የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

የትምህርቱ ርዕስ | ወንጌል ምንድነው ?


“እኔም ለዚህ ነገር አዋጅ ነጋሪና ሐዋርያ በእምነትና በእውነትም የአሕዛብ አስተማሪ ለመሆን ተሾምሁ ፤ እውነት እናገራለሁ ፤ አልዋሽም ።” 1ጢሞ. 2፡7
የኬንያው መሪ የነበሩት ጆሞ ኬኔያታ፡- “ፈረንጆቹ ጌታን ተቀበሉ አሉን ፣ እኛም እሺ ብለን ተቀበልን ፤ ዓይናችሁን ጨፍናችሁ ጸልዩ አሉን ፣ እኛም ዓይናችንን ጨፍነን ጸለይን ፤ ዓይናችንን ስንገልጥ ግን መሬታችንን ወስደውታል” በማለት ተናግረዋል ። ወንጌልን የቅኝ ግዛት መሣሪያ አድርገው አፍሪካን የወረሩ አያሌ ናቸው ። ዛሬ ታሪካቸውን ሳያጣሩ ለአፍሪካ ዋጋ የከፈሉ ሰማዕታት በማለት በአገራችን ወንጌላውያን ሳይቀር የሚሞገሱት አፍሪካን ያዋረዱ ፣ ታሪኳን ያጠፉ ፣ ቅኝ ገዥዎችን መንገድ መርተው ያመጡ ፣ “እነዚህን እንስሳ ሕዝቦች ማሰልጠን ከእግዚአብሔር የተሰጣችሁ አደራ ነው” ብለው በአውሮፓ ቤተ መንግሥት የሰበኩ ናቸው ። “እመት ስመኝ ለማያውቅሽ ታጠኝ” ይባላል ። ታላቁ ንጉሠ ነገሥት ኢትዮጵያን አንድ ለማድረግ የታገሉ ዐፄ ተዎድሮስ ሚስዮናውያኑን አልቀበልም ብለው ሲናገሩ፡- “መጀመሪያ ወንጌል የሚሰብክ ትልካላችሁ ፣ ቀጥሎ እርሱን የሚረዳ ብላችሁ ቆንሲል ታመጣላችሁ ፤ በመጨረሻ የጦር መሪ ልካችሁ አገር ትወርራላችሁ” ብለዋል ። ያሉት አልቀረም መጀመሪያ ወንጌል ሰባኪ ፣ ቀጥሎ ቆንሲል በመጨረሻ ጀነራል ናፒር ተልኮ የእርሳቸውም ሕይወት በመቅደላ አምባ አለፈ ። ዐፄ ዮሐንስም ወንጌል ልንሰብክ መጥተናል ያሉትን ሚስዮናውያን፡- “የአይሁድን አገር እስራኤል ፣ የእስላምን አገር ምድረ ዐረብ አልፋችሁ እንዴት እኛ ጋ ወንጌል ልትሰብኩ መጣችሁ ፣ እኛ በወንጌል እናምናለን” በማለት አባርረዋል ።  

አፍሪካን የማጥ ጉዞ ውስጥ የከተታት በወንጌል ስም የመጡባት ወራሪዎች ናቸው ። ወጣሁ ስትል የምትያዘው ፣ በአጉል የአምልኮ ልምምድ የጠፋችው አፍሪካ የዚህ ገፈት ቀማሽ ሁና ነው ። ወንጌል የምሥራችንና የእግዚአብሔርን አሳብ ይዞ የሚጓዝ እንጂ ባሕልና የኢንዱስትሪ አብዮት ይዞ የሚጓዝ አይደለም ። በአገራችን ወንጌል ሲሰበክ ነጠላውን እንዲተውና የፈረንጅ ሙሉ ልብስ እንዲለብስ ተደረገ ። በዚህም የአገራችን ሸማኔ ሥራ አጣ ። ምዕራባውያን ወንጌሉን የተጠቀሙበት የኢንዱስትሪ አብዮታቸውንም ለማስተዋወቅ ነው ። “አፀድ የሌለው ደብር ፣ ጢም የሌለው መምህር አይከብድም” በሚባልበት ባሕል ሰባኪዎቹ ጢምን ሙልጭ አድርገው ከባሕል ውጭ እንዲመጡ ተደረገ ። በአገራችን የሚሠሩ የፕሮቴስታንት አብያተ ክርስቲያናት የተገለበጠ የእንግሊዘኛው V ፊደል የሚመስሉ ናቸው ። ይህ አሠራር በረዶ ላለባቸው አገሮች ለማንሸራተት የሚውል ነው ። በረዶ በሌለበት አገር በረዶ የሚያንሸራትት ቤተ ክርስቲያን መሥራት ወንጌል ሳይሆን የሌሎች ባሕል እየተጫነን ለመሆኑ ማሳያ ነው ። በምድሪቱ ላይ ያለች ፣ በኢትዮጵያ ስም የምትጠራ ቤተ ክርስቲያን እያለች ሌላ ቤተ ክርስቲያን ማቋቋም ተገቢም አልነበረም ። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ለማገዝና ለመርዳት ሳይሆን ለማፍረስ ለዘመናት ተሠርቷል ። ውጤቱ ምን ሆነ ? ሃይማኖቱን ወዝ የለሽ አድርገውት የቀረውን አገር ደግሞ ለመናድ ጉዞ ላይ ያሉ ይመስላል ።
ወንጌል ተብሎ የተሰበከው ሰውን ከእናት ቤተ ክርስቲያኑ ማፈናቀል ነው ። በዚህም ሥርዓት የለሽ ትውልድ ፣ ተዋረድ የሌለው መዋቅር ፣ መከባበር ያጣ ክርስትና ፣ ሌላውን መናቅና መኰነን ያለበት ስብከት ተወለደ ። ወንጌል እየተባለ የሚሰበከው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንንም እንደ እርግጠኛ ጠላት ማየት ፣ የገዛ ልጆቿን እየመለመሉ የውስጥ አርበኛ አድርጎ ማፍረስ ነው ። ውጤቱ ግን ለማንም የማይሆን ራሱንም የከሰረ ትውልድ ማፍራት ሆነ ። ይህ ብቻ አይደለም የበታችነት ስሜት የሚሰማውና ጥላቻን የተሞላ ትውልድ በወንጌል ስም ስለ ተመረተ ጸሎቱ ፉከራ ፣ ስብከቱ ነቀፋ ፣ ከሰው ጋር ያለው መቀራረብ ወገናዊ ፣ የተለየ አሳብን አውጋዥ ሆነ ። ኢየሱስ የግሌ ብቻ ማለት ፣ እንደ እኔ የማያምን ሰው ርኩስ ነው ብሎ መደምደም ፣ አውቄአለሁ ብሎ ጨርሶ መኖር የበታችነት ስሜት የሚወልደው ነው ። እገሌ ያልዳነ ነው ፣ ያልበራለት ነው እያሉ መሳለቅ ያው የበታችነት ስቃይ የሚወልደው ነው ። እግዚአብሔርን ግን በጅምላ ገዝቶ በችርቻሮ የሚያከፋፍል ማንም የለም ። እርሱ የሁሉ አምላክ ነው ። ወንጌል ፍቅር እንጂ ጥላቻ አይደለም ። ወንጌል ሕይወት እንጂ ቃል አይደለም ። እነርሱ ሳይወዱኝ ኢየሱስ ይወድሃል ቢሉኝ እየዋሹኝ ነው ። አምላካቸው እንደሚወደኝ የማውቀው እነርሱ ሲወዱኝ ሳይ ነው ።
ወንጌል አሉታዊ ስብከት አይደለም ። ሐዋርያት ሙሴ አያድንም ፣ ምኵራብ አይጠቅምም ብለው አላስተማሩም ። በምኵራቡ ሰበኩበት ፣ ኦሪቱን ጠቅሰው አሳመኑበት ። “ያልተማረ ሁሉን ያረክስ ፣ የተማረ ሁሉን ይቀድስ” ይባል የለ!
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡- “እኔም ለዚህ ነገር አዋጅ ነጋሪና ሐዋርያ በእምነትና በእውነትም የአሕዛብ አስተማሪ ለመሆን ተሾምሁ ፤ እውነት እናገራለሁ ፤ አልዋሽም” ይላል 1ጢሞ. 2፡7
ሐዋርያው የተላክሁት ወንጌልን ልሰብክ ነው ይላል ። ወንጌል የእግዚአብሔር ማዳን ፣ የእስረኞች ነጻ መውጣት ፣ የዕዳ መከፈል ዜና ነው ። አብዛኛው ሰው ወንጌሉን ሳይሆን የተሰበከበትን መንገድ ተቃውሟል ። ሁሉም ሰው የራሱ ክብር አለው ፣ ወደ ሌላው ግዛት የሚገባ የሌላውን ባሕልና ታሪክ ካላከበረ ጠላትነትን ያበዛል ። ወደው ባመጡት እሳት የሚቃጠሉ ባለጌዎች እንጂ ሰማዕታት አይባሉም ። ሐዋርያው ለወንጌል አዋጅ ነጋሪ ነኝ ይላል ። አዋጅ ንጉሣዊ ድምፅ ፣ የሰማ ላልሰማ የሚያሰማው ፣ የማይጣስ ቀይ መስመር ነው ። ወንጌል የእግዚአብሔር ልጅ ለዓለም ቤዛ ሁኖ መሞቱን የምትናገር ናት ። የመንግሥቱ አዋጅም ናት ። መስማት ይገባል ፣ ላልሰማም ማሰማት ግድ ይላል ። ወንጌልን የሚሰብኩ ሰዎች ተራ ሥራ እየሠሩ ሳይሆን ንጉሣዊ መልእክትን ይዘው እየተጓዙ ነው ። በጥንት ዘመን የንጉሥን መልእክት የያዘ ሰው በደረሰበት ሁሉ አክብረው ይቀበሉት ነበር ። መልእክተኛውን መናቅ የላከውን መናቅ ነው ። ከመልእክቱ ጀርባ በረከትና ቅጣት አለ ። ወንጌል የእግዚአብሔር የምሥራች ነው ። የተሰበከበት መንገድ ግን የመርዶ ድምፅ የሰሙ እስኪመስላቸው ብዙዎችን አስደንግጧል ።
ቅዱስ ጳውሎስ ራሱን ሐዋርያ በማለት ይጠራል ። ሐዋርያ ማለት በሥልጣን የተላከ ማለት ነው ። ራሱን የቀባና የላከ ሳይሆን በእግዚአብሔር ተጠርቶ የተላከ ማለት ነው ። በዚህ ዘመን ሐዋርያዊ ሥራ አለ ። የሐዋርያትንም መንበር ጳጳሳትና ቀሳውስት ተረክበዋል ። ሐዋርያ የሚል ሹመት ግን የለም ። ሐዋርያ ለመባል ጌታን ፊት ለፊት ማየትና በቀጥታ ከእርሱ መላክ ያስፈልጋል ። /የሐዋ. 1፡21-26/ በኤፌሶን መልእክቱ ቅዱስ ጳውሎስ፡- በሐዋርያትና በነቢያት መሠረት ላይ ታንጻችኋል፥ የማዕዘኑም ራስ ድንጋይ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው” ይላል ። /ኤፌ. 2፡20 ።/ ሐዋርያት የመሠረት አገልግሎት አገልግለዋል ። ሕንጸቱ ግን በወንጌላውያን ማጽናናት ፣ በአስተማሪዎች ማጽናት ፣ በእረኞች ስምሪት ይቀጥላል ። /ኤፌ. 4፡11 ።/
ሐዋርያው ጳውሎስ ለአሕዛብ የተሾመ አገልጋይ ነው ። አሕዛብ በጣዖት ፣ በሥርዓት የለሽነት መደዴ ሁነው የኖሩ ናቸው ። ጳውሎስን የሚያህል ረቢ ፣ በአይሁድ ባሕል የኖረ ሰው ፣ ፈሪሳዊ የነበረ ወግ አጥባቂ ከአሕዛብ ጋር ሲውልና ሲያስተምር ሕይወቱ በፍጹም ፍቅር እንደተለወጠ እንረዳለን ። የማይወዱትን ሰው ከመስበክ ዝም ማለት ይሻላል ። ቅዱስ ጴጥሮስ የአይሁድ መምህር ፣ ቅዱስ ጳውሎስ የአሕዛብ መምህር ነው ። የብሉይ ኪዳን እውቀት በጥልቀት የነበረው ሐዋርያው ጳውሎስ ነው ። መዳቢዎቹ እኛ ብንሆን ጳውሎስን መምህረ አይሁድ ፣ ጴጥሮስን መምህረ አሕዛብ እናደርግ ነበር ። እግዚአብሔር አይሳሳትም ።
ሐዋርያው በእውነት ያለ ሐሰት የአሕዛብ አስተማሪ ነኝ ማለቱ ለእናንተ የተላክሁ በረከት ነኝ ተቀበሉኝ ፣ አዳምጡኝ ማለቱ ነው ። እኛስ የተላክነው ለማን መሆኑን አውቀን ይሆን ? ሰው ያለ ቦታው ትርፍ ፣ በቦታው ግን ዋና ነው ።
1ጢሞቴዎስ 28
ታህሣሥ 27 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም