መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ከዓለቱ ጋር መስማማት

የትምህርቱ ርዕስ | ከዓለቱ ጋር መስማማት

 

እንኳን ለብርሃነ መስቀሉ አደረሳችሁ!

ወንድሟ በአደጋ የሞተባት ሴት እንዲህ ብላ የልቅሶ ሙሾ አቀረበች ይባላል፡-

“እስቲ ልነሣና ሙሾ ላውጣለት ፣

ለዚህ ለወንድሜ ለቀረው ከዓለት ።”

የቅኔው ሰሙ ከዓለት ላይ ወድቆ መሞቱን ሲገልጥ ወርቁ ደግሞ ካለ እኅት ፣ ካለ ዘመድ ብቻውን ለቀረው ወንድም የኀዘን መግለጫ ነው ። ካለት ከዓለት ማለት ሲሆን ደግሞም ካለ እኅት ማለት ነው ። ዓለት ብንወድቅበትም ይሰብረናል ፣ ቢወድቅብንም ይሰብረናል ። ይህ ለጌታችን ምሳሌ ሁኗል ። ማቴ. 21፡44 ። ጌታችን ባለማመን ብንቃወመውም ፣ አላውቃችሁም ቢለንም ሁለቱም ጉዳት ነው ። ዛሬ ይህን ዓለት በማያምን ልብ ብንቃወመው የወደቅነው በዓለቱ ላይ ነውና ይሰብረናል ። ንስሐ ካልገባን ደግሞ በመጨረሻ ቀን ዓለቱ በፍርድ ይወድቅብናል ። የጌታችን የክርስቶስ ኢየሱስን ፍርድ ለየት የሚያደርገው ምስክር የማይጠራበት ፣ የእምነት የክህደት ቃል የማይጠየቅበት ፣ የውሳኔ ቀጠሮ የማይሰጥበት ፣ መረጃና ማስረጃ የማይሰበሰብበት ፣ ይግባኝ የማይባልበት ፣ ዘላለማዊ ቅጣት ያለበት ነው ። ይህ ዓለት ለሚያምኑት የሚከተላቸውና የሚያረካቸው የበረሃው ዓለት ነው  ። 1ቆ. 10 ፡ 1-5 ። 

መከተሉ አለመለየቱን ያመለክታል ። እርሱ አይለየንም ። እስከ መጨረሻው ድረስ በእኛ ተስፋ አይቆርጥም ። እርሱ ለደግነቱ ማለቂያ ፣ ለፍለጋው ማረፊያ የለውም ። በመጥራቱ የማይጸጸት ነው ። በፍለጋውም የማይደክም ነው ። እገሌ ልቡ ጠንካራ ነው እንዴት ያገኘዋል ብለን ብናስብ ለመንገዱ ፍለጋ የሌለው ነው ። የሁሉ ፈጣሪ ፣ ልብ አውቃ ነውና ማንን በምን ቋንቋ እንደሚያነጋግር ያውቅበታል ። የት ቦታ ሲመቱ አቤት እንደሚሉ ያውቃል ። እርሱ የሚከተል ዓለት ነው ። የሚመራው ብሩህ ደመና ፣ የሚከተለው ዓለት ነው ። የሚከተል ከኋላ ያለ ነው ። እግዚአብሔር ከፊት የሚመራ ፣ ከጀርባችን የሚጠብቀን ፣ ከቀኝ ከግራ ወዳጅ ሁኖ የሚከበን ነው ። ሕልም አይተነን ስናስፈታ ፈቺዎቹ “በጀርባዬ መጣብኝ ያልከው በጀርባ የሚመጣ ጠላት ነው እግዚአብሔር ያውጣህ” ይሉናል ። ጠላት ከጀርባ ይመጣል ። የጀርባ ጠላታችንን ብቻ ሳይሆን የጀርባ አካላችንን እንኳ አይተነው አናውቅምና ዓለቱ ክርስቶስ ሊከተለን ይገባል ። እስራኤልን የሚከተል ዓለት ነበረ ። የዓለት ግድግዳን የትኛውም ጦር አይበሳውም ። ጦርን ያጥፋል እንጂ በጦር አይበሳም ። የእኛ ከለላ እንዲህ ነው ፤ ደስ ያለው አሁን በልቡ ቆሞ ፣ በሕሊናው ተንበርክኮ ፣ በነፍስ ጩኸት እልል ይበል ። 

ያ የሚከተለው ዓለት ሕያው ዓለት ነው ። ያ ዓለት የሚያረካ ዓለት ነው ። ያ ዓለት በበትር ሲመቱት ያለ ሕጉ ምንጭ የሚያፈልቅ ነው ። ዓለቱ በትሩን መስበር ሲገባው በትሩ ዓለቱን እንዲሰብረው ፈቃድና ጊዜ አገኘ ። “ጊዜ የሰጠው ቅል ድንጋይ ይሰብራል” እንዲሉ ። ዓለት ክርስቶስም መስቀሉን መስበር ሲችል መስቀሉ እርሱን ሰቅሎ ለዓለም አሳየው ። ያልተሰቀለ ነገር አይታይምና ሁሉ አይቶት እንዲድን ተሰቀለ ። አርማና ሰንደቅ ነውና ፣ መኩሪያ አገራችን ፣ መመኪያ ንጉሣችን ሊሆን ተሰቀለ ። ይህን ዓለት ሊያምኑት ፣ ሊጠጉት ፣ ሊደበቁበት ይገባል ። ያ ሰው ግን ዓለቱ ላይ ወድቆበት ሞተ ። በክርስቶስ የማያመኑ የሚሞቱት ዓለቱ ላይ ስለሚፈጠፈጡ ነው ። እርሱ የሕይወት ምንጭ ነው ። ዓለት ብርታቱ በመስቀል ተመትቶ የሕይወት ውኃ ፈለቀልን ። ብዙ ዘመን የተከተለን ነው ። ስንሸሸው የተከተለን እርሱ ነው ። የሚከተለው ዓለት በበረሃው ዓለም ድፍረት ነው ። እኛን የሚነካን ከዚህ ዓለት ጋር የሚጋጭ ነው ። ሥልጣን ብርታት ኃይል እስከ ዛሬ ያልረታው የዘላለም ጽናት ነው ። የሚከተለው ዓለት የኋላ አጥር ፣ የኋላ እሸት ነው ። እርሱን የጠበቁ እነ አብርሃም የማታ በረከት ፣ የሠርክ መብራት አግኝተዋል ። ዓለቱን ሊድኑበት ሲገባ ወድቀውበት የሚሞቱ ብዙዎች ናቸው ። ሊለቀስላቸው ይገባል እንጂ ሊለቀስባቸው አይገባም ። 

በዓለት ላይ ወድቆ የሞተው ያ ሰው የሞተው ለአንድ ጉዳይ ሳይሆን ለብዙ ጉዳዮች ሞቷል ። የሚወዱትን አጥቷል ። የሚጠሉትም ሞቷልና አይጎዳንም ብለው ይቅር ብለውታል ። ሊያሙት የሚፈልጉም “ሙት አይወቀስ ፣ ድንጋይ አይነከስ” ብለው አልፈውታል ። በዓለቱ ላይ የወደቀው ያ ሰው እኅት ፣ ወንድም ፣ አባት ፣ እናት አጥቷል ። ዓለቱ ከሆነው ከክርስቶስ ጋር የሚጋጩም ብዙ መንፈሳዊ ዘመዶችን ያጣሉ ። ከቅዱሳን ጋር ባለ አገሮች መሆናቸው ያከትማል ። ጉዳታቸውን የትኛውም የኢንሹራንስ ተቋም ሊክሰው አይችልም ። ክርስቲያን ስንሆን ዘጠና ዘጠኝ ነገድ የሚሆኑ ቅዱሳን መላእክት ወዳጆቻችን ይሆናሉ ። ልብ አድርጉ መላእክት ኅብረት የሚያደርጉት ከአባት ከእናት ልጅ ጋር ፣ ዘር በመቋጠር አይደለም ። ቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤል ሥጋዊ የልደት ትስስር የላቸውም ። ፍቅራቸው ግን በምድር ላይ ካለ ከእናትና ከልጅ ፍቅር ይበልጣል ። የቅዱሳን መላእክት ፍቅር ልዩ ነው ። ንስሐ ስንገባ ታላቅ ደስታ የሚያደርጉት ስንወድቅ ታላቅ ኀዘን ስለተሰማቸውና ስለጸለዩልን ነው ። ሉቃ. 15፡7 ። ዓለቱ ላይ ወድቆ የሞተ ወይም ክርስቶስን ተቃውሞ መንፈሳዊ ሕይወትን ያጣ ሰው ይህን ሁሉ ዘመድ ይከስራል ። ከአዳም ጀምሮ እስከ ዕለተ ምጽአት ያለው የሰው ዘር አንድ ነገድ ነው ። መላእክት ዘጠና ዘጠኝ ነገድ ናቸው ። ይህን ሁሉ ወዳጅ ማግኘት ትልቅ ሀብት ነው ። ከአቤል ጀምሮ ድል የነሡ የቅዱሳን ኅብረትም ክርስቲያን ስንሆን እንዛመዳቸዋለን ። 

እስቲ ልነሣና ሙሾ ላውጣለት ፣

ለዚህ ለወንድሜ ለቀረው ከዓለት ፤

መስቀሉ በሚታወስበት በዚህ ቀን በመንፈሳዊ ነጻነትና ድል የሚያከብሩ ፣ ከዓለቱ ክርስቶስ ጋር በንስሐ የታረቁ ብቻ ናቸው ። መስቀል ቅርጹም ኅብረት ነው ። ወደ ላይና ወደ ጎን ነው ። ወደ ላይ ከእግዚአብሔር ጋር ወደ ጎን ከሰዎች ጋር መተሳሰር ነው ። ከዚህ ሕይወት ለጎደለው ወንድም አልቅሱለት ። የሞተ ይለቀስለታል እንጂ አይለቀስበትም ።

ታላቁን የክርስትና ኅብረት የምናገኘው ከዓለቱ ጋር ስንስማማ ነው ።

እንኳን ለብርሃነ መስቀሉ አደረሳችሁ ። ዛሬም መስቀሉ ተቀብሯልና እናውጣው ። መስቀል ሰላም ነው ። መስቀል የሰው ክብር ነው ። መስቀል ቀና ብሎ መሄድ ነው ። መስቀል መስማማት ነው ። መስቀል ጦርን ማረሻ ፣ ቀስትን መኮትኮቻ ያደረገ ነው ። ከመስቀሉን ብርሃን ያሳትፈን ።

የብርሃን ጠብታ 8 

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

መስከረም 15 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም