መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » ብሉይ ኪዳን » መዝሙረ ዳዊት » ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (10)

የትምህርቱ ርዕስ | ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (10)

“ለበጎ እንኳ ዝም አልሁ ፥ ቍስሌም ታደሰብኝ ። ልቤም በውስጤ ሞቀብኝ ከማሰቤም የተነሣ እሳት ነደደ ፥ በአንደበቴም ተናገርሁ።” (መዝ. 38 ፡ 2-3 ።)

ማሽላ በእሳት ሲጠበስ ይስቃል ። ነጭ ጥርሱ ይታያል ። የማሽላ መሳቅ ግን እያረሩ ነው ። አንዳንድ ዝምታም በውስጥ እያወሩ ነው ። እውነተኛ ዝምታ እግዚአብሔርን መጠበቅ ያለበት ነው ። ብዙዎች የሆዳቸውን በሆዳቸው ይዘው ፣ ማንም ሳያውቅላቸው አርረው ሞተዋል ። መናገር ባያስፈልግ ኖሮ እግዚአብሔር አንደበትን አይፈጥርም ነበር ። መጽሐፍም አትናገሩ አላለም ። ብዙ ማዳመጥ ጥቂት መናገርን ልመዱ ብሎናል ። ተፈጥሮ ራሱ እንደሚያስተምረን ሁለት ጆሮ አንድ አፍ ተሰጥቶናል ። ከንግግር ብዛት መሳት አይቀርም ። ደግሞም፡- “ተናጋሪ ሰው በምድር ውስጥ አይጸናም” ይላል ። (መዝ. 139፡11።) ወጥተው የቀሩ ሰዎችን አስታውሱ ፣ የጥይት እራት ሆነው በሚኖሩበት ዕድሜ ያለፉትን አሰላስሉ ። ተኳሾች አልነበሩም ፣ ተናጋሪዎች ነበሩ ። ሰዎች የጥይት አረርን በይቅርታ ያልፋሉ ፣ የንግግር አረርን ግን ማለፍ ይቸገራሉ ። ለዚህ ነው፡- “አጥንት የሌላት ምላስ አጥንት ትሰብራለች” የሚባለው ።

ተናጋሪ ሰው በምድር ውስጥ መጀመሪያ በክብሩ አይጸናም ። ብዙ የሚናገር ይናቃልና ። ደግሞም አንደበት የጉልበት መውጫ ነውና የመሥራት አቅሙን በመናገር ይጨርሰዋል ። ሁለተኛው ተናጋሪ የሆነ ሰው አያኖረንም ብሎ ሁሉም ሊቀጨው ይነሣል ። አንዲት እኅት በካንሰር በሽታ ተይዛ ባሏም ፣ ልጇም ፣ ቤተሰቦቿም ሳያውቁ ከስምንት ጊዜ በላይ ለዚህ በሽታ መርጃ የሚባለውን መድኃኒት ወስዳለች ። ፍጹም አቅም አጥታ በወደቀች ጊዜ ግን ሁሉም አወቁ ። ይህች እኅት ዛሬ ሞታለች ። ሞቷን የተቀበሉ ቤተሰቦቿ ሕመሟን የማይቀበሉ መሰላት ። እንዲህ ዓይነት ዝምታዎች ጉዳት አላቸው ። ሰው መናገር አለበት ። “ካልተናገሩ አይገኝ ብልሃቱ ፣ ካልታረደ አይታይ ስባቱ” ይባላል ። ካልተናገርን ፣ ድርግም ስንል አፋችን ሳይቀር መጥፎ ጠረን ያመጣል ። መጥኖ መናገር ፣ የሚናገሩትን ማወቅ ፣ አስቦ መሰንዘር ተገቢ ነው ። በዝምታ ዘመን መናገር ግን ለጥፋት ነው ። ለሰነፎች መናገርም ማባከን ነው ።

ለበጎ እንኳ ዝም የሚባልበት ጊዜ አለ ። ቤታችን ሥርዓት ሲያጣ ፣ መናገራችን እንደ ተራ መለፍለፍ ሲታይ የሚበልጠውን መከፋፋት በማሰብ ዝም እንላለን ። ልጆቻችንን ለማቅናት ስንጣደፍ የትዳር አጋራችን በፉክክር ልጆቹን ወደ ገደል ሲከትት ፣ እኛን ለማናደድ ብሎ ልጆቹን በምግባር ሲያራቁት ያን ጊዜ ዝም እንላለን ። እንዳንናገር ገደብ ፣ እንዳንታመን ስም ሲሰጠን ፣ እኛን ለማድመጥ ጆሮ ሁሉ ዝግ ሲሆን ለበጎ እንኳ ዝም የምንልበት ጊዜ አለ ። የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ሲወድቅ ፣ በዘላለማዊ ነገር መቀለድ ሲጀመር ፣ ያልተማሩ በድፍረት ሲያወሩ ፣ ለሊቁ ጥቅስ ሲጠቅሱ ዝም ብለው የሚያዩ አዋቂዎች አሉ ። አገር ቅርጫ ፣ ቤተ ክርስቲያን የጥቂቶች ዐጽመ ርስት ስትሆን ብንናገር ጠላት ፣ መንገዱን ብናሳይ መናፍቅ እንባላለን ብለው ለበጎ እንኳ ዝም ያሉ አያሌ ናቸው ። ደፋር ደንቆሮ ስንሆን አዋቂዎችን ዱዳ እናደርጋለን ። በአባቶች ፊት ከመስማት መናገር ሲቀናን መካሪዎችን ዝም እናሰኛለን ። ይህችን ዓለም ከክፉዎች ክፋት በላይ የደጎች ዝምታ ጎድቷታል ። ክፋት ራሱን የሚያሳድግ ፣ ከችግኝ ወደ ግንድነት የሚለወጥ ነውና ዝም በማለታችን ብዙ ነገሮች ጠፍተዋል ።

እግዚአብሔርን መጠበቅ የሌለበት ዝምታ እንደ ነቀዝ ውስጥ ውስጡን የሚበላን ፣ እንደ ፍም የሚያጋየን ነው ። ጸሎት የሌለው ዝምታ ፣ ጊዜውን ያልቃኘ ዱዳነት ፣ የምን ቸገረኝ መለጎም በውስጣችን ድንጋጤ እየፈጠረ ይመጣል ። አንድ ቀን የታመቀው ስሜት ይፈነዳል ። ለብዙ ዘመን እነርሱ ብቻ ተናጋሪ የሆኑ ሰዎች አንድ ቀን ዝም ያለው ወገን ሲያፈነዳው መድረሻ ያጣሉ ። በጊዜው ያልተነፈሰ ነገር መጨረሻው ፍንዳታ ይሆናል ። እሳተ ጎሞራው ሲተነፍስ ሙቅ ውኃ ይሆናል ። በሽተኛን ይፈውሳል ። በጊዜው ማረም ከተቻለ እኛም እናርፋለን ፣ ያም ሰው ከስህተቱ ይመለሳል ። እሳተ ጎሞራ ከፈነዳ ግን ተራራን ያቀልጣል ፣ ከተሞችን ያፈርሳል ።

አንዳንድ ሰው በውስጡ ዝም ብሎ ነዶ ያልቃል ። ለበሽታ ይዳረጋል ። “ተናዳጅ እንጂ አናዳጅ አይሞትምና” ዕድሜው ያጥራል ። ሌላው ሰው ደግሞ ይናገራል ፣ ተመልሶ ይበሳጫል ። ብዙዎቻችን ስናገር ይቀለኛል ብለን ዶፉን እናወርደዋለን ። ሰዎቹን ማስደንገጥ እንችላለን ፣ መለወጥ ግን አንችልም ። ኃይለኛ የሆኑ ንግግሮች ቍስልን ከመፈወስ እንደገና እያደሱት ይመጣሉ ። አንድ ቀን ይህ አንደበት እንደሚታሰር በማሰብ እውነትን በፍቅር መግለጥ እርሱ የፈረሰውን ይገነባል ።

ሊቁ እንዲህ ብለዋል፡-

ጥበብ የሌለበት አነጋገር ስንፍና ፣
ማሰብ የሌለበት ዝምታ ድንቁርና ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥቅምት 24 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም