መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » አዲስ ኪዳን » ኤፌሶን ትርጓሜ » እውነቱ ያለው ማን ጋ ነው ?

የትምህርቱ ርዕስ | እውነቱ ያለው ማን ጋ ነው ?

“በእርግጥ ሰምታችሁታልና ፥ እውነትም በኢየሱስ እንዳለ በእርሱ ተምራችኋል ፤” ኤፌ. 4 ፡ 21።

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዕርቃኑን በመስቀል ላይ የዋለው እውነት ስለሆነ ነው ። እውነት ከፍ ብላ ትሰቀላለች ። ሰቃዮች አዋረድን ብለው እውነትን ከፍ አድርገው ይሰቅሏታል ። ከፍ ካላለ ሰንደቅ ዓላማ አይታይም ። ክርስቶስም ከፍ ብሎ ባይሰቀል ክርስትና አይታይም ነበር ። እውነት ሽፍንፍን የለውም ። ስለዚህ ክርስቶስ ዕርቃኑን ተሰቀለ ። ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብ ፍጹም ግልጽነት አስፈላጊ ነው ። እግዚአብሔር ምን ያህል ብቁ ነህ ? ሳይሆን ምን ያህል ግልጽ ነህ ? የሚል አምላክ ነው ። ክርስቶስ ክፍ ብሎ መሰቀሉ ሁሉ ያየውና ያምንበት ዘንድ ነው ። ክርስቶሰን አለማመን ሊኖር ይችላል ፣ አለመስማት ግን እንዳይኖር ወንጌል ሊሰበክ ይገባዋል ። ዓለም ለእውነት የመደበችው ስፍራ መስቀል ነው ። የመጨረሻ ውርደት በነበረው መስቀል ላይ እውነት የሆነው ክርስቶስ ቢሰቀል መስቀል የመጨረሻው የክብር ዙፋን ሆነ ። መስቀል ዙፋን ነው ፣ ክርስቶስ ውሎበታልና ። መስቀል ጻሕል/ገበታ ነው ፣ ክርስቶስ ሥጋውንና ደሙን ሰጥቶበታልና ። መስቀል ሰንደቅ ነው ፣ ዓላማ የሆነውን ክርስቶስ ያሳያልና ። መስቀል ማካፈያ ነው ፣ ጻድቅና ኃጥእ ተለይቶበታልና ። ዓለማት የማይችሉት በማኅፀነ ማርያም ሲወሰን መስቀል ነው ። መስቀል የማይወሰነው ለመወሰን መፍቀድ ነው ። መስቀል ብዙ ፍቺ አለው ። ዕድሜ ልካችንን የምኖረው ነውና ትርጉሙን ሁሉ አሁን ማወቅ አያሻንም ።

ብዙ ሰዎች ብዙ ነገር ይሰማሉ ። ያለንበት ዘመን የምንሰማውንና የምናየውን ካልመረጥን ብዙ አማራጭ ያለበት ዘመን ነው ። የሚያስፈልገንን ሽተን ስናስስ የምንፈልገው ጋ ሳንደርስ ሰዓታችንን የሚበላ ፣ አንጎላችንን የሚያናጋ ብዙ ወሬ አለ ። የምፈልገው ምንድነው ? ለምፈልገውም የመደብኩት ሰዓት ስንት ነው  ማለት ያስፈልጋል ። የማንፈልገውን በተለጠጠ ሰዓት በማየትና ራስን በማድከም መኖር የዕድሜን አጭርነት አለመገንዘብ ነው ። ሰዎች ፍቅርን በለስላሳ ጆሮ ይሰማሉ ፣ ጥላቻን ግን በድምቀት ያደምጣሉ ። ያበበውን ነገር በማየት በእርግጥ የሰማነውን ማወቅ ይቻላል ። ወንድማማችነት ካበበ ፍቅርን በእርግጥ ሰምተናል ማለት ነው ። ባለመስማት ውስጥ መስማት አለ ። በመስማት ውስጥም አለመስማት አለ ። በመስማት ውስጥም በእርግጥ መስማት አለ ። በእርግጥ ልንሰማው የሚገባውን መለየት ያስፈልጋል ።

በእርግጥ የምንሰማው አሽሙርን ከሆነ የሚራመደው እግራችን ይወላከፋል ። በእርግጥ የምንሰማው አሉባልታን ከሆነ የተነቃቃው ራእያችን ይከስማል ። በእርግጥ የምንሰማው ሰዎች የሚሰጡንን መደብ ከሆነ ጽንፈኛነት ያጠቃናል ። በእርግጥ የምንሰማው ራሳችንን ከሆነ ግምታችን ያደናግረናል ። በእርግጥ የምንሰማው ጀማውን ከሆነ ሁሉም ነገር ያለቀ ይመስለናል ። በእርግጥ የምንሰማው ጠብ ዘሪዎችን ከሆነ እሳቱ እንዳይጠፋ እንጨት አቀባይ ያደርጉናል ። በእርግጥ የምንሰማው ትሞታላችሁ የሚሉንን ከሆነ ሕይወት የእግዚአብሔር ቀመር መሆንዋን ያስረሱናል ። በእርግጥ የምንሰማው የክፉን ፉከራ ከሆነ የያዝነውን ያስጥለናል ። በእርግጥ የምንሰማው ትላንትን ከሆነ ጸጸት በእሳት ጅራፍ ይገርፈናል ። በእርግጥ የምንሰማው ዛሬን ከሆነ ዜናው ያውከናል ። በእርግጥ የምንሰማው ነገን ከሆነ ተስፋ ያጥርብናል ። በእርግጥ የምንሰማው ኢኮኖሚውን ከሆነ እየበላን ይርበናል ። በእርግጥ የምንሰማው ነፋሱን ከሆነ የረገጥነው መሬት ይከዳናል ። በእርግጥ የምንሰማው ሰይጣንን ከሆነ የእግዚአብሔርን ፍቅር ያጠራጥረናል ።

ክርስቶስን በእርግጥ የሰሙ ለዛሬውም ለዘላለሙም ያርፋሉ ። በእግዚአብሔር የተፈጠረ ዓለም የሚድነው በእግዚአብሔር ብቻ ነው ። እግዚአብሔር ይህን ዓለም ሲያበጀው የሌለውን ወደ መኖር እንደሚያመጣ አሳየን ፣ በዚህም ከየት ታመጣዋለህ ? የማይባለው አምላክ ሊረዳን እንደሚችል አስተማረን ። እግዚአብሔር ይህን ዓለም በለቢሰ ሥጋ ሲያድነው ጥፋታችንን መጨረሻ አድርጎ የማይጥለን አምላክ መሆኑን ነገረን ። ይህን ዓለም ሊያሳልፍ ዳግም ሲመጣም የአደባባይ ተግባራችን የአደባባይ ፍርድ እንደሚሰጥበት ያስተምረናል ። በእርግጥ እርሱን ሰምተናል ወይ ? ብለን ራሳችንን መጠየቅ አለብን ።

“እውነትም በኢየሱስ እንዳለ በእርሱ ተምራችኋል ፤” ይላል ። ብዙ ሰዎች ሃይማኖት በዛ ማንን እንመን ? ይላሉ ። ብዙ ሰዎች በግራና በቀኝ ዓይናቸውን አፍጥጠው የሚናገሩ ሰዎችን በማየት ትክክሉ የማን ነው ? ግራ ገባን ይላሉ ። ሽምግልና የተቀመጡ ባልና ሚስትን የሚያዳምጡ ሁለቱም ተመርረው ሲያለቅሱባቸው እውነቱ ማን ጋ ይሆን ? ብለው ይጨነቃሉ ። ሲለያዩ የሚቦጫጨቁ ፣ ሲገናኙ የሚሳሳሙ ሰዎችን በማየት ሰዎች እውነቱ ፍቅር ነው ወይስ ጥላቻ ? ብለው ግራ ይጋባሉ ። እገሌም የሚናገረው እገሊትም የምትለው ሳይሆን እውነት ያለው ክርስቶስ ጋ ብቻ ነው ። እውነቱን አውቀው ቢሞቱም የማይቆጫቸው ሰዎች አሉ ። እውነትን መጠማት እስከዚህ ድረስ ያስመኛል ። እውነቱ ግን ያለው እግዚአብሔር ጋ ነው ። እግዚአብሔር ሁላችሁም ዝም በሉ ብሎ እውነትን ሲናገር ያን ቀን እንደነቃለን ። ተጋርዶ የሚቀር ቀን ፣ መሽቶ የሚቀር ሌሊት የለም ። እግዚአብሔር ትልቅ ነውና እኛ እየለፈለፍን እርሱ አይናገርም ።

ክርስቶስ በእርግጥ የምንሰማው ነው ። ይዋሸናል ብለን አንጠራጠረውም ። ክርስቶስ እውነት ነው ፣ ይከዳናል ብለን አንሰጋውም ። ክርስቶስ ትምህርት ነው ፣ እንደሚያሳርፈን እርጠኞች ነን ።

አቤቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ፣ የተራቆተችውን ነፍስ በእውነትህ ክዳን አልብሳት ። አሜን።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥቅምት 26 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም