻ አድርጋ ለመናገር አምላካዊ አደራ አለባት ። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ወንድና ሴት ለብቻ ቆመው እንዲጸልዩ በማድረግ አርቃ አጥራለች ። ይህም የሚደነቅ ነገር ነው ። በቤተ ክርስቲያን ውስጥም የልብስና የጫማ ውድድር እንዳይኖር ወንዱም ሴቱም አንድ ዓይነት ነጠላ እንዲለብስ አድርጋለች ። በዚህም ሀብታምና ድሀ የሚል የኑሮ ልዩነት እንዳይታይ ሠርታለች ። ይህ የሌላቸው አብያተ ክርስቲያናት በምእመናን መካከል የልብስ ውድድር ውስጥ ገብተው ፣ በጨርቅ ተባርኬአለሁ እገሌ አልተባረከም ወደ ማለት ደርሰዋል ። ክብርት ቤተ ክርስቲያን ግን የሥጋ ነገር ርእስ እንኳ እንዳይሆን አድርጋ አስቀድሞ አጥራለች ። በዚህም ልትመሰገን ይገባታል ። ሰው በቤተ ክርስቲያንም ሆነ በደጅ ለማሳየት መጣር ያለበት ክርስቶስ ወይም በክርስቶስ የተለወጠውን ሕይወት ብቻ ነው ።
ከቅድስና ትምህርቶች አንዱ አለባበስ መሆኑን ብዙ ክርስቲያኖች የተረዱት አይመስሉም ። ክርስቲያናዊ አለባበስ እጅግ አስፈላጊ ነው ። ምስክርነትና ከዓለም ሰዎች የምንለይበትም ነው ። ይህ ማለት መጎሳቆልና መቆሸሽ ጽድቅ እንደሚመስላቸው ሰዎች እንሁን ማለት አይደለም ። መቆሸሽ ጽድቅ ሳይሆን ስንፍና ነው ። መድኃኔ ዓለም ውኃን አብዝቶ የፈጠረው እንድንጸዳ ነው ።
በአእምሮ ጭንቀት ውስጥ የሚያልፉ ሰዎች ከመጠን በላይ ጌጥ ያበዛሉ ። የሚያልፉበትን ሕይወት ሰዎች ያወቁ ሲመስላቸው አንድ ጌጥ ይደርባሉ ፣ አይበቃም ሲሉ ሌላ ይጨምራሉ ። በጣም ማጌጥ ድሎት ሳይሆን ጭንቀትም ሊሆን ይችላል ። አትኩሮትን ፈላጊነት ጌጥን ማብዛት ያመጣል ። ጫማው ድምፅ የሚሰጥ ሲሆን መጣ ፣ መጣ እየተባልሁ ነው የሚል ስሜት ያመጣል ።ሽቶው ለወረዳው የሚሸት ከሆነ አልፌም አልረሳም ብለው ያስባሉ ። ወርቁ የውሻ ሰንሰለት ከመሰለ ሀብታም እባላለሁ በማለት አትኩሮትንና ርእስ መሆንን የሚፈልጉ ወገኖች አሉ ። እነዚህ ሰዎች የምንፈርድባቸው ሳይሆን ትልቁን ጌጥ መንፈሳዊነትን ልናስተምራቸው ይገባናል ።
የዓለማችን ሀብት ከሚባክንባቸው ነገሮች አንዱ ጌጥ ነው ። የጌጥ ትልቁ ችግር ውስጣዊውን ውበት እንድንረሳ ያደርገናል ። ደራሲው “ውበት ማጥመጃ ብቻ ሳይሆን መጠመጃም ነው” እንዳለ ጌጥና ውበትን በጣም መውደድ አይገባንም ። ምድራዊው ውበት መቃብር የሚያበቃ ፣ ጌጡም ተከትሎ ሰማይ የማይገባ ነው ። ሐዋርያው ራስን ስለ መጣል እያስተማረ አይደለም ።ራስን መጣልም ተገቢ አይደለም ። ራሳችንን ከጣልነው የሚያነሣን ማንም የለም ። ብዙ እህቶች ወደ ትዳር ከገቡ በኋላ ራሳቸውን በመጣል ኑሮን ብቻ በማሰብ ይጎሳቆላሉ ። በተገቢው መንገድ ራሳችንን መጠበቅ ግን ይገባናል ። ምክንያቱም ሰውነታችን ከእግዚአብሔር በአደራ የተቀበልነው ነውና ።
እግዚአብሔር ሰውን ሲፈጥር ለሴት ልጅ መሸፈን ክብር ፣ ለወንድ ደግሞ እፍረት እንዲሆን አድርጎ ነው ። ሴት ልጅ መሸፈን እንዳለባት የፀጉር ካባዋ ገላጭ ነው ። የሠራን እግዚአብሔር የሚያምርባችሁ እንዲህ ነው ካለን የማንንም ምክር መጠበቅ አያስፈልገንም ። ሴት ልጅ ፀጉሯ ካባዋ ከሆነ ፀጉሯን መንከባከብ አለባት ማለት ነው ። ልታይ በማለት ግን ጌጥን ማብዛት ተገቢ አይደለም ። እዩኝ ፣ እዩኝ ማለት ደብቁኝ ፣ ደብቁኝ ያመጣልና ። ከተማውን ሞልተው የነበሩ ቆንጆ ሴቶች ዛሬ የት እንዳሉ አይታወቅም ። እግዚአብሔር እርሱን ስናሳይ እንጂ ልታይ ፣ ልታይ ስንል አይወድም ። አሁን ካሉት ቆንጆዎች ፣ ዛሬ ካሉት ጌጠኞች ያለፉት ይበልጣሉ ። ሁሉም ጥርኝ አፈር ሁነዋል ። ይህችን ዓለም በጥቂቱ ተረስቶ ማሳለፍ ጤና ነው ። የመሰንበት ምሥጢሩ መሰወር ነው ። ለቅማችሁ መጨረስ እስኪያቅታችሁ ፎቶአችሁን የበተናችሁ መካሪስ ዘመድ አልነበራችሁም ወይ ? እንደ ሞኝ በገዛ ፎቶአችሁ ስትዝናኑ አይገርማችሁም ወይ ? የተፈጠራችሁት ፍቅራችሁን እንጂ ፎቶአችሁን እንድታሳዩ አልነበረም ። የቅዱሳንን ሥዕል ሲቃወሙ የነበሩ ዛሬ በየአምልኮ ቦታቸው የራሳቸውን ፎቶ ሰቅለው ፣ አጋንንት ፎቶአችንን ሲያይ ይወድቃል ይላሉ ።
እንደሚገባ ሰውነትን መሸለም ማለት ዕራቁትነትን መሸፈን ብቻ ሳይሆን የሰውነት ቅርጽንም መሰወር ነው ። የሰው ልጅ ውበት ያለው በልብስ ውስጥ ነው ። እንስሳት ቢከሱ ፣ ቢወፍሩ ያለ ልብስ ያምራሉ ። እኛ ግን ክሳታችንም ውፍረታችንም ያለ ልብስ የሚያምር አይደለም ። ብዙ ሰዎች ለማውለቅ የሚግደረደሩ እስኪመስል የተቦጨቀ ልብስ ጣል አድርገዋል ። ሌሎችም ቅርጻቸው እስኪታይ የተጣበቀ ልብስ ለብሰዋል ። መሸለም ግን የክርስቲያን ወግ ነውና መልበስ ይገባናል ። ይልቁንም በአምልኮ ስፍራዎች ላይ ሴቶች መሸፋፈን ይገባቸዋል ። እንደሚገባ ሳይለብሱ ቤተ መንግሥት መግባት ክልክል ነው ። የእግዚአብሔር ቤት ከቤተ መንግሥት በላይ ነው ።
የሴቶች ውበት የተቀደሰ ማፈር ነው ። እግዚአብሔር ሲፈጥራቸው ተገቢ ማፈርን ውበት አድርጎላቸው ነው ። የማያፍሩ ማለት ተራቁተው የሚለምኑ ማለት ነው ። የሴት ልጅ ክብሯ ለባሏ ብቻ ስትገለጥ ነው ። ተገቢ እፍረት ለወንዶችም አስፈላጊ ነው ። መሰልጠን የራቃቸው ሰዎች ማፈርን ስላቆሙ በድፍረት ነቢይና ፈዋሽ ይሆናሉ ። እግዚአብሔርን የማይፈራ ሰውን የማያፍር ማለት ትልቅ ንግግር ነው ። ሰው ሁለቱም ነገሮች ሲለዩት ቆሞ የሚሄድ አውሬ ይሆናል ።
ለሴቶች ራስን መግዛት ትልቁ ውበታቸው እንደሆነ ተነግሯል ። ራስን መግዛት ለወንዶች ብቻ የሚነገር አይደለም ። ሴቶችም በተሰጣቸው ኑሮና የትዳር ጓድ ረክተው ሊኖሩ ይገባቸዋል ። የእነርሱ ባል ከሁሉ የተሻለ ነው። ድስት ያለ ግጣሙ እንዲሉ ሰው ባልተሰጠው ቦታ ትርፍ ወይንም ጎዶሎ ነው ። ራስን መግዛት ለዝሙት ብቻ የሚነገር ሳይሆን በንግግርም ፣ በቅንዓትም ራስን መግዛት ይገባል ።
“እግዚአብሔርን እንፈራለን ለሚሉት ሴቶች እንደሚገባ ፥ መልካም በማድረግ እንጂ በሽሩባና በወርቅ ወይም በዕንቍ ወይም ዋጋው እጅግ በከበረ ልብስ አይሸለሙ” ይላል ። መልካም ማድረግ የሴቶች ዋነኛ መገለጫ ነው ። ኤልያስን የተቀበለችው የሰራፕታዋ መበለት ፣ ለኤልሳዕ ቤት የሠራቸው የሱነም ሴት መልካም አድራጊዎች ናቸው ። በየትኛው ዘመን ለአገልግሎትና ለአገልጋዮች የሚያዝኑና የቤተ ክርስቲያን ደጃፍ እንዲከፈት የሚጥሩ ሴቶች ናቸው ። ብዙ ወርቅና ጌጥ የሚያበዙ ሴቶች ለመልካም ሥራ ጊዜም አቅምም እያጡ ይመጣሉ ። መልካም ሥራ ከትርፍ ሳይሆን ከጉድለት ነውና ። ብዙ ልብስ ያላቸው የቱን ልልበስ ሲሉ ሰዓታት ይፈጃሉ ። ቶሎ ለብሶ የሚወጣ ትንሽ ልብስ ያለው ነው ። በመጠን መኖር ጊዜን ማትረፊያ ነው ። ወርቅና ዕንቊም ጠላት ማትረፊያ እንጂ በዛሬ ዘመን ጌጥ አይደለም ። ሰው በቀላሉ የሚያየውንም ኑሮ ሳይሆን የተሰወረውን ሕይወት መምረጥ ይገባል ። ደግሞም ጌጥ ወዳድነት ውድድር የሚወልደው ነው ። ገንዘብ ሥር የለውምና መልሶ መውደቅ እንደሚመጣ በማሰብ ቁምነገር ልንሠራበት ይገባል ።
አቤቱ ጌታ ሆይ ለቤትህ ሥራ የደከሙትን እናቶችና እህቶችን አትርሳ ።
1ጢሞቴዎስ 30
ታኅሣሥ 29 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም