መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ውስጣዊ ቍጣ » ውስጣዊ ቍጣ / ክፍል 8

የትምህርቱ ርዕስ | ውስጣዊ ቍጣ / ክፍል 8

 

“የሰው ቍጣ የእግዚአብሔርን ጽድቅ አይሠራምና ።” ያዕ. 1 ፡ 20 ።

8) ጉድለት አለብኝ ብሎ ማሰብ

አንዳንድ ጊዜ ለውስጣችን የምንነግረው የጉድለት ስም አለ ። አለብኝ የምንለው ጉድለት ግን በርግጥ ላይኖር ይችላል ። ጥሩ መናገር የሚችሉ ሰዎች እኔ መናገር አልችልም ብለው ሲያዝኑ ይታያሉ ። በሌለ ችግር ተጨባጭ ጭንቀት ውስጥ የሚያልፉ ሰዎች አሉ ። መልከ ቀና ናቸው ፣ ንጹሕም ናቸው ። ነገር ግን ራሳቸውን መልክ የለኝም ፣ ንጹሕ አይደለሁም ብለው የሚጠራጠሩ አያሌ ሰዎች አሉ ። በዚህ ምክንያት ራሳቸውን ብቸኛ ያደርጋሉ ፣ ከሰዎችም ገለል ብለው ይተክዛሉ ። ባልተጨበጠ ችግር የተጨበጠ ጉዳትን በራሳቸው ላይ ያስተናግዳሉ ። በእነዚህ ሰዎች ላይ ከመፍረድ ማበረታታት የበለጠ መልካም ነው ።

ሌሎችም ጠላት በእነርሱ ላይ ያሰማውን ትችትና ነቀፌታ አምነውት ራሳቸውን ችግር እንዳለበት ሰው ይቆጥራሉ ። በተለያየ ፍርሃት ውስጥ በማለፍም ለምሳሌ እንስሳትን ፣ ከፍታ ቦታዎችን ፣ ውኃን ፣ መኪና መንዳትን በመፍራት ምክንያት ውስጣቸው ብስጩ የሚሆንባቸው አሉ ። ሌላው ያደረገውን ባለ ማድረጋቸው ያዝናሉ ፣ በራሳቸው ደካማነት ይናደዳሉ ። ነገር ግን እንዲህ ዓይነት ፍርሃቶች ሰውን ሁሉ ሊያጋጥሙ የሚችሉ ፣ በመሸሽ ሳይሆን ቀስ በቀስ በመላመድ የሚወገዱ ናቸው ።

የሰው ልጅ በሁሉ ነገር ሙሉ አይደለም ። ሙሉ ቢሆን ኖሮ አምልኮተ እግዚአብሔርን ያስቀር ነበር ። ሙሉ ቢሆን ኖሮ ሰዎችን ይገፋ ነበር ። ሙሉ ቢሆን ኖሮ ራሱን እንደ አምላክ ይቆጥር ነበር ። እግዚአብሔር ለሰውና ለመላእክት የሰጠው ቅዱስ ጉድለት አለ ። ያንን በደስታ መቀበል ይገባል ። ሳጥናኤል ይህን መረዳት አቅቶት አምላክነትን ሲሻ መልአክነትን አጣ ።

አንዳንድ የታወቁ ጉድለቶች በጸሎት ከጠየቅን ይሰጡናል ። ሌሎቹ ደግሞ ስለማያስፈልጉን አይሰጡንም ። የምንሻው ጸጋ ያለውን ጸጋ እንዳያጠፋው የማይሰጡን ሀብታት አሉ ። የቤተ ክርስቲያን እረኛ የሆነው አባት ሀብተ ፈውስ ቢሰጠው ቤተ ክርስቲያንን ለመምራት ጊዜ ሊያጣ ይችላል ። ነቢይ ትንቢት ቢናገር ሊሰማ ይችላል ። አንድ እረኛ ቢናገር ግን መንግሥትን ለመቃወም እንደ ተናገረ ሊተረጎም ይችላል ። ሌጣ ለሆነውና በማንኛውም ጊዜ ወደ ጫካው ሊገባ ለሚችል ባሕታዊ ትንቢትን ፣ አደራ ላለበት አባት ደግሞ ጥበብን የሰጠ እግዚአብሔር ድንቅ ነው !

ጉድለትን እንደ ሙላት መጠቀም ብዙዎችን ታላላቅ ቦታ ያደረሰ ነው ። ሕይወት ከዓይን ብሌን በላይ ነው ብለው ታላላቅ የዜማ ሰዎች ወጥተዋል ። ዓይነ ሥውርነታቸው ሳይገድባቸው የብዙዎችን የልብ ጨለማ የገፈፉ አሉ ። እጅና እግርን ማጣት አእምሮን ማጣት አይደለም ። ዛሬ ዘመን ሰልጥኖ ውጫዊ አካል ሳይሆን እውቀት ብቻ እንጀራ የሚያመጣ ሁኗል ። እግር የሌላቸው መኪና ይነዳሉ ፣ የማያዩ ሰዎች መራመድ ችለዋል ። ዘመኑ ከአካል ይልቅ ለእውቀት የቀረበ ነው ። ጉድለት የምንለው ነገር በራሱ ሙላት ሊሆን ይችላል ። ያንን በደስታ መቀበል አስፈላጊ ነው ። እኛ ያልተቀበልነውን ማንነት ሌሎች እንዲቀበሉት ማስገደድ አንችልምና ። በምድር ላይ ጉድለት የምንለው ነገር በሰማይ የሚጠቅም አይደለም ። የምድር ሙላት በሰማይ ባዶነት ነው ። ትልቁ ጉድለት በሥላሴ አለማመን ፣ የወልድን ቤዛነት አለመቀበል ፣ ሀብተ ወልድና ስመ ክርስትናን አለማግኘት ነው ።

በጉድለት ስሜት ብቻቸውን የሚሰቃዩ ሰዎች ሊለውጡት የሚችሉትን ነገር ዛሬ ቢጀምሩ ፣ ሊለውጡት የማይችሉትን ዛሬ እንደ ሙላት ቢያዩት ታሪክ መሥራት ይቻላል ። በእግዚአብሔር ግን ሁላችንም ሙሉ ነን ። ያለ እግዚአብሔር ያለ ሙላት ከጉድለት በላይ ያሰቃያል ። አዎ ውስጣዊ ቍጣ ጉድለት አለብኝ ብሎ ከማሰብ ይመጣል ።
ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥር 24 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም