መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ከቀደምህ ልከተልህ

የትምህርቱ ርዕስ | ከቀደምህ ልከተልህ

ከፊት የቀይ ባሕር ፣ ከኋላ የፈርዖን ሠራዊት ያስጨንቀኛል ፤ ብሄድ ገደሉ ፣ ብመለስ እሳቱ ያስፈራኛል ። ጋረድ ኢየሱስ ሆይ ከቀደምህ ልከተልህ ። የተዘጋጀልኝን ቀን ሳልዘጋጅ ተጋጥሜ መቋቋም አቅቶኛል ፤ ብችለው እንኳ “እንዴት?” የሚለው ጥያቄ አቅም ይነሣኛል ። ለመድረስ መራመድ ፣ ለማሸነፍ መዘርጋት የማያሻህ ጽኑ መለኮት ሆይ ከቀደምህ ልከተልህ !

የምኖረው ኑሮ የተማርኩትን ፣ ፈተናው ያሳየኸኝን ተአምር ያስረሳኛል ። ጎርፉ ሊጠርገኝ በሞትና በጭንገፋ ጀርባ ላይ ተጭኖ ይመጣብኛል ፤ ነፋሱ ሊነቅለኝ በወሬ ፈረስ ላይ ሁኖ ደረስሁ ይለኛል ፤ ወጀቡ ደስታዬን ሊያርቀው በከዳተኞች ላይ ሆኖ ይረብሸኛል ። በሚመስል ነገር ጠላት ያታልለኛል ፣ በማያድን ወሬ ጊዜዬን ይበላብኛል ። ላንተ ስኖር ብዙ ወጥመድ ይታየኛል ። አማኑኤል ሆይ ፣ ከቀደምህ ልከተልህ ! ለመማሬ የመጣው ለማማረር ሆነብኝ ፣ ለእምነት የሰጠኸኝ የብልጠት መሣሪያ ሆነኝ ፣ የጽድቁን ሥራ የውዳሴ ከንቱ ማትረፊያ አደረኩት ። አንተን ብቻ ስል ከራሴም ከሰውም እጣላለሁና ከቀደምህ ልከተልህ !

ሰው ሁሉ ሐሰተኛ ራሴ ግን ሐቀኛ መስሎ ይሰማኛል ። ኃይለኞች የሁልጊዜ ኃይለኛ መስለው ይታዩኛል ። የተመሠረተው “ቢፈርስስ?” የሚል ስጋት አቅሌን ያስተዋል ። የተለወጡ “ቢክዱስ?” እያልሁ ፍርሃት ይንጠኛል ። አባት ልጅ ሲሆን ፣ ልጅ አባት መሆኑ መሰል ፣ ለሁሉ ማሰብ ይዳዳኛል ። ሁሉን ትቶ በእምነት መከተል ፣ መስቀልን በደስታ መሸከም ለዚህ ሥጋዬ ይከብደዋልና አዶናይ ሆይ ከቀደምህ ልከተልህ!

ባሕረ አሳብ ውስጥ ሆኜ ዋኝቼ መዝለቅ አልቻልኩም ፣ አንዱን ስህተት በሌላ ስህተት ማረም አላረካኝም ፣ ብርሃንን ጠልቶ የውሸት ወዳጅነት አቅም አልሰጠኝም ። የሆኑ ነገሮችን በሚመስሉ ነገሮች መለወጥ ዕረፍት አልሆነኝም ። እንዳስተማርከኝ እውነት ፣ እንዳሳየኸኝ ፍቅር መኖር እሻለሁና ከቀደምህ ልከተልህ ! አንተ ቃልህን የማትለውጥ ወዳጅ ፣ አንተ ሰውዬውን ሠርተህ ሥራውን የምትሠራለት ውብ ዓለም ፣ አንተ ወደ ዓለም ሁሉ የላክህ የወንጌል ባላባት ፣ ርስተ ብዙ ነህና ከቀደምህልኝ ልከተልህ ! የናፈቀህ ሁሉ አሜን ይበል ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ተጻፈ ሰኔ 29 ቀን 2015 ዓ.ም

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም