መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ውስጣዊ ቍጣ » ውስጣዊ ቍጣ / ክፍል 2

የትምህርቱ ርዕስ | ውስጣዊ ቍጣ / ክፍል 2

ውስጣዊ ቍጣ የተለያዩ መነሻዎች አሉት ።

1- ያለመፈለግ ስሜት

ስልካቸው ቀኑን በሙሉ ባለ መጥራቱ “የሚፈልገኝ የለም” በሚል ስሜት ውስጣዊ ቍጣ ውስጥ የሚገቡ ሰዎች ብዙዎች ናቸው ። በዚህች ምክንያት ብቻ አእምሮአቸው የተቃወሰ ፣ ለምን እኖራለሁ ? ብለው ሕይወታቸውን የጠሉ ሰዎች ብዙ ናቸው ። እጮኛቸው ጋር ሊቀጥሉ ባለ መቻላቸው ያለ መፈለግ ስሜት ውስጥ የገቡ ፣ ለእኔ ያልሆነ ለማንም አይሁን ብለው አደጋ የሚያደርሱ አያሌ ናቸው ። እጮኝነት መጠናናት በመሆኑ ሊቀጥልም ሊቆምም የሚችል ነጻ ቀጠና ነው ። ሰዎች መቀጠል አልችልም የሚሉት እኛ ተፈጥሮአዊና ሞራላዊ ጉድለት ስላለብን ብቻ ሳይሆን የእኛን ፍቅር ፣ ፍቅር አልባው ልባቸው መሸከም ስላቃተው ሊሆን ይችላል ። ያለ መፈለግ ስሜት ውስጥ የገቡ ሰዎች ዛሬ ተዋውቀውት ነገ ካልደወለላቸው በዚያ ሰው ላይ ቍጠኛ ይሆናሉ ። ያለ መፈለግ ስሜት ለአገር ለወገን ደክመው ሲረሱ ፣ ከደከሙበት መንግሥት ጡረታ ሲነፈጉ የሚመጣ ነው ። ዕድሜ ዝቅም ከፍም ሲል ይህ ስሜት ይኖራል ። ወጣቶች ሌላው ላይ መኩራት ደስ ሲላቸው ሲኮሩባቸው ግን ይረበሻሉ ። ሽማግሌዎችም የገዛ አካላቸው እንኳ እየከዳቸው ነውና ሁሉ እንደ ረሳቸው ሊሰማቸው ይችላል ።

ወላጆች የልጆቻቸውን ድምፅ ሲያጡ ፣ ቀድሞ የሞቀው ቤት አሁን የሰው ረሀብ ሲገባበት ያለ መፈለግ ስሜት ይሰማቸዋል ። ያለ መፈለግ ስሜት ቍጣንና የእልህ ተግባርን እንዲፈጽሙ ያደርጋል ። ልጆቼ አይፈልጉኝም ብሎ አንድ አባት ትልቅ ቦታና ንብረቱን ሸጦ ለቤት ሠራተኛና በቅርብ ለረዱት ሰጥቶ ፣ ለራሱ መናኛ ቦታ ላይ ወድቆ በጥቂት ቀናት ውስጥ ሲሞት አውቃለሁ ። ውስጣዊ ቍጣ የእልህ ተግባር ያስፈጽማል ። ሰው የሚያጠፋው እንደ አቅሙ ነውና የአገር መሪዎችም ሁሉም ጠላት የሆነባቸው ሲመስላቸው ውስጠዊ ቍጣ ላይ ይወድቃሉ ። በአገራችንና በቤተ ክርስቲያን የእልህ ተግባራት ያመጡት ዕዳ ትውልድ የሚከፍለው ሁኗል ። አገራችን የዓለም ባንክ ዕዳ ብቻ ሳይሆን የቀደሙት ትተውት የሄዱት የእልህ ዕዳም አለባት ።

2- ወላጅ አባትን ማጣት

ብዙ ወላጅ አባቶች ለልጆቻቸው ክፉ አይደሉም ። አባቶች ግን ክፉ ተደርገው እንዲሳሉ ይደረጋል ። ገንዘባቸው እየጣፈጠ አባትነታቸው ይጠላል ። ልጆችም በልጅነት አእምሮ አባትን እንደ ክፉ ማየት እያዳበሩት ያድጋሉ ። አባቶች ስለመቆጣታቸው እንጂ ለምን እንደ ተቆጡ ልጆች እንደ ገና መመርመር ያስፈልጋቸዋል ። የሚሰሙ ጩኸቶች የማይሰሙ ቁንጥጫዎች ውጤት ናቸው ። ሁሉ አባት ደግ ላይሆን ይችላል ፣ ሁሉ አባትም ክፉ አይደለም ። በቤታቸው ሰላም ሲያጡ ጠጪ የሚሆኑ ፣ የማልመጥ ሥራ ሲሠራባቸው ቤቴንም ልጆቼንም ከስሬአለሁ ብለው አጉል ተግባር የሚፈጽሙ አባቶች አሉ ። የተናገረ ሁሉ ትክክል ፣ ዝም ያለ ሁሉ ጥፋተኛ አይደለምና ሊጠና ይገባዋል ። እግዚአብሔር ልጆች በአባትና በእናት እኩል እንክብካቤ እንዲያድጉ ፈቅዷል ። ምክንያቱም ከአባት ጥንካሬን ፣ ከእናት ፍቅርን ስለሚያገኙ ነው ። ይህን ሚዛናዊና የመንፈስ ምግብ የሚያገኙት አባትና እናት በሰላም ሲኖሩ ነው ። አባት እንዲኖርም አገር ሰላም መሆን አለባት ። ብዙ አባቶች የሚሞቱት በጦርነት ነውና ።

እናት ምንም ጎበዝ ብትሆን የአባትን ቦታ መተካት አትችልም ። ልተካ ብትልም በቶሎ ትደክማለችና ልጆችዋ ለመርዳት ሲፈልጓት አትገኝም ። አባታቸውን የማያውቁ ፣ አባታቸውን በሞት የተነጠቁ ፣ አባታቸው የማይፈልጋቸው ልጆች የሰው አባት ባዩ ቍጥር ይቀናሉ ። አባታቸውን ቢያገኙ አሁን ካለው የተሻለ ኑሮ እንደሚኖሩ ያስባሉ ። በዚህ ምክንያት የዝምታ ፍለጋው ፣ የልብ ሩጫው ሲያደክማቸው ውስጣዊ ቍጣ ውስጥ ይገባሉ ። ብስጩዎች ፣ ለእናታቸውና ለአሳዳጊዎች የማይመቹ ፣ የበቀለኝነት ስሜት የሚያዳብሩ ፣ ሰውን ሁሉ የሚጠራጠሩ ሁነው ያድጋሉ ። እግዚአብሔር አባትን ውስዶ እናትን ካስቀረ ጨርሶ አልከፋምና ተመስገን ማለት ይገባል ። አባትም እናትም ሞተው አሳዳጊ ከሰጠም ማመስገንና አሳዳጊዎችን ማክበር ያስፈልጋል ። ትልቁ ቁም ነገር መውለድ ሳይሆን ማሳደግ ነውና ። ደግሞም ይህ ሁሉ ባይኖር እግዚአብሔር አባትነቱ ከአባትም በላይ ነውና በእርሱ መደሰት ይገባል ። አለኝ ለማለት እንጂ የሚሞቱ አባትና እናትን የሰጠ ፣ የማይሞተው አባት እናት እግዚአብሔር ነው ። አባትን ማጣት ውስጣዊ ቍጣ ፣ ውጫዊ ግጭት ይፈጥራል ። የሁሉም ነገር መልስ ያለው ግን ሥላሴ ጋ መሆኑን ማሰብ ያስደስታል ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 27 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም