“በምድር ላይ ብቻህን ብትቀር እንኳ ከግፈኞች ጋር አትተባበር ።” ማኅተማ ጋንዲ
ውግዘት የምንለው ነገር አጥፊውን ሰው ከቤተ ክርስቲያን ፍቅር ፣ ከምእመናን ኅብረት በመለየት መቅጣት ነው ። እንደ ውሻ በማባረር ስሙን በማሳነስ ሳይሆን እንደ ሰው በማክበርና ጊዜ ሰጥቶ አሳቡን በመጠየቅ የሚፈጸም ውሳኔ ነው ። ያ ሰው የሚቀጣው በስድብና በነገሥታት ዱላ ሳይሆን ፍቅርንና ኅብረትን በማጣት ነው ። ጠፍቶ እንዲቀር ወይም አስወጥቶ በር መዝጋት ሳይሆን ውግዘት በፍቅርና በኅብረት ረሀብ ቀጥቶ ወደ ቤቱ እንዲመለስ ማድረግ ነው ። ቤተሰባዊ ቅጣት እንጂ ውግዘት የበቀል በትር አይደለም ። ያለ በቂ ምክንያት የሚያወግዝም ራሱ የተወገዘ ፣ የኣላውያን ወዳጅ ፣ የአረማውያን ጓደኛ ነው ። ክርስቶስ የሞተለትን ሰው በማባረሩ የክርስቶስን ደም የረገጠ ነው ። በቤተ ክርስቲያን ፍቅሩ በሽንገላ ፣ ኅብረቱ በአድማ ከተተካ ውግዘቱ በቂ ቅጣት መሆን አይችልም ። የሄደውም ለመመለስ አያስብም ። የተሻለ ክፉ እየፈለገ ፣ ራሱን እየደለለ ይኖራል ። ቢሆንም ውግዘት የሚፈራው መለየት ፣ መውጣት ፣ ብቻ መሆን ስላለው ነው ። እንደ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ፖፑ አይሳሳትም አንልም ፣ በማይሳሳቱ የሃይማኖት መሪዎች እየተመራን አይደለምና ኦርቶዶክሳዊነት ሁልጊዜ የመታረም ሕይወት ነው ። የተወገዘም ርጉም ፣ ያወገዘም ቡሩክ አይደለም ። ውግዘት በጥቅም ፣ በጥላቻ ፣ በጉቦ ፣ ለፖለቲካ በማደር ፣ በቡድን ስሜት ፣ በጎሠኝነት ሊከናወን ይችላል ። ውግዘት መክሮ ዘክሮ አልመለስ ያለውን ልጅ በፍቅር የመቅጣት ሥርዓት ነው ። ዓላማውም አስወጥቶ በር መቆለፍ ሳይሆን እስኪመለስ መጠበቅ ነው ። ታዲያ ውግዘትን በመፍራት እውነትን ሐሰት ማለት ፣ መገለልን በመስጋት ከእግዚአብሔር መለየት አይገባም ። ሰማይን በምድር ፣ ቤተ ክርስቲያንን በዕድር መለወጥ ስሌትን አለማወቅ ነው ። ግፈኞች በቅንዓት ተነሣሥተው ፣ ቅንዓታቸውን የሃይማኖት ካባ አልብሰው እናውግዝ እናጥፋ ቢሉን ከግፈኞች ጋር መተባበር አይገባንም ።
“ጊዜ የሰጠው ዘፈን እንቅርት ያፈርጣል” ይባላል ። ወቅታዊ ርእስ ፣ ስሜት እውነት እንዲመስል ያደረገው ወሬ ፣ ሁሉ የተስማማበት ጥበት ፣ እንደ መጨረሻው ቀን አድርጎ የሚነጋገርበት ክፋት ወደ እኔ ኑ ይላል ። ሌላው ግሎ መቀዝቀዝ ፣ ብዙኃኑ ተስማምቶ እኔ አልስማማም ማለት ለሥጋዊ ፍርሃት ከባድ ነው ። ልዩ ሰው ላለመሆን አዎ አዎ ማለት ፣ ላለመገለል ግፍን ማድነቅ ፣ ዕድሩን እቁቡን ላለማጣት ሕሊናን መሸጥ ፣ ብቸኛ ላለመሆን ትልቁን ጌታ መጣል አይገባም ። በማኅፀን ዓለም ብቻችንን ነበርን ፤ እናታችን ሳታየን ያየን የነበረው እግዚአብሔር ነው ። በመቃብርም ብቻችንን እንቀበራለን ። ለዘላለም ከእግዚአብሔር ጋር እንሆናለን ። ይህችን የመተላለፊያ ዓለም ፣ የመሻገሪያ ድልድይ ለማትረፍ ብለን ነፍሳችንን ማሰቃየት አይገባንም ። ማኅበረሰብ ነጻ ብሎን ሕሊና እስረኛ ከሚለን ፣ ሕሊና ነጻ ብሎን ማኅበረሰብ ቢያስረን ይሻላል ። ለመለየት ብለን አንድ ነገርን ማድረግ እብደት ነው ። ልዩ ሰው መሆን የታይታ ጥማት የሚወልደው ነው ። ልዩ ሰው መሆንን ስንመርጥ ልዩ መከራ ይገጥመናል ። ድሀን ሁሉም ሲረግጠው ፣ ብቸኛውን ሁሉም ሲያሳድደው እንቢ ብለን ከተገፋው ጋር መቆም ያስፈልጋል ። ይህ መገለልን ያስከትላል ። ሳይረዳን የራቀን ሰው የተረዳን ቀን ይመጣል ። ትልቁ ብቸኝነት ከሰው ሳይሆን ከእግዚአብሔር መራቅ ነው ።
ባሕልና ልማድ የሰው ልጆችን ረጅም ታሪክና ድካም የሚገልጥ ያልተጻፈ ግን የሚኖሩት መጽሐፍ ነው ። ባሕሉና ልማዱ ብዙ መልካም ነገር ያለው የብዙዎች ብቻ ሳይሆን የትውልዶች ስምምነት ነው ። ማኅበረሰቡን አስተሳስሮ ያቆመ በመሆኑ ባሕልና ልማድ መልካም ነው ። ሁሉም ባሕልና ልማድ ግን ጥሩ ነው ማለት አይቻልም ። ባሕልና ልማድ አንዱ ሲሽረው ሌላው ነጋሢ ደግሞ የሕዝብን ድጋፍ ለማግኘት ከፍ ያደርገዋል ። ባሕልና ልማድ እውነትንና የሰው ልጆች የደረሱበትን ተጨባጭ ሥልጣኔ የሚገፋ መሆን የለበትም ። ባሕልና ልማድ የሰው ልጆችን እኩልነትና ክብር የሚጋፋ መሆን የለበትም ። ባሕልና ልማድ ጤናንና የአካልን ደኅንነት የሚሽር መሆን የለበትም ። ባሪያና ጨዋ የሚል ባሕል ፣ አጋንንትን የሚያነግሥ ልማድ ፣ የሰውን ጤና የሚጎዳ ተግባር ፣ አንዱን ዝቅ የሚያደርግ ምሳሌም ሆነ ጥቅስ ሊወገዝ ይገባዋል ። ባሕልንና ልማድን ስንከተል የእግዚአብሔር ቃል ምን ይላል ማለት አለብን ፣ ዘመኑን የመጠነ እውቀትን የተላበሰ መሆኑን ማስተዋል ያስፈልገናል ። የሰውን ጤናና አካላዊ ክብር የሚጠብቅ መሆኑን መመርመር ያስፈልጋል ። ብቻዬን እቀራለሁ ብሎ በመስጋት አጉል ባሕልና ልማድን መከተል አይገባም ። ከአንድ በላይ ትዳር ልማድ ሆኗል ። ልማድ ስለሆነ ግን የሚከበር መሆን የለበትም ።
በምድር ላይ አንድ ዘር አለ ። እርሱም የአዳም ዘር ነው ። ሌላው ግለሰብ ፣ ቤተሰብ ፣ ጎሣ ፣ ነገድ እያለ የሚያድግ ስብስብ ነው ። ነገደ ካም በማለት አፍሪካንና እስያን ፣ ነገደ ሴም በማለት እስራኤልና ዐረብ ኢትዮጵያን ፣ ነገደ ያፌት በማለት አውሮፓን እንጠራለን ። ቅርንጫፉ ቢበዛም ግንዱ ግን አንድ ነው ። አንድ እግዚአብሔር ያበጀን ነን ። ሁለት አዳሞችን ያልፈጠረው የሰውን መገኛ ከአንድ ምንጭ ያደረገው ለአንድነታችን በማሰብ ነው ። መላእክት አንድ ጊዜ በብዛት ሲፈጠሩ ሰው ግን አንድ ሁኖ ተፈጥሮ በየጊዜው የሚባዛ ነው ። በተለምዶ ዘረኝነት የምንለው ጎሠኝነት የሰውን ልጅ ከትልቁ ቤተሰብ የሚያወጣ ፣ የሚኖርበትን ዓለም የሚያጠብ ነው ። የመጨረሻው ዘመን መገለጫ ጎሠኝነት ነው ። የሰይጣን ቀጥተኛ ወኪል የሆነው አውሬው ጎሠኝነትን ያራምዳል ። “በነገድና በወገንም በቋንቋም በሕዝብም ሁሉ ላይ ሥልጣን ተሰጠው” ይላል ። ራእ. 13 ፡ 7 ። መለያየትን ያመጣል እንደ ማለት ነው ። ጌታችንም፡- “ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ይነሣልና” ብሏል ። ማቴ. 24 ፡ 7 ። ሕዝብ በሕዝብ ላይ የሚነሣው በጎሠኝነት ስሜት ነው ። የሕዝብ ለሕዝብ እልቂት ያድግና መንግሥት ለመንግሥት ደግሞ ይዋጋል ። የትንቢት መፈጸሚያ እየሆነ ያለ ሰው ካለ ፣ የአውሬ ተከታይ ሊባል የሚገባው ጎሠኛ ወይም ዘረኛ ሰው ነው ። ከቤተሰብ ካገር ልጅ ላለመገለል ብሎ ሃይማኖቱን ሳይቀር ችላ ብሎ ጎሠኛ የሆነ ብዙ ሰው አለ ። ትላንት ክርስቶስን በሰበከበት አፉ አሁን ስለ መንደር ሲያወራ ሐፍረት የማይዘው አያሌ ነው ። ብቻዬን እቀራለሁ ብሎ ዘረኛ የሆነ ሰው አለ ። ስለዚህም ግፍን በደልን ያደንቃል ። ብቻችንን ብንቀር እንኳ ዘረኛ መሆንን መጠየፍ ይገባናል ።
ብቻቸውን ላለመቅረት የሚዘርፉ ፣ በመጠጥ የሚናውዙ ፣ በጊዜ ወደ ቤት ለመግባት ፈልገው የሥራ ዕድል አላገኝም እያሉ መጠጥ ቤት ከባለጠጎች ጋር የሚያመሹ ፣ ኃጢአትን የሚያደንቁ ፣ እግዚአብሔር ለጠላው ነገር እውቅና የሚሰጡ ፣ የእነርሱ ጎሣ ያደረገውን ግፍ ጽድቅ ነው ብለው የሚያሞካሹ አያሌ ናቸው ። የሕንዱ የነጻነት ታጋይና መሪ ማኅተማ ጋንዲ ያሉትን መከለስ ይገባል፡- “በምድር ላይ ብቻህን ብትቀር እንኳ ከግፈኞች ጋር አትተባበር ።”
የብርሃን ጠብታ 28
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ኅዳር 28 ቀን 2014 ዓ.ም.