የትምህርቱ ርዕስ | ወዳጄ ሆይ

ብዙ ብትወልድ እግዚአብሔር የሚባርክህ በአንዱ ነው ። አብርሃም ስምንት ወልዶ በአንዱ በይስሐቅ ተባረከ ። ዳዊት ብዙ ወልዶ በሰሎሞን ተባረከ ። ልጆችህ መልካቸው ለየራስ እንደሆነ ጠባይና ሙያቸውም ይለያያልና በማንነታቸው መንገድ በጥበብ ምራቸው ። የእናት ርኅራኄ ፣ የአባት ቆራጥነት ለአንድ ልጅ ሁለት ክንፎች ናቸው ። የእናት ርኅራኄ ብቻ ፈሪ ፣ የአባት ጭካኔ ብቻ ልጅን ደረቅ ያደርጉታል ። አስተዳደግ ሚዛናዊ ካልሆነ ልጅ አንድ ክንፍ ያለው ይሆናል ።
ወዳጄ ሆይ
መልክህ ከቤተሰብህ የተለየ ከሆነ የውጭ ሰዎች ሁሉ የዚያ ቤት ልጅ አይደለም ብለው ያልፉሃል ። ወንድሞችህና እህቶችህም አንተን ለማናደድ የሚቀልዱበት ርእስ ይሆናል ። ባደግህበት ቤት የሚመጡ እንግዶች ወንድሞችህንና እህቶችህን ስመው አንተን ሲያልፉህ ለጋ አእምሮህ የውጭ ልጅ ነኝ ወይ ? ብሎ መቀበል ይጀምራል ። ወላጆችህ ሲቆጡህና ሲመቱህ ሌላ ወላጅ ያለህ ይመስልሃል ። ነገር ግን ልዩ በመሆንህ ደስ ይበልህ ። ዓለምን ውብ ያደረጋት ልዩ ልዩ ነገር መኖሩ ነው ። የብቸኝነት ስሜት ሰበብ ፈላጊ ነውና ማንጎራጎርም ሱስ ነውና ተጠንቀቀው ።

ወዳጄ ሆይ
“የሚተኛ ሰው ዓሣ አይዝም” ይላሉ ። በማለዳ መንቃትን ፣ ለሥራ መሠማራትን ለልጆችህ አስተምር ። ልጆችህ ሊያደርጉት የሚገባቸውን ድርሻ ገና በልጅነታቸው አስለምዳቸው እንጂ አንተ አትሥራላቸው ። የሰውን ዕድሜ ጣፋጭ የሚያደርጉት ትጉ ሠራተኝነትና አንድ ጉድለት ነው ። ትጉ ሠራተኝነት ለዛሬ እንቅልፍን ይሰጣል ፣ ጉድለትም ደግሞ ለነገ ተስፋ ይሰጣል ። እናት ስትሆኚ ልጅሽን አቅፈሽ መያዝ ትፈልጊያለሽ ፣ አባት ስትሆን ደግሞ ልጅህን ሜዳ ላይ ለቅቀህ ማንበብ ትሻለህ ። ልጁም ከእናቱ አባቱን ይወዳል ፤ ምክንያቱም ነጻነት ይሰጠዋልና ። ስለዚህ ወላጅ ስትሆኑ ለልጆቻችሁ ነጻነት ስጡ ። አሊያ ይጠሉአችኋል ።
ወዳጄ ሆይ
ሰዎች የሚገኙልህ አንተ በተገኘህላቸው መጠን ነው ። ከነተረቱም “ለገቢህ ተንገብገብ” ይባላል ። ገቢህ ማለት አለሁ የሚልህ ፣ እሳት ውስጥ ስትገባ አብሮ ገብቶ የሚያወጣህ ማለት ነው ። በክፉ ቀን ወዳጅ እንድታገኝ አንተም ሰዎችን በክፉ ቀን አለሁ በላቸው ። ተማክረው ያረጉት ጥፋት የልማት ያህል ነው ። ያለ ምክር የተደረገ መልካም ነገር በምክር ከተደረገው ጥፋት በላይ ሰዎችን አልጥም ይላቸዋልና መመካከርን ውደድ ። ኑሮህን በተረት አትምራ ። የሌሎችን ተሞክሮ እቤትህ ላይ ልሞክረው አትበል ። ምክርን ሁሉ አትቀበል ። ያልሞከርከውን ለሰው አትስጥ ። ስለማታውቃቸው ሰዎች በጎም ክፉም አትናገር ። ዘመን የወለደውን በጉልበት ሳይሆን በጸሎት እንደምትጥል እወቅ ። የባለሥልጣን ወዳጅ መሆን ሲያምርህ የአንገትህን ከረባት ሰይፍ እንዳደረግህ ተረዳ ።
ወዳጄ ሆይ
ሲወለድ ትልቅ የሆነ የለም ። ከጅምሩ ስኬትን መፈለግ የሰነፎች ጠባይ ነው ። መታገል የማይሻ ተአምራትን ሲናፍቅ ይውላል ። አንዳንዴ አቋራጭ መንገድ ከዋናው ይርቃል ። በጊዜው የሚሆን መልካም ነገር ከጊዜው በፊት ከሆነ ክፉ ነገር ያመጣል ። ትልቅ ደረጃ ለመድረስ ሳይሆን ወገንህን ትልቅ ቦታ ለማድረስ ጣር ። በሬሳ ላይ ደስ ብሎት የሚመገብ እንደ ሌለ በረሀብተኛ ሕዝብ ላይም የቅምጥል ኑሮ አትመኝ ። ትልቅ ስም ያለህ ሳይሆን ትልቅ ሥራ ያለህ ሁን ። መፍትሔ ከሌለው ጎምላላነት መፍትሔ ያለው ኮሳሳነት የተሻለ ነው ። ማኅበረሰቡን ለመርዳት ከፈለግህ ርቀህ አትቀመጥ ። የማታውቀውን ሕዝብ አትረዳውምና ። አይመጣም ብለህ ከሚመጣ ፣ ይመጣል ብለህ ቢቀር ይሻላል ። ጥንቃቄ የሌለው አገር ድንገት ይናዳል ። አገር ሲሞት ማልቀሻም ይጠፋል ። በደረጃ መውጣት ልምድና ዕድገት አለው ፤ ዋጋ ስለምትከፍልም ታከብረዋለህ ። በአንድ ጀንበር ትልቅ ቦታ መድረስን አትውደደው ።
ወዳጄ ሆይ
ሙከራ የጥራት እናት ነች ። መሳሳት ከፈራህ አትሞክር ። ካልሞከርህ ሕይወትህ አይለወጥም ። ካልተራመድህ አትደናቀፍም ፣ ቁጭ ካልህ ተበላሽተህ ትቀራለህ ። እየሠሩ መሳሳት የማልማት ያህል ነው ። ከማይሠሩ አራሚዎች የሚሠሩ ተሳሳቾች ይሻላሉ ። እንዲህ ቢደረግ ከማለት እንዲህ ማድረግ የትልቅነት መገለጫ ነው ።
ወዳጄ ሆይ
መውጣት መውረድ አለውና ሰው አትበድል ። የሚገድሉ ወንጀለኞችን ያህል የማይፈርዱ ዳኞችም ገዳዮች ናቸው ። መውረድ መውጣት አለውና ተስፋን አትጣል ። ዓለም ተረኛ እንጂ ቋሚ ወዳጅ የላትምና አቦ ፣ አቦ ስትባል እባክህን ፍራ ። የእኔ የምትለው ከሄደ ያንተ አልነበረም ። የእኔ ብለኸው ያልሄደው ጌታ ግን ያንተ ነው ። ብቻህን ብትዘራም የምታጭደው ብዙ ሁነህ ነው ። መከር ሠራተኛ ፣ ማግኘትም ድሆችን ይፈልጋል ።
ወዳጄ ሆይ
ሰይጣን ሰዎችን የሚያዋርደው እንዳይናገሩ ዲዳ በማድረግ ነው ። መፍትሔ የሚገኘው በመናገር ነውና ሁኔታዎች ሲከብዱህ ከወዳጆችህ ጋር ተማከር ። ችግርህን ለመስማት ወዳጆችህ ቢሸሹህ ካንተ የባሰ ችግር ውስጥ እንዳሉ ተረዳ ። ድብቅነት ውስጥ ውስጡን የሚጨርስ እሳት ነው ። አዲስ ነገር በዓለም ላይ የለምና ለወዳጆችህና ለመንፈሳዊ አማካሪዎችህ መናገርን አትፍራ ።
ወዳጄ ሆይ
በውስጥህ ያለውን ፍቅር ካልገለጥህ ወዳጅህ አያውቀውም ። እውቀትህን ካላካፈልህ በጨለማ ያሉትን አታበራላቸውም ። ራእይህን ካልገለጥህ ተከታይም ተቃዋሚም አታገኝም ። ያልተጻፈ መጽሐፍ አይገመገምም ፣ ያልታወቀ አሳብም ጠላት የለውም ። በውስጥህ ያለውን ቅሬታ ካላወጣህ ሰዎች ይቅርታ አይጠይቁህም ። ፍላጎትህን ግልጽ ካላደረግህ ሰዎች ሳያውቁ ያስቀይሙሃል ።
ምክር /20
ጥቅምት 10 ቀን 2012 ዓ.ም.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም