የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ወንዶች ጸልዩ

 “እንግዲህ ወንዶች በስፍራ ሁሉ አለ ቍጣና አለ ክፉ አሳብ የተቀደሱትን እጆች እያነሡ እንዲጸልዩ እፈቅዳለሁ ።” 1ጢሞ. 2፡8
የአሜሪካው ፕሬዝዳንት የነበሩት ቶማስ ጃፈርሰን፡- “ቊጣዬን ለማብረድ አንድ ሁለት ብዬ ካልቆጠርሁ በሕይወቴ የሚያጸጽተኝን ነገር አደርጋለሁ ብዬ እፈራለሁ” ብለዋል ። ቶማስ ጃፈርሰን ሲናደዱ ከአንድ እስከ አሥር ይቆጥሩ ነበር ። በጣም ሲናደዱ ደግሞ ከአንድ እስከ መቶ ይቆጥሩ ነበር ። በጣም ሲናደዱ መቊጠር እስኪደክማቸው ድረስ ይቆጥሩ ነበር ።

ዓለምን የገዙ ሰዎች በቊጣ ምክንያት ራሳቸውን መግዛት አቅቷቸው በታላቅ ጸጸት ውስጥ ወድቀዋል ። በወተት ላይ ያረፈች ትንሽ ነቁጥ ጎልታ እንደምትታይ በብዙ ትልልቅ ሥራዎቻችን ቊጣ ጎልታ ትታያለች ። ልፋታችንን ሁሉ ከንቱ ታደርገዋለች ። ሰዎች ስለ ብዙ ፍቅራችን ጥቂት ከመናገር ይልቅ ስለ ትንሽ ቊጣችን ብዙ ያወራሉ ። ቊጣ ጊዜያዊ ስሜት ሲሆን እየቆየ ሲመጣ ቂም ፣ እየከረመ ሲመጣ በቀል ይሆናል ። ቊጣ ትንሽ ዘወር ካልን የሚበርድ ነው ። ከአንድ እስከ አሥር ለመቊጠር ከደፈርን ቊጣ ይበናል ። ስሜታችን እያተኮሰ ፣ ውስጣችን እየጋለ ከመጣ ዘወር ማለት፤ ቊጣችንን ልንገልጽባቸው የምንችልባቸውን ስልኮቻችን ፣ ራስ መጠበቂያዎቻችን አብዝተን መራቅ መልካም ነው ። ነፋስ ነክቶን ስንመለስ ሌላ ሰው እንሆናለን ። “እልፍ ሲሉ እልፍ ይገኛል” እንዲሉ ። ቊጣ እንዲያናግረን ስንፈቅድ መደምደሚያው እኛን ነፍሰ ገዳይ ማድረግ ነው ። ዘወር ስንል ደግሞ ብን የሚል ከንቱ ነገር ነው ። በተቆጡ ሰዎች ፊትም መፋጠጥ ተገቢ አይደለም ። ሌላውንም ከስህተት መጠበቅ አንዱ ቅድስና ነው ። ሌላውን እያረከሱ ፣ ሌላውን እያበሳጩ እኔ ተቀድሻለሁ ማለት ሐሰት ነው ። በቊጣ ላይ ላለ ሰው እግዚአብሔር ይቅር ይበልህ ማለት እንኳ የበለጠ ማቀጣጠል ነው ። ሰዎችን ከማብረድ የሚናደዱበትን ነገር አለማድረግ የተሻለ ነው ። ቊጣ ለአሁን ጀግና ለዘለቄታው ሰባራ ሰዎች ያደርገናል ።
የወንዶች ነገር ሊታሰብበት ይገባል ። የሴት ማኅበራት አሉ ። የወንዶች ማኅበራት ግን ብዙ የሉም ። ወንዶች ራሳቸውን ማየት ያስፈልጋቸዋል ። የዓለማችን የሚበዙት መሪዎች ወንዶች ናቸው ። ዓለም ግን የጦርነት ውድማ ከመሆን ፣ በደም አባላ ከመመታት አርፋ አታውቅም ። በወኅኒ ቤት ከሴቶች ይልቅ ወንዶች እስረኞች ናቸው ። በታላላቅ የጭካኔ ተግባራት የተሰማሩ ፣ እንዲሁም ሌብነትን ሥራቸው ያደረጉ የሚበዙ ወንዶች ናቸው ። ዓለሙ የወንዶች ብቻ እስኪመስል ጀማሪም ፈጻሚም እየሆኑ ያሉ ወንዶች ናቸው ፤ በስህተት የማይማር ፣ ታሪክን የሚደግም የወንዶቹ ዓለም ነው ። ወንዶች እርስ በርሳቸው የሚነጋገሩበት ፣ ሐቁን የሚያወሩበት ፣ በኪሳቸው ሳይሆን በአእምሮአቸው የሚያስቡበት መድረክ ያስፈልጋል ። ብዙ ወንዶች ከብስለት የራቁ ናቸው ። ሐዋርያው ወንዶችን አድራሻ አድርጎ መናገሩ በእውነት ተገቢ ነው ።
“እንግዲህ ወንዶች በስፍራ ሁሉ አለ ቍጣና አለ ክፉ አሳብ የተቀደሱትን እጆች እያነሡ እንዲጸልዩ እፈቅዳለሁ ።” 1ጢሞ. 2፡8
በስፍራው ሁሉ ማለቱ ድንቅ ነው ። ጸሎት በሁሉ ጊዜና በሁሉ ቦታ ነው ። የማይጸለይበት ጊዜና ቦታ የለም ። በደሳሳ ጎጆ ብቻ ሳይሆን ባማሩ ቤተ መንግሥቶችም ጸሎት አስፈላጊ ነው ። በአገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን በውጭ አገርም ጸሎት አስፈላጊ ነው ። በቅጥረ ቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይሆን በቤታችንም ጸሎት ወሳኝ ነው ። በሰላም ጊዜ ጸሎት ፣ በክፉ ጊዜ ቡጢ ማንሣት የብዙ ወንዶች መገለጫ ነው ። ወንዶች በእግዚአብሔርና በጡንቻቸው ያምናሉ ። በእግዚአብሔር ብቻ አምነው ሊጸልዩ ይገባል ። ልብ በሉ በስፍራው ሁሉ ። አንዳንድ አገልጋዮች በመድረክ እኛ ባለ ጥቁር ቀበቶ ነን ብለው ሲናገሩ ሰምተናል ። ድሮ እገሌ የተባሉ ብርቱ አስማት አላቸው ሲባሉ ይፈሩ ነበር ። አሁን ደግሞ ከእግዚአብሔር ይልቅ በእርግጫ የሚኮሩ እያፈራን ነው ። በስፍራው ሁሉ ማለት በሰላም ለመጣው ቡራኬ ፣ በነገር ለመጣው አበርክኬ እቀጣለሁ የሚል ስልት ሊኖር አይገባም ማለት ነው ። በእውነት የራሳቸው የገራፊ ቡድን ስላላቸው አገልጋዮች ስንሰማ ይህን የሐዋርያውን ምክር አላነበብነውም ወይ ? ያሰኛል ። ክርስቶስ ሕይወቴ ነው የሚሉ ለሰማዕትነትም ዝግጁ ናቸው ፣ የማይጠፋ ብርሃን ከክርስቶስ አግኝተዋልና ። በአደባባይ “አገልግሎት ሕይወቴ ነው” የሚሉ ሰዎች ውስጣዊ ንግግራቸው፡- “በሕይወቴ የመጣውን በሕይወቱ እመጣበታለሁ” የሚል ነው ። ክርስቶስ ብቻ ሕይወት ካልሆነልን ከቊጣና ከክፉ አሳብ አንድንም ።
“አለ ቍጣና አለ ክፉ አሳብ” ይላል ። ቊጣ የመጸለይ አቅማችንን ይጋፋል ።መጸለይም ከቊጣ ያድናል ። ቊጣ እኔ አስተካክለዋለው ማለት ነው ። መጸለይ እግዚአብሔር ያበጀዋል ማለት ነው ። “አንተው አብጀው ፣ አስቤም አልፈጀው” የሚባለው ለዚህ ነው ። ክፉ አሳብ መጠራጠር ነው ። መጠራጠር በአሳብ ማዕበል ያንገላታል ። እርምጃ እንዳይወስዱ እርግጠኛ አይደለም ። አርፈው እንዳይተኙ ልብ ተከፍሏል ። መጠራጠር አጉል ነዋሪ ያደርጋል ። መጸለይ ግን ራስንና ጉዳይን ለእግዚአብሔር አሳልፎ መስጠት ነው ። ጸሎት ሰላም ይሰጣል ።
“የተቀደሱትን እጆች እያነሡ እንዲጸልዩ እፈቅዳለሁ ።” ለብዙ ዘመናት ግራ እጃችንን እያወጣን እናሸንፋለን ብለን ፎክረናል ። በግራ እጃችን ስንፎክር ኑረን ይኸው ግራ ገብቶናል ። እጆች በሁለት ነገር ይነሣሉ ። በድል ስሜትና በመማረክ እውነት ነው ። አሸንፋለሁ ወይም እናሸንፋለን የሚል እጁን ያነሣል ። ተማርኬአለሁ የሚልም እጁን ያነሣል ። እጆች እናሸንፋለን ብለው ሲነሡ ከመቀደስ መርከስ ይጀምራሉ ። እጆች ዕፀ በለስን ቆረጡ ፣ እጆች አቤልን በድንጋይ ቀጥቅጠው ገደሉ ። እጆች በክፉ አሳብና በቊጣ ሲነሡ የሚያደርሱት ጥፋት ታላቅ ነው ። እጆች ለጸሎት ሲነሡ ፣ ለምጽዋት ሲዘረጉ ግን ማዳን ይችላሉ ። ደግሞም ይቀደሳሉ ።
ሁለት ጊዜ ተንበርክከን ይሆናል ። አንድ ጊዜ ትምህርት ቤት ፣ ሁለተኛው ደግሞ ቤተ ክርስቲያን ሊሆን ይችላል ። ትምህርት ቤት የተንበረከክነው ለቅጣት ነው ። ቤተ ክርስቲያን የምንበረከከው ግን ለበረከት ነው ። እጆቻችን የቊጣንና የመጠራጠርን መልእክት ለማድረስ ሳይሆን ለጸሎት ሊዘረጉ ይገባል ። ብዙ ወንዶች በቊጣ ተነሥተው ሚስታቸውን ይጎዳሉ ። ሚስት ላይ መሰንዘር በጣም መጥፎና የማይረሳ ነገር የሚተዉ በመሆኑ መጠንቀቅ ያስፈልጋል ። አንድ የሂንዱ አባባል፡- “ሚስትህን በአበባም እንኳ አትምታት” ይላል ። ወንዶች በክፉ አሳብ ወይም በመጠራጠር ሲነሡ ሌላውን ሰው ያጠቃሉ ። የአገራችን ሰው በሦስት ነገር ቀናተኛ ነው ። በሴት ፣ በመሬትና በአገሩ ። ወንዶች ሚስታቸው ላይ ጥርጥር ሲገጥማቸው መጸለይ ያስፈልጋቸዋል ። በገጠሩ ሚስቴን ትክ ብለህ አየሃት በማለት የሚገድሉ አያሌ ናቸው ። ሚስቴን ተመኝተሃታል በማለትም የሚገድሉ ብዙ ናቸው ። ወንዶች ቊጣን ከቤታቸው ፣ ጥርጥርን ከወዳጆቻቸው ሊያነሡ ይገባል ። ይህ ግን በራስ አቅም ብቻ አይሆንምና አጥብቀው መጸለይ ያስፈልጋቸዋል ።
እግዚአብሔር በትዕግሥት ይባርከን !
1ጢሞቴዎስ /29/
ታኅሣሥ 28 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ