የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

“እውነት ታብራ”

የዲ/ን አሸናፊ መኰንን ገጽ

                                                                        ማክሰኞ ጳጉሜ 4/ 2006
እንደ ፀሐይ የሚያበሩ፣ ጨዋነትንና የሴትነትን ማፈር የደረቡ፣ መንፈሳዊነት የተጫናቸው፣ ከበላያቸው ነፋስ ሳይሆን እግዚአብሔር እንዳለ የሚያምኑ፣ ያሉበትን ስፍራ እንደ ንስሐ ቦታ የቆጠሩ፣ ባላሰቡበት ቦታ ራሳቸውን ያገኙት፣ ሌት ተቀን በዕንባ የሚጣሩ፣ የዕንባን ቋንቋ ሰሚ ወደ ሆነው ጌታ አቤት! አቤት! የሚሉ  ባልቴት ናቸው። እኚህን ሴት ያየኋቸው በወኅኒ ቤት ውስጥ ነው፡፡ ስለ ጉብኝታችን ምስጋና ለማሰማት ልቅሶ እንቅፋት ሆነባቸው፣ ሳይናገሩ ከሚናገር ሰው በላይ ነገሩን፡፡ በመጨረሻ ዕንባቸውን ዋጥ አድርገው ጠንከር ባለ ቃል፣ መዝለፍለፍን ንቀው በፀና ቁመና፣ አንገት መድፋትን ሽረው በሥልጣን ቃል፡- “ልጆቼ አንድ ነገር ለምኑልኝ” አሉ፡- ድምፃቸው ስለ ተለወጠ ፈራሁ፡፡ ብዙ የሚናገሩ መስሎኝ ተዘጋጀሁ፡- “እውነት ታብራ ብላችሁ ጸልዩ” አሉና ጥለውን ወደ ማደሪያቸው ገቡ፡ “እውነት ታብራ”  የሚለው ቃል እስከዚህች ደቂቃ ልቤን ይመታዋል፡፡ እኚህ ባልቴት እውነት ብታበራ እኔ እዚህ አላድርም በማለት በንጽሕናቸው የተማመኑ ናቸው፡፡
ክፉ ጎረቤት፣ ስቶ የሚያስት ብልሹ ሰው፣ ኃጥኡን አጽድቆ ጻድቁን የሚኰንን ክፉ ምስክር፣ ጉቦ የበላ ዳኛ … የእኚህ ባልቴት ስቃይ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ምክንያቱን ማወቅ ግን አስፈላጊ አይደለም፡፡ የታዘዙትን ማድረግ ግን ግድ ይላል፡- “እውነት ታብራ” ብሎ መጸለይ።

ሐሰት የተስማማቸው፣ ሌብነት ያበለጸጋቸው፣ ካለመዱት መንፈስ  ቅዱስ የለመዱት ሰይጣን ይሻላል የሚሉ፣ ምንም ትክክል ባይሆን ብዙ ዘመን የኖርኩበትን ሐሰት ማለት አልፈልግም የሚሉ፣ ዘመኑ ተለባብሶ ተመሳስሎ ነው እያሉ ወሽካታነታቸውን ለዘመኑ የሚያሸክሙ፣ ግትር በማለት እነ እገሌ ምን አገኙ የሚሉ፣ ስለ ሐቅ የተከፈለውን ዋጋ ሞኝነት በማለት የሚተቹ፣ እንደ ድመት ምቾታቸውን እያመለኩ ከቤተ መንግሥት ወደ ቤተ መንግሥተ እየተገላበጡ የሚኖሩ፣ በአንድ ጊዜ ሁለት ሰው መሆን የማይከብዳቸው፣ በልባቸው እየረገሙ በአፋቸው የሚመርቁ፣ በጥርሳቸው ሰውን ሁሉ መቅበር እንደ ልዩ ችሎታ የሚቆጥሩ፣ በገንዘብ ፍቅር የተነደፉ፣ ኑሮዬ ይበቃኛል ማለትን የማያውቁ፣ አልጠግብ ብለው ሲተፉ የሚኖሩ፣ ልኬ ይህ ነው በማለት ከማረፍ የልኩን ድንበር አጥተው የሚባዝኑ፣ ፍርድን እያዛቡ ጨለማውን ብርሃን የሚሉ፣ ፊት አይተው ጉቦ በልተው ደካማዋን የሚያጠቁ፣ ምን ይጠቅመኛል እያሉ የሚወዳጁ “እውነት ትጨልም” ይላሉ፡፡ ካልጨለመ መፋነን አይችሉም። ስለዚህ እውነትና ፍትሕን ሲያፍኑ ይኖራሉ። የሌባ ትልቅ አጋዡ ጨለማ ነው። ለሌባ ትንሽ ብርሃን ተዋጊው ነው።


በዚህ ተቃራኒ የእውነት አገሯ የት ነው? የሚሉ፣ ሐሰትን መልመድና ማላመድ ያቃታቸው፣ የምንኖረው ለማወቅ ነው ብለው ጆሮአቸውን የከፈቱ፣ እንደ ዘመኑ ሳይሆን እንደ ቃሉ ለመኖር የሚፈልጉ፣ በንጽጽር ሳይሆን እንደ ራሳቸው የሚኖሩ፣ ስለ እምነትና ስለ እውነት ጥቅማቸውን የተው፣ ራስ ወዳድነትን የካዱ፣ አፋቸው የልባቸውን አሳብ የሚያብራራላቸው፣ ከኋላ ጦር አስከትለው እንደ ይሁዳ መሳም የማይወዱ፣ የጥርስ ግብዣን እንደ ዘማዊና ዘማዊት የማይጋብዙ፣ እያንዳንዱ ቃላቸውን እንደ መሐላ የሚጠብቁ፣ የራሳቸውን ደግነት እየናቁ የሌሎችን በጎነት የሚያጎሉ፣ ከገንዘብ እስራት የተፈቱ፣ ቊሳቊስ መገልገያ እንጂ ጣኦት ያልሆነባቸው፣ ኑሮዬ ይበቃኛልን የተማሩ፣ ተረጋግተውና ተማምነው የሚኖሩ፣ እውነትን ለማዳፈን ጉቦ የማይሰጡ፣ ከሐሰት ጮማ የእውነትን ጥሬ የመረጡ፣ ቀን እስኪያልፍ ውሸት አሻጋሪ ነው የማይሉ እውነት ታብራ እያሉ በናፍቆት ያነባሉ፡፡
ዘመናችን ሌብነትን አልጠላም፣ የጠላው ትንንሽ ሌቦችን ነው። ሚሊየን የዘረፈውን ጎበዝ ጥብቆ የሰረቀውን ልክስክስ የሚል ነው፡፡ ዘመናችን ስለ በሽታ የሚጨነቅ ዝሙትን ግን የሚያበረታታ፣ ውበት አድናቂ የሚመስል ሕፃናትን ግን ለከንቱነት የሚገዛ፣ ሁሉም ሃይማኖተኛ የሆነ የሚመስልበት ሃይማኖቱ ግን ለሰላም አስተዋጽኦ ያላደረገበት፣ ብዙዎች ፍርድ አጥተው በየችሎቱ የሚንከራተቱበት፣ ማንም ኃላፊነትን ላለመውሰድ የሚጠነቀቅበት፣ ሕክምና ንግድ የሆነበት፣ መምህራን ክፉ አርአያ በመሆን የድፍረትን ኃጢአት ያነገሡበት፣ የሃይማኖት መሪዎች የዘመን ሎሌ የሆኑበት፣ ሰማይን ረስተው ምድር ላይ የቀሩበት፣ ብልሹዎች ስለ ብልሹ አመራር የውግዘት ቃል የሚያሰሙበት፣ እውነት ድራማ የሆነበት፣ ተግሣጽ ስድብ የሚባልበት፣ የተገሰጹበትን ቀን ስንሰደብ ውለናልና ግብዣ እናድርግ በማለት ተግሣጹ በመጠጥ ጎርፍ የሚወገድበት፣ የሚወዱትን ሰው እወድሃለሁ ለማለት የሚታፈርበት፣ የማይወዱትን እወድሃለሁ ለማለት የሚደፈርበት. . .  ይህ ሁሉ ተደርጎ እኛ ክፉ ነን ከማለት ዘመኑ ክፉ ነው የሚባልበት እንደሆነ እያየን ነው፡፡
እውነት የጨለመችው በወኅኒ ቤት ብቻ አይደለም፡፡ በትዳር ውስጥም እውነት ጨልማለች፡፡ ባልና ሚስት በእውነት አይግባቡም፡፡ የሚግባቡት በውሸትና በሽንገላ ነው፡፡ በሐሰት የተጠመቀ ትዳር፣ እውነትን አዳፍኖ ሰላምን የሚሻ ጋብቻ እየበዛ ነው፡፡ እውነት ለእኒያ ባልቴት ብቻ ሳይሆን ለብዙ ምእመናንም ተሸሽጋለች፡፡ እኔ ልክ ነኝ ለማለት እገሌ ተሳስቷል የሚሉ ምስኪኖች፣ እውነትና ሐሰትን ቀላቅለው የሚስተምሩ ሰባኪዎች ለሕዝባችን ዝናብ የሌላቸው ደመናዎች ናቸው፡፡ ፍትሕን አርግተው፣ የተበተኑትን ሰብስበው፣ ግፈኞችን ገስጸው ይለያያሉ ተብለው ተስፋ የሚደረጉ ትልልቅ ጉባዔዎች የሊቃነ መናብርቱን ደመወዝ ጨምረው የሚለያዩበት፣ ዛሬም በሬሳ ላይ ለመኖር የሚወስኑበት እንደሆነ እያስተዋልን ነው። እውነት መፈጸም እንኳ ባትችል ርእስ መሆን ለምን አልቻለችም?
ከተማው የተጣበበው ሊወገዙ የሚገባቸው አውጋዦች፣ ሃይማኖት ሳይኖራቸው የእገሌ ሃይማኖት ህፀፅ አለው ባዮች፣ ለማይኖሩበት እምነት የአዞ ዕንባ በሚያፈሱ ፖለቲከኞች ነው።። ተያይዞ መግባት እየቀረ ተጣጥሎ መግባት ድል እየሆነ፣ ሐሰተኛው ሐሰተኛ ስላልተባለ እውነተኛው እየተከሰሰ ያለበት ይህ ዘመን የሚያሳዝን፣ እኛ የምናሳዝን ነን፡፡ እስከ መቼ ለበላንበት እንጮሃለን? እስከ መቼ ለግፈኞች እናደላለን? የምንልበት ጊዜ ነው። አዎ እውነት ታብራ ለካ የእኒያ ሴት ብቻ ሳይሆን የመላው ዓለም ጸሎት ነው።
እውነት ስታበራ ተመሪው መሪ ይሆናል፣ እውነት ስታበራ አራሚው ታራሚ ይሆናል፣ እውነት ስታበራ መኰንኑ ተከሳሽ ይሆናል፣ እውነት ስታበራ አዋቂው ስፍራውን ይይዛል፣ እውነት ስታበራ አውጋዡ ይወገዛል፣ እውነት ስታበራ ባለጠጋው ድሀ ይሆናል፣ እውነት ስታበራ ጻድቅ የተባለው ይኰነናል፣ እውነት ስታበራ ምስጉኑ ይወቀሳል፣ እውነት ስታበራ አደባባዩ በወንጌል ሠራዊት ይወረሳል፣ እውነት ስታበራ ወንጌል ይገለጣል፣ እውነት ስታበራ እውነተኛ ፍቅር ይመጣል፡፡ አዎ እውነት ታብራ ብላችሁ ጸልዩ! የእውነትንም አንድ ሻማ በስፍራችሁ ለኩሱ። ሐሰተኞች በሐሰት ሳያፍሩ እኛ በእውነት ልናፍር አይገባንም። ሐሰትን ሰይጣን ያግዛታል፡፡ እውነትን ግን ክርስቶስ ይረዳታል። አምላካዊ ኃይል ከእኛ ጋር እንዲሆን ለእውነት እናድላ።
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ