የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ከጣራዬ በታች አትግባ

ከክርስቶስ ልደት በፊት በ59 ዓመት በጁልየስ ቄሣር ዘመን የተጀመረው ጋዜጣ በጣልያንኛ ስሙ “ጋዜታ” የ90 ዓመት ዕድሜውን ለማክበር ጠብ እርግፍ የሚልበት ሰሞን ነው ። በሰሌዳ ላይ ተለጥፎ ሕዝብ የሚያነበው በኩሩ ጋዜጣ “አክታ ዲዮረና” በልዩ እትሙ የሮማን መንግሥትና ሕዝብ ለማስደሰት  እየጣረ ነው ። “መንገዶች ሁሉ ወደ ሮም ያመራሉ” የሚለው አባባልም በብርቱ እየተነገረ ነው ። ሮማ ያልገዛችው ግዛት አልነበረምና ። ከሮም እስከ ኢንግላንድ ፣ ከኢየሩሳሌም እስከ ሩቅ ምሥራቅ ፣ ደግሞም እስከ ሰሜን አፍሪካ በክንዷ ያላንበረከከችው አይገኝም ነበር ። በኩሩ ጋዜጣም የቅኝ ግዛት ዜናዎችን ፣ አስገራሚ ክስተቶችን እየሰበሰበ ነው ። ታላቁ እስክንድር ባለመጽሐፍ የሆነውን ፣ አደረጃጀቱ የሰለጠነውን የአይሁድን እምነትና ክህነታዊ ሥርዓት እውቅና ሰጥቶት ስለነበር ከእርሱ በኋላ የመጣው የሮማ አገዛዝም ተቀብሎት ነበር ። ከምድረ እስራኤልም ልዩ ዜና ይጠበቅ ነበር፤ አንጾኪያ ፣ ቁስጥንጥንያ የሮማ መንግሥት ትልቅ መናገሻዎች ቢሆኑም ኢየሩሳሌም ደግሞ የበለጠ ታሪካዊ ግዛቱ ናት ። ይልቁንም በእስራኤል የተነሣው መሢሑ ክርስቶስ ዝናው ወደ ሮም ተሰምቶ በጥንቃቄ ይመረመር ነበር ። ሰላማዊነቱ ስለ ታወቀም የሮማ መንግሥት በቸልታ አልፎታል ። ከሮማ እውቅ ባለሥልጣናትም የእጁን ተአምራት የቀመሱ አሉ የሚለው ዜና በሮም ተሰምቶ ነበርና የመቶ አለቃውን ወደ ሮም መምጣት ጋዜጠኞች ሁሉ በጉጉት ይጠብቃሉ ።

የመቶ አለቃው ከረጅም ጉዞ በኋላ በሮም ወዳለው ቤቱ ደረሰ ። ከወትሮ በተለየ ብዙ የወሬ አነፍናፊዎች ይጠብቁታል ። የጋዜጣው ዕድሜ ዘጠና ሞልቷልና ለዚያ ልዩ እትም የእርሱ ቃለ ምልልስ በጣም ማራኪ ገጽ ያደርገው ነበር ። ይልቁንም በምድረ እስራኤል ያለ ሐኪም ቤት ይፈውስ ፣ ያለ ሆቴል ይመግብ ፣ ያለ ማደሪያ ብዙዎችን ያስከትል ስለነበረው ስለ ክርስቶስ የሚያውቀውን ምስክርነት እንዲሰጥ ይጠበቃል ።
የመቶ አለቃውም ብላቴናውን እንዴት እንደ ፈወሰለት ዜናው ሮም ድረስ በመሰማቱ ደስ ብሎታል ። ቅዱስ ማቴዎስን አግኝቶ የተራራው ስብከት እንደ ተፈጸመ በስምንተኛው ምዕራፍ ላይ ጻፍልኝ ብሎታል ። ቅዱስ ሉቃስንም አግኝቶ ሰባት ቊጥር የፍጹምነት ምልክት ናትና በሰባተኛው ምዕራፍ ላይ ዘግብልኝ ብሎታል ። አሁን ደግሞ በሮማ ጋዜጣ ላይ ዜናው የመውጣቱን ነገር ሲያስበው ልቡ በደስታ ተሞላ ። የክርስቶስ ተአምር አይሸሸግምና ። ጋዜጠኞቹም አዋከቡት ። “አንተና ክርስቶስን ምን አገናኛችሁ ?” በማለት በጫጫታ ውስጥ ጠየቁት ። “ያገናኘን ጣር ነው” ብሎ በጫጫታ ውስጥ መለሰ ። በልቡም፡- “ካልተወጋ ሰው መቼ ክርስቶስን ያመልካል” አለ ። የሮማ ቋንቋ ድምፁ ኃይል አለውና ሴቷ ጋዜጠኛ “እርሱን የለመንከው ስለ ባሪያህ ነው ይባላል ፣ ይህ የሮማን መንግሥት ክብር አይነካም ወይ ?” ብላ በጩኸት ጠየቀችው ። “አዎ ክብራችን ካልተነካ ክብሩን ማወቅ አይቻልም ። በሁለት ወገን ክብራችን ተነክቷል ። የመቶ አለቃው ከአንድ ምስኪን መምህር ዘንድ ደጅ በመጥናቱ ፤ ሁለተኛ ባሪያ እንደ ዕቃ በሚሸጥበት ግዛት ስለ ባሪያ በመማለዱ ክብሩ ተነክቷል ። ክብር ከሰማይና ከምድር ትርጉሙ ልዩ ነው ። ምድር ክብር የምትለውና ሰማይ ክብር የሚለው ይለያያል” በማለት መለሰ ። በጫጫታ ውስጥ ያለው ቃለ መጠይቅ ማስታወሻ ላይ ለማስፈር አላመች አለ ። በዚህ ጊዜ የተመረጡ “የአክታ ዲዮረና” ጋዜጠኞች ፀጥታ ባለው አጸድ ውስጥ የመቶ አለቃውን እንዲያነጋግሩ ተወሰነና ብዙዎች ተበትነው ሁለቱ ጋዜጠኞች ከመቶ አለቃውን ጋር ተቀመጡ ።
“በእስራኤል የተነሣውን ክርስቶስን ታውቀዋለህ?” በማለት አንደኛው ጋዜጠኛ ጠየቀ ። የመቶ አለቃው ግን በግርምት ፈገግ አለ ። ትንሽ ጥያቄም መስሎ ተሰማው ። “ክርስቶስ ያውቀናል እንጂ ገና አናውቀውም ፣ ባወቅነውም ቊጥር አለመታወቁ እየሰፋ ይሄዳል ፤ እርሱ ስለ እኛ ባለው እውቀት እናርፋለን እንጂ እኛ እርሱን በማወቃችን አንጠነቅቀውም” አለ ። “በመጀመሪያ እርሱን ባገኘኸው ጊዜ ምን ተሰማህ?” አለችው ሴቷ ጋዜጠኛ ። እርሱም፡- “ከክርስቶስ ጋር መገናኘት ከብርሃን ጋር እንደ መገናኘት ነው ። ብርሃን በጠባዩ ራቁትነትን ያሳያል እንጂ አይሸፍንም ። እርሱ ግን የሚሸፍን ብርሃን ነው ። ብርሃን የለበሰ ፣ በሰማይም በምድርም ያለ እርሱ ነው” በማለት መለሰ ። ሁለቱም ጋዜጠኞች ቃለ ምልልሱ አላረካ አላቸው ። መቶ አለቃው እንዲሁ ቢተርከው ተመኙ ። “ራስህን በክርስቶስ እንዴት አገኘኸው?” በማለት ጠየቁት ። እርሱም፡- “እንኳን እናቴ ሙታብኝ እንዲሁም አልቅስ አልቅስ ይለኛል” የሚለውን ብሂል ጠቅሶ የባለ ዝናውን ዝና መተርተር ጀመረ ።
የሮማ መንግሥት መቶ አለቃነት እንዲህ በቀላሉ የማይገኝ ነው ። ከአዝማደ መንግሥቱ አንዷን በማግባት ደጃዝማችም ፣ ፊታውራሪም መባል ይቻላል ። መቶ አለቃነት ግን ሙያና የጥረት ውጤት ነው ። ውትድርናዬን ሳስበው አመጋገቤ ፣ የሰውነት እንቅስቃሴዬ ፣ ታዛዥነቴ ፣ ትዕግሥቴ ሁሉ ተጠቃለው ያሉበት ነው ። ያለ ዓላማ ከመኖር በዓላማ መሞትን የሚያከብር ነውና ወታደርነቴን እወደዋለሁ ። ስሙም ወጥቶ አደር ማለት ነው ። በከተማ የሚያውደለድል ፣ ሀብታምና ቆንጆ ሴት የሚጠብቅ ሳይሆን ወጥቶ የሚያድር በመሆኔ ስሙም ግብሩም ኩራቴ ነው ። ለአገሬ ለመንግሥቴ ሕይወቴን የምሰጥ በመሆኔ ታላቅ ክብር ይሰማኛል ። የምኖረውም ሕይወት ለመስጠት ሳይሆን ወታደር የሆንኩት ገና ከጅምሩ ሕይወቴን ሰጥቼ ነው ። የተሠዋ ሕይወት አይፈራም ። የሞተ ሞትን አይሰጋም ። ንጽሕና ፣ ንቃት ፣ ማልዶ መውጣት ፣ ለሰላም ዋጋ መክፈል የወታደርነት መለያ ነው ። ተመልከት ዓላማህን ፣ ተከተል አለቃህን የሚለውን መመሪያ እወደዋለሁ ። በዓላማዬ መሠረት አለቃዬን የምከተል ነኝ ። እንዲህ ዓይነት ሥነ ሥርዓት ባይኖር ኑሮ ዓለም የጨምላቃ አስተዳደግ መድረክ ትሆን ነበር ። እናንተ በከተማ እንድትንጎማለሉ ወታደር በበረሃ ፣ በድንበር መቀመጥ አለበት ። ቤዛ ባይኖር ሕይወት አይቀጥልም ነበር ። ጨዋ ለመሆን አዳሪ ትምህርት ቤት ወይም ወታደርነት መልካም ነው እያሉ የሮማ ሰዎች ሲናገሩ ትሰማላችሁ ። እኔም ሰው ሁሉ ወታደር ቢሆን እመኛለሁ ። ብቻ ሰው ሁሉ ወታደር ባይሆንም ወታደር ሁሉ ግን ሰው ነው ።
የመቶ አለቃው ከመቀመጫው ብድግ አለ ። ጋዜጠኞቹም ከተመስጦ ሰመመን ነቁና ቆሙ ፤ እርሱ ግን፡- “እናንተ ተቀመጡ ፣ እኔ ግን ቆሜ የእርሱን ዝና ልተርክ” በማለት ስለ ክርስቶስ ለመናገር ፈለገ ። መሐል ባሕር ላይ እንደ ለቀቁት ከየት ተነሥቶ ወዴት እንደሚሄድ ተጨነቀ ። እንደ ምንም ብሎ ትረካውን ጀመረ ።
“ሰዎች ሁለት ደግነት አለህ ይሉኛል ። የመጀመሪያው ባሪያህን እንደ ልጅህ ማየትህ ሲሆን ሁለተኛው ሰዎችን የምትወድና ካንተ በሚፈልጉት ነገር ቀድመህ መገኘትህ ነው ይሉኛል ። ሁለተኛውን አሳብ የሚሰነዝሩት አይሁድ ናቸው ። ምኩራብ ሠርቼላቸዋለሁ ። እኔ ለደስታዬ የሠራሁትን እነርሱ የዝናዬ ስም መጥሪያ አድርገውታል ። ለዝና የሠሩት ለደስታ አይሆንም ፣ ለደስታ የሠሩት ግን ለዝና ይሆናል ። ሁለት መቅደስ እንደ ሠራሁ ይሰማኛል ። አንደኛው የአይሁድ ምኩራብ ነው ። እርሱ ሰው ተሰብስቦ የእስራኤልን እምላክ የሚያመልክበት ነው ። ሁለተኛው መቅደስ ግን ራሱ እግዚአብሔር የሚያድርበት የሰው ልጅ ነው ። ባሪያዬን ያገኘሁት በሶሪያ ውጊያ ምርኮኛ ሁኖ ነው ። ምርኮኛ ሁሉ ወደ ሮማ መንግሥት ገብቶ ከዚያም በመሸጥ መንግሥቱ ያወጣው የጦርነት ወጪ ይካካሳል ። እኔም የማረክሁትን ገዝቼ ባሪያዬ አደረግሁት ። በሁለት ዋጋ የእኔ ሆነ ። ከሁሉ የሚያስደስተኝ ግን በፍቅር እንደገና ልጄ አደረግሁት ። ባሮች ሁሉ ሕመማቸው ጌቶች ናቸው ። ይህ ባሪያ ግን አባት ሲያገኝ ታማሚ ሆነ ። ዓለም በአንደኛው ጎኑ ቀዳዳ ነው ። ሕመሙ ያዝ ለቀቅ እያለ ቢዘልቅም አሁን ግን እየበረታ መጣ ። በቅፍርናሆምም ታላላቅ ተአምራትን መሢሑ እንደሚደርግ ብሰማም በየትኛው ማንነቴ በፊቱ እቆማለሁ እያልሁ አመነታ ነበር ። አንድ ቀን የብላቴናዬ ሕመም ጠንቶበት መላው ቤተሰብ ከእኔ ጋር ሲጨነቅ ድንገት ብድግ ብዬ ከቤቴ ወጣሁ ። በጎዳናውም የአይሁድ ረቢዎችም ከምኩራብ ወጥተው ለጉብኝት ወደ ምእመናን ቤት ሲሄዱ አየሁ ።እነርሱም ምንም እንኳ አይሁድ ካልሆነ ጋር በገደብ የሚቀራረቡ ቢሆኑም እኔ ግን ስለምወዳቸው ይወዱኝ ነበር ። ሮማዊነቴን ዘንግተው አይሁዳዊ እመስላቸው ነበር ። ፍቅር አገርና ጎሣን ያስረሳል ። ፍቅር ግዛቱ እግዚአብሔር በሚገዛበት ሁሉ ነውና ጥበት አይስማማውም ። ምን ሆነሃል? የመቶ አለቃ ሲሉኝ እኔም ከእንቅልፍ እንደ መንቃት ብዬ ደህና ነኝ አልኳቸው ። እነርሱም ወዲያው ገባቸው ። ከብዙ ሰው ጋር በመኖራቸው የሥነ ልቡና አዋቂ ሁነዋል ። ብላቴናህ ሕመሙ ጠናበት ? አሉኝ ። እኔም አዎ አልኳቸው ። መቼም ስለ ወዳጅ እሬት ይላሳል ። እኛ ባናምንበትም ፣ ወንበራችንን ሊፈነቅል የመጣ ቢመስለንም ያ ኢየሱስ የተባለው እንዲፈውስልህ እስቲ እንጠይቀው ሲሉኝ እባካችሁ ብዬ መሬት ላይ ወደኩኝ ። በዚያ ቀን አንድ ለምጻምን ፈውሶ የመንደሩ ሰው ሁሉ ግብዣ አድርጎለት በቅፍርናሆም ነበረ ።
የምኩራብ አለቆችን ከፊት አስቀድሜ እኔ ከኋላ ራቅ ብዬ ወደ መሢሑ ሄድሁ ። ‘ይህን ልታደርግለት ይገባዋል ፣ ብላቴናው ታሞበታል ። ሕዝባችንን ይወዳል ፣ ምኩራብም ሠርቶልናል’ አሉት ። ክርስቶስም ‘ልክ ናችሁ ፖለቲካውን ለማርጋት ሕዝቡን ሳይወድ ምኩራብ የሚሠራ አለ’ አላቸው ። እነርሱም በደመ ነፍሳቸው እውነት መናገራቸውንና እርሱም የሰማቸው መሆኑን አስተዋሉ ። ክርስቶስም ቀጠለ፡- ‘ፍቅር ያለውም ምኩራብ መሥራትን አይተውም’ በማለት ፍቅር አካል እንዳለው ተናገረ ። ቃሎቹ እያስገመገሙ ወደ ልቤ ይመጡ ነበር ። እርሱ ግን እነርሱን አልፎ ወደ እኔ መጣ ። እኔም ችግር አደባባይ ያውላልና ፣ ችግር ክብርን ያስጥላልና መለፍለፍ ጀመርሁ ። ‘ጌታ ሆይ ብላቴናዬ ሽባ ሆኖ እጅግ እየተሣቀየ በቤት ተኝቶአል’ ብዬ ለመንሁት ። ‘ባሪያህን ልጄ በማለትህ የፍቅር ሰው ነህ ። ባሪያና ጌታ የሚለውን ቃል የፈጠረው የሰው ዓመፀኛነት ነው ። እግዚአብሔር ሰውን የፈጠረው እኩል አድርጎ ነው ። በአያቱ ባለጠጋ ያልነበረ ድሀ ፣ በአያቱ ድሀ ያልነበረ ሀብታም የለም ። ቦታ መለዋወጥ ሲመጣ አንተ ባሪያ እርሱ ጌታ ሊሆን ይችላል’ አለኝ ።”
ሁለቱም ጋዜጠኞች በመቶ አለቃው የሚነገረውን የክርስቶስን ቃሎች ለመስማት ድንገት ብድግ ብለው ቆሙ፡- ‘መሢሑ ሥጋዊ አካልም ፈዋሽ ብቻ ሳይሆን የዛጉ ልቦችን አዳሽ ነው’ አሉ ። በመቀጠል፡- ‘ለባሪያህ ስለ ነበረህ ፍቅር ካደነቀህ ለጌትነትና ለቅምጥል ኑሮ የመጣ አይደለም’ አሉ ። እርሱም የጀመረውን አሳብ ሳይረሳ ለመቀጠል አንገቱን አወዛውዞ የዚያን ቀን ትርክት መተንተን ቀጠለ፡-
ይቀጥላል 
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ