የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ዋጋን ማወቅ

 ዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ ከዕለታት በአንዱ ቀን መኳንንቱና ሊቃውንቱ በተሰበሰቡበት፡

“ለመሆኑ እኔ ብሸጥ ስንተ አወጣለሁ ?” በማለት ጥያቄ አቀረቡ ። ጥያቄው ድንገተኛ ፣ ለመመለስም አስቸጋሪ ነበር ። የሚወዷቸውና የሚያከብሯቸው ነበሩና ለእርሳቸው ዋጋ ለመተመን ሕሊናቸው ተጨነቀ ። ሁሉም መልስ መመለስ አቅቶት ዝምታን በመረጠበት ጊዜ አንድ የቆሎ ተማሪ “እኔ አለሁ” በሚል ስሜት መንቆራጠጥ ጀመረ ። መልስ አለኝ ብሎም ብድግ ብሎ ቆመ።

ምኒልክም “በል ተናገር” ብለው ዕድሉን ሰጡት ። ሊቃውንቱና መኳንንቱ ያቃታቸውን መልስ ተማሪው በድፍረት መለሰ ። 

“ንጉሥ ሆይ ሃያ ዘጠኝ ብር ያወጣሉ” አላቸው ። 

ዳግማዊ ዐፄ ምኒልክም ቆጣ ብለው፡- “እንዴት እኔን በሃያ ዘጠኝ ብር ገመትከኝ?” ቢሉት ተማሪውም፡-

“የሰማይና የምድር ጌታ የሆነው ክርስቶስ የተሸጠው በሠላሳ ብር ነውና ምን ደግ ቢሆኑ ከክርስቶስ አይበልጡም ብዬ ነው በሃያ ዘጠኝ ብር የገመትክዎት” አላቸው ። 

በተማሪውም መልስ ንጉሡና በዙሪያቸው የነበሩ መኳንንቱና ሊቃውንቱ ተደንቀው ሳቁ ።

በዚህ ዓለም ላይ የራሳችንን ዋጋ ማወቅ የምፈልግበት ቀን አለ ። ንጉሥም ሆነ ሎሌ “እኔ ስንት አወጣለሁ ?” ብሎ ራሱን ይጠይቃል ፤ ዙሪያውንም መልስ ፍለጋ ያማትራል ። ምን ያህል ሕዝብ ይወደኛል ? ብሞት ማንን አጎዳለሁ ? ብኖርስ ማንን እጠቅማለሁ ? የሚሉ ጥያቄዎች በውስጣችን ተረግዘው ይወለዳሉ ። እነዚህ ጥያቄዎች ከጽንሰት እስከ ልደት ድረስ አስጨናቂ ናቸው ። አንዳንድ ሰው ራሱ በራሱ ፊት ዋጋው እያነሰበት “መኖር ትርጉም የለውም” ብሎ ይደመድማል ። ምክንያቱ ካለቀበት አንድ እርምጃ መጓዝ ሁሉም ሰው ሊከብደው ይችላል ። ወደ እግዚአብሔር “አቤት” ብሎ “ጌታዬ ሆይ ዋጋ ሁነኝ” ካላለ ውስጡን መገሠጽ ፣ ማዕበሉን መቅዘፍ ይቸገራል ። 

“እኔ ብሞት ምን ትላላችሁ ?” ብለን ልጆቻችንን እንጠይቃለን ። የምትሄደው ወይም የምትሄጅው ክርስቶስ ጋ ነውና ጥሩ ነው ካሉን ፣ “የዛሬ ልጅ ጨካኝ ነው” እንላለን ። የጠየቅነው የምንፈልገውን መልስ ለመስማት ነው ። ራሳችን ጠይቀን ራሳችን እንታዘባለን ። የዚህ ሁሉ አሰሳ ምክንያቱ ዋጋችንን ለማወቅ ነው ። ጓደኞቻችንን “ፎቶዬን ላሳድግ ፎቶ ቤት እየሄድኩ ነው” እንላለን ። ለምን ? ሲሉን “ብሞት እንኳ ማስለቀሻ ይሆናል” በማለት እንመልሳለን ። ሲደነግጡና “አይባልም” ሲሉን ደስ ይለናል ። ምክንያቱም በእነርሱ ዘንድ ያለንን ዋጋ አውቀናልና ። የአገር መሪዎች ሰልፍ የሚያስወጡት ዋጋቸውን ለማወቅም ነው ። ይጠፉና ታመሙ የሚባል ወሬ ያስወሩና ሁሉም ለፍልፎ ሲደክመው ብቅ ይላሉ ። የፎከረና ዙፋን ያማረው ያፍራል ። ያዘነና ያለቀሰም ይደሰታል ። አመመኝ የሚሉ ሚስቶች ፣ የሚያጉረመርሙ ባሎች አንዱ ችግራቸው ዋጋቸውን ስንት መሆኑን ማወቅ ስለሚፈልጉ ነው ። ኑሮ በዘዴ እንጂ በጉልበት አይደለም ። ዘዴውን ያወቁ መንገዱ ጥርጊያ  ሲሆንላቸው ፣ ያላወቁት ደግሞ ፊት ለፊት ከሚጋረጥ ተራራ ጋር ይጋጠማሉ ። 

ሕፃናትም ዋጋቸውን ማወቅ ይፈልጋሉ ። በድንገት ውድቅ በማለት “ልጄን” ሲባሉ ይደሰታሉ ፣ ይስቃሉ ። የሚደነግጥላቸው ፣ በአካል ሲወድቁ በአሳብ አብሮ የሚወድቅላቸውን ማወቅ ይሻሉ ። ወንድም በወንድሙ ዘንድ ያለውን ዋጋ ለማወቅ “እንዲህ ያለ ወንጀል ሠርቼ ልታሰር ነው” ይለዋል ። ወንድሙም ሐሰተኛ ዜና መሆኑን ሳያውቅ ይደነግጥና መላ ማቅረብ ይጀምራል ። ያን ቀን ጠያቂው ወንድም ፣ ተጠያቂ ወንድሙን በወርቅ ቀለም ይጽፈዋል ። መምህራን ዋጋቸውን ለማወቅ፡- “ጉባዔውን በትኜ አንድ ገዳም እገባለሁ” ይላሉ ። ተማሪውና ሕዝቡም፡- “ምን በደልን ይቅር ይበሉን” ሲላቸው ዋጋቸውን ያገኙትና ደስ ይላቸዋል ። 

ክርስቶስ የሰማይና የምድር ጌታ ነው ። ምንም ትሑት ብንሆን ከእርሱ አንበልጥም ። እርሱ ሊያጠፋን አቅም እያለው ችሎናል ። ምክንያቱም ትሑት ነውና ። እኛ ግን አቅም ስላነሰን ዝቅ ማለታችን ትሕትና ተብሎ ይጠራል ።

እርሱ ቢገድለንም ቢያድነንም ሁሉም በፊቱ ነው ። ትዕግሥተኛ ነውና ለመግደል በቂ ምክንያት እያለው ያድነናል ። ጥፋታችንን ሳይሆን ራሱን እያየ ይጋርደናል ። ምንም ትዕግሥተኛ ብንሆን የእርሱን ያህል ታጋሽ አይደለንም ። ምንም መከረኛ ብንሆን የእርሱን ያህል መከራ አልተቀበልንም ። እርሱ በጌትነቱ ብቻ ሳይሆን አርአያ ገብርን በመንሣቱም ልክ የለም ፣ አይደረስበትም ። 

እርሱ በበረት ተወልዷል ። ከበረት ያነሰ ቦታ መፈለግ ይገባናል ። እርሱ እኛን ሀብታም ሊያደርግ እንደ ደኸየ ከማሰብ እርሱ በመንፈስ ሊያበለጥገን ምንም የሌለው ምስኪን እንደሆነ ማመን የተሻለ ነው ። እርሱ በግብጽ በረሃ ተሰድዷል ። እኛ ግን ተሰደድን የምንለው ከእርሱ ስደት ጋር የማይነጻጸር ነው ። እርሱ ቤት የለሽ ሁኖ ኑሯል ። እኛ ግን በኪራይ ቤት ስለምንኖር እንበሳጫለን ። በኪራይ ዓለም ተቀምጠን ፣ በኮንትራት ዕድሜ እየኖርን ቋሚ ቤት እንፈልጋለን ። እርሱ በተውሶ ጀልባ ተንቀሳቅሷል ፣ እኛ ግን የራሳችን መኪና ስለሌለን ፣ በታክሲ ስለምንንቀሳቀስ እንበሳጫለን ። እርሱ በባሪያው እጅ ተጠምቋል ፣ እኛ በዕድሜም በጸጋም በክህነትም ለሚበልጡን አባቶች ዝቅ ማለት አንሻም ። እርሱ ጋኔን አለበት ተብሏል ። እኛ ግን ባነሰ ስድብ ደንብረናል ። እርሱ እብድ ነው ተብሏል ። እኛ ግን መናፍቅ መባል ያሰጋናል ። እርሱ አናጢነትን ሙያው አድርጓል ። እኛ ግን ሥራ እናማርጣለን ፣ በምንሠራው ሥራም ትልቅነት አይሰማንም ። እርሱ በጲላጦስ አደባባይ ያለ ወንጀሉ ተከስሷል ። እኛ ግን በገዛ ወንጀላችን ስንከሰስ ይከፋናል ። እርሱ በጴጥሮስ ተክዷል ። እኛ ግን በልባችን የከዳናቸው በአካል ሲከዱን ተቀደምኩ ብለን እናዝናለን ። እርሱ በይሁዳ ተሽጧል ። እኛ ግን ብዙዎችን ሸጠን ፣ አንድ ጊዜ ስንሸጥ ይቆረቁረናል ። 

በጣም ትሑት ሆነን ዝቅተኛውን ስፍራ በረትን ከመረጥን እርሱንም ክርስቶስ ይዞብናል ። በሲና በረሃ መንከራተትን ብንመርጥ እርሱ ተሰዶበታል ። ቤት የለሽ መሆንን ብንፈልግ እርሱ በተራራ ያድር ነበረ ። የገዛ ወንድሞቻችን ስለናቁን ትልቅ ማዕረግ እንዳለን ከቆጠርን እርሱ ይበልጥ በእናቱ ዘመዶች  ተንቋል ። ከበረት ያነሰውን ቦታ ፣ ከባሪያ ያነሰውን አገልጋይ ፣ ከሲና በረሃ የባሰውን  መንገድ ፣ ከሠላሳ ብር ያነሰውን ዋጋ መፈለግ አለብን ። እርሱ የሰማይና የምድር ጌታ ይህን ካገኘ እኛማ ገና ይቀረናል ። 

ስለ መከራችን ለማውራት መከራው ይገሥጸናል ። ስለ ስደታችን ለመተረክ ስደቱ ገና ነው ይለናል ። የሚሊየን ብር ዋጋ ለራሳችን ስናወጣ ክርስቶስ የተሸጠበት ሠላሳ ብሩ ተዉ ይለናል ። በመከራው ፊት መከራችን ፣ በአገልግሎቱ ፊት አገልግሎታችን ፣ በመሥዋዕትነቱ ፊት የከፈልነው ዋጋ ትንሽ ነው ። 

ጌታ ሆይ ዋጋችንን ካንተ ዋጋ እንዳናስበልጥ እርዳን ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

መስከረም 12 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ