“ኢየሱስም፦ እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ፤ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም ። እኔንስ ብታውቁኝ አባቴን ደግሞ ባወቃችሁ ነበር። ከአሁንም ጀምራችሁ ታውቁታላችሁ አይታችሁትማል አለው።” ዮሐ. 14 ፡ 6-7 ።
እውነት በዘመናውያን አስተሳሰብ መሬት የረገጠችና የተረጋገጠች አይደለችም ። እውነት የግል ምልከታና እሳቤ ተደርጋ ትቆጠራለች ። ያንተ እውነት ላንተ ፣ የእኔ እውነት ለእኔ በሚል ያለመነካካት ሥልጣኔ ውስጥ ላለ ትውልድ ፣ እውነት እንደ ሰዉ የምትለያይ ናት ። ዘመናዊነቱ እያየለ ሲመጣ አንተ ትክክል አይደለህም ብሎ ሌላውን በፍቅር መውቀስ ፣ በሥልጣን መገሠጽ እንዳይኖር ያደርጋል ፣ ስብከትም መታገዱ አይቀርም ። እውነት ነፋስ እንደ ተሞላ ፊኛ የምትንቀዋለል ፣ ከምድር የለቀቀች ፣ ብትወርድም የማትጠቅም ፣ አቅጣጫዋን በነፋሱ መንገድ የምትለዋውጥ አይደለችም ። የሰው ልጆች እውነትን በየዕለቱ እየፈለጉ ከእውነት ግን እየራቁ ይመጣሉ ። ፍርድ ቤት ደጃፍ ላይ እውነትን ይፈልጋሉ ። እውነተኛ ፍቅርን ሲሹ ዘመናቸውን የጨረሱ የሚመስላቸው ሰዎች አሉ ። እውነተኛ ኑሮ የሌላቸውን ሰባክያን ሲወቅሱ የሚታዩ አያሌ ናቸው ። በትልልቅ ቦታ ላይ ያሉ ሰዎች ሲዋሹ የሚሰማቸው ሰው ያፍርላቸዋል ። ትልቅነት ያለ እውነት ትንሽነት ነው ። ሽንገላን ብንወዳጅም ሸንጋዮችን ግን አንወድም ። ልቡ እና ቃሉ የተለያዩበት ሰው ወዳጅ እንዲሆነን አንፈልግም ። እኛ ጋ እየበሉ ጠላት ጋ የሚውጡ ሰዎችን መቀበል ይከብደናል ። ሃይማኖት ለዋጮችም ሥራቸው ያጸይፈናል ። ሰው እሞትለታለሁ ላለው ዓላማ መኖር እንዴት አቃተው? የሚል ትዝብት በውስጣችን ይጮኻል ።
ያለ እውነት ፣ ፍርድ ገዳይን አወድሳ ሟችን የምትኰንን ናት ። ያለ እውነት ፍቅር የላይ ጥርስ እንጂ የልብ ግብዣ የሌለባት ናት ። ያለ እውነት እውቀት ውስጣዊ መዝገብን ማጣበብ ነው ። ያለ እውነት ወዳጅነት ሲገናኙ መወዳደስ ሲለያዩ መቦጫጨቅ ነው ። ያለ እውነት አገር መውደድ ሰውዬውን እየገደሉ ተራራ ሸለቆውን ማምለክ ነው ። ያለ እውነት አገልግሎት ሰማይን እያዩ ምድር ላይ መቅረት ነው ። ያለ እውነት ንግግር የውኃ ማስተላለፊያ ቦይ መሆን ፣ ሌላውን ማራስ ለራስ ግን መድረቅ ነው ። ያለ እውነት ትዳር በድብብቆሽ ዕድሜን መፍጀት ነው ። እውነት ሁሉን ነገር እርግጥ ፣ የታመነ ፣ የሚኖርለት ፣ የሚሞትለት መሆኑን ማኅተም የምታሳርፍ ናት ። ያለ እውነት ዙፋን አይጸናም ። ያለ እውነትም የሰው መንገድ ፍጻሜ የለውም ። በዚህ ዘመን ሰዎች ውሸትን ከእውነት በላይ እየኖርዋት ነው ። ውሸታቸውን እውነት ለማሰኘት ሲጥሩ እውነት የማድረግ አቅም ግን አላገኙም ። ሁልጊዜ ሰውን ማታለል እንደማይቻል ፣ የብልጣብልጥነት መጨረሻ ሞኝነት መሆኑን እያየን ነው ። የእውነት አገርዋ ወዴት ነው ? የምንልበት ዘመን ላይ ነን ።
እውነትን በድርቅና ብቻ የያዙ እውነትን ምሕረት የለሽ ያስብሏታል ። እውነትን ያለ ፍቅር የያዙ እውነትን ሰይፍ ያሰኝዋታል ። እውነትን የግል ገንዘባቸው ያደረጉ የሚመስላቸው ሌላው ከሀዲ እነርሱ ብቻ አማኒ እንደሆኑ አድርገው በማሰብ ላይ ይገኛሉ ። እውነት ግን የእግዚአብሔር ገንዘብ ፣ የመለኮት ወኪል ናት ። የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሰው መሆን ከእውነት ጋር የተያያዘ ነው ። እርሱ በእውነት ሰው ሆነ እንጂ ሰው አልመሰለም ። ሞቱም አማናዊ እንጂ ተመስሎ ያለበት ተውኔት አይደለም ። በርግጥ ቤዛችን በመሆኑ ድነናል ። አማኑኤል እግዚአብሔር ከሥጋችን ሥጋ፣ ከነፍሳችን ነፍስ ነሥቶ ከእኛ ጋር ሆነ ማለት ነው ። አዳም የበደለው በሐሰት ተታሎ ነው ፣ በእውነተኛ ተዋሕዶ ክርስቶስ አድኖናል ። የክርስቶስ ሰው መሆን እውነትና ምሕረት የተስማሙበት ነው ። እውነት ነጻ ታወጣለች ። እውነቱ የተገኘላቸው ሰዎች ከፍርድ ቤት በነጻ ሲለቀቁ ይታያሉ ። እውነት ሰውን ከአእምሮ እስር ቤት ትፈታዋለች ። ዳኛ ቢፈርድበት እንኳ ውስጡ ነጻ ነህ የሚለው ነጻ ነው ። ዳኛ በነጻ ለቆት ውስጡ እስረኛ ነህ የሚለው እሱር ነው ። ሕሊናም በሐሰት የሚወቅስበት ጊዜ ይኖራል ። ከአእምሮ መታወክ ምክንያቶች አንዱ ሕሊና በሐሰት ሲወቅስ የሚሰማ ሕመም ነው ። ከሁሉ የሚበልጠው በአንድ ልጁ ሰው መሆን እኛን የተዛመደው ፣ በአንድ ልጁ ሞትም እኛን የታረቀው የእግዚአብሔር እውነት ነው ።
እውነቱ የት ነው ( ግራ ገባን የሚሉ ሰዎች አሉ ። እውነትን አለማወቅ ግራ ያጋባል ። ይልቁንም የደቦ ፍርድ ባለበት በዚህ ዘመን እውነቱ የት ነው የሚለው የአደባባይ ጥያቄ ነው ። እውነት ከኑሮአችን ሩቅ በሆኑ አገራትና ሰዎች ላይ ስትጓደል እንኳ የሕመም ስሜት ይሰማናል ። የነፍስ መከራዋም እውነት ሲጓደል ማየት ነው ።
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እውነት ሆኖ መጥቷል ። ግራ መጋባትን የሚያርቅ ፣ መደናገርን የሚያስቀር ፣ እስራትን የሚፈታ ፣ ፍርጃን የሚያነሣ የእውነት አዋጅ ሆኖ ተገልጧል ። ከመጻሕፍት የምትበልጠውን ወንጌል ፣ ከሃይማኖት የከበረችውን ክርስትና ሰጥቶናል ። የእኔ መጽሐፍ ይበልጣል ፣ የእኔ ክርስትና ይልቃል ብለን ሌላውን እንድናሳንስበት ግን አልሰጠንም ። የሰጠን ነገር ሁሉ ለመዳን የተሰጠን ነው ። የፍለጋ ሁሉ ማብቂያ እውነት ክርስቶስ ነው ። ዕርቃኑን ተሰቅሎ ያላፈረው እውነት ስለሆነ ነው ። ደግመው የሚናገሩት ፣ ጠፍተው የሚመለሱበት እውነት የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ። በዘመናት ሁሉ የነበሩ ፈላስፎች እውነት ምንድነው ? በማለት ፈልገዋል ፣ በዱር ገብተዋል ፣ መናኔ ንብረት ሆነዋል ። እውነት የጠቢባን ፣ የነገሥታት ፣ የባለጠጎች ጥልቅ ጥያቄ ናት ። ይህንን የነፍስ ሸለቆ የሞላው እውነት የሆነው ፣ በጲላጦስ ፊት የተከሰሰው ክርስቶስ ነው ። በችሎት አደባባይ እውነተኞች ሲከሰሱ ኖረዋል ፣ በቀራንዮ ግን ራሱ እውነት ተከስሶ ቆመ ። ለእውነት ስፍራ በሌላት ዓለም ክርስቲያንነትህን አበባ ይዞ የሚቀበለው የለም ።
ምስጋና ብርሃን ለምታወጣው እውነት ይሁን ! አሜን ።
ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 25 ቀን 2017 ዓ.ም.