መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » ብሉይ ኪዳን » መዝሙረ ዳዊት » ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (16)

የትምህርቱ ርዕስ | ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (16)

“አንተ ሠርተኸኛልና ዝም አልሁ አፌንም አልከፈትሁም ።” (መዝ. 38 ፡ 9 ።)

“ሸክላ ሠሪው አይቀድመውም” ብሏል ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ። ሸክላ ሠሪ እንዳለው ይናገራል ። የፍጥረት የጸጥታው ጩኸት “እግዚአብሔር አለ” የሚል ነው ። እግዚአብሔር ቀዳማዊ ተብሎ መወደስ ክብሩ ነው ። የመጀመሪያነቱ መነሻ የሌለው ነው ። ከእርሱ በፊትም ማንም አልነበረም ። ከእርሱ በፊት የነበረ ካለ እርሱ የተገኘ ይባል ነበር ። እርሱ ግን የሁሉ አስገኚ ነው ። ከመልካምነቱ ፍጥረትን አስገኝቷልና ፍጥረት መልካም ነው ። ክፉ የሆነ ብናገኝ እንኳ በምርጫው እንጂ በተፈጥሮው ክፉ አይደለም ። “አረም ምንነትዋ ያልታወቀ ጠቃሚ ተክል ናት” የተባለውን ስናስብ አንድም ፍጥረት በከንቱ እንዳልተፈጠረ እንረዳለን ። ራሱንም ወደ ህልውና ያመጣ ማንም የለም ። ፍጥረት ግኝት ነው ። ግኝት ደግሞ በግድ አስገኚ አለው ። እግዚአብሔር ከፍጥረታት አልቆ ሰውን ፈጥሯል ። ከምድር አፈርም አበጅቶታል ። ሰው የተጠገነ ፣ የተሠራ ፣ የተበጀ ፍጥረት ነው ። ሰው አንድ ጊዜ ያለቀ ፍጥረት አይደለም ። መላእክት ፈተናቸውም ትንሣኤያቸውም አንድ ጊዜ ነው ። ሰው ግን በእንደገና ዕድል የሚኖር ነው ።

ሠሪ አለን ። ዓይን ግንባር ላይ ከሆነ ይፈርጣል ብሎ አምባ ውስጥ ያስቀመጣት ሠሪ አለን ። አፋችን ውስጥ የምናስገባው ምግብ መዓዛው እንዲያውደን ፣ መመረዙ ብክለቱ እንዲታወቀን አፍንጫን አጠገቡ የሠራ ሠሪ አለን ። አራቱ ጣታችን ያለ አምስተኛው እንደማይጨብጥ አውቆ አምስተኛ ጣትን የፈጠረ ሠሪ አለን ። ዝናብ ሲመታን ውኃ ዓይናችን ውስጥ እንዳይገባ አድርጎ ቅንድብ የሚባል በረንዳ የሠራ ሠሪ አለን ። ልባችን የሕይወት መውጫ ነውና ከተፀነስንበት ቅጽበት አንሥቶ እስከ ሞት ድረስ እንዲመታ ያደረገ ፣ ልብን ከብረት በጠነከረ ሳንቃ ውስጥ የሸሸገ ሠሪ አለን ። በሁለት እግር እየሮጥን እንዳንወድቅ አድርጎ የፈጠረን ሠሪ አለን ። ልጁ አባቱን ያውቀዋል ። የእኛ ግኝት ዝንጀሮ ሳይሆን እግዚአብሔር ነው ። ካኮራቸው አንቃወማቸውም ፣ እኛ ግን እግዚአብሔር የሠራን ሰዎች ነን ። የተሠራነው በሚራሩ እጆች ላይ ነው ። ከአፈርነት ያሥነሣን የአፉ መሳም የሆነው ትንፋሹ ነው (ዘፍ. 2 ፡ 7) ። ጠቢቡ ይህን ጥንተ ተፈጥሮ የሚያስታውስ ዝማሬ አቅርቧል፡- “በአፉ መሳም ይሳመኝ ፥ ፍቅርህ ከወይን ጠጅ ይልቅ መልካም ነውና ።” (መኃ 1 ፡ 2 ።)

ከጣኦት ቤት የወጣው አብርሃም “አንተ ሠርተኸኛል” ይላል ። በዝሙት ከተማ የመነነው ኖኅ “አንተ ሠርተኸኛል” ይላል ። በምድረ በዳ ትምህርት ቤት የተማረው ሙሴ “አንተ ሠርተኸኛል” ይላል ። ከእረኝነት ቤት ንጉሥ ሆኖ የተቀባው ዳዊት “አንተ ሠርተኸኛል” ይላል ። ክዶ ንስሐ የገባው ጴጥሮስ “አንተ ሠርተኸኛል” ይላል ። እስጢፋኖስ ሲወገር ድገም ይል የነበረው ጳውሎስ “አንተ ሠርተኸኛል” ይላል ። በመንግሥተ ሰማያት የሚበዙት ምሕረት ያገኙ ኃጢአተኞች ናቸው ። ቅዱስ አውግስጢኖስ፡- “የትላንት ስህተት ያልነበረው ጻድቅ ፣ የነገ ተስፋ የሌለው ኃጥእ የለም” ብሏል ። እግዚአብሔር ሠርቶልናል ብለን የምናመሰግነው ብቻ ሳይሆን ሠርቶናል ብለንም የምንዘምርለት ነው ። በርግጥም በሽተኛው ጳውሎስ ዓለምን አሳመነ ሲባል እግዚአብሔር ሥራውን ሠርቶለት ነው ። በዋሻ ይኖሩ የነበሩ ክርስቲያኖች የሮምን ቤተ መንግሥት ሲወርሱ እግዚአብሔር ሥራቸውን ሠርቶላቸው ነው ። ከዚህ ሁሉ በላይ እግዚአብሔር የሠራቸው ክርስቲያኖች በቤተ ክርስቲያን ይገኛሉ ።

መሠራትን መፍረስ ይቀድመዋል ። እግዚአብሔር ሠሪ ከሆነ ፈርሰናል ማለት ነው ። ተሠርተን ከሆነ የፈረስን ሰዎች ነበርን ማለት ነው ። ዛሬ ለወደቀ ስናዝን ለትላንት ማንነታችን እያዘንን ነው ። ለወደቀው ማንነታችንም እግዚአብሔር እንዳዘነለት ምስክሮች ነን ። የዛሬው ታሪካችን ከትላንት መፍረስ የጀመረ ነው ። የሁላችንም ጀርባ ደኅና አይደለም ። እግዚአብሔር ተስፋ ቢቆርጥብን ኖሮ ዛሬን ፣ “ዛሬ” ብለን ለመጥራት አንበቃም ነበር ። የትዕግሥቱ ፍሬዎች ነን ። ስለዚህ በማንም ተስፋ መቍረጥ አይገባንም ። በየቀኑ በአሳባችን የምንፈርስ ነን ። ወተቱን እያጠቆርን ፣ ማሩን እያመረርን ፣ ንጹሑን እየኰነንን የምንኖር ነን ። በገዛ ግምታችን የጠፋን ፣ ከእውነቱ ይልቅ ለተሰማን ነገር ዋጋ እየሰጠን ትዳራችንን ወዳጅነታችንን የምናፈርስ ነን ። እርሱ እየሠራን ፣ ከአሳብ ውድቀት እያነሣን ለዚህ አድርሶናል ። ውስጣችን ቢታይ ከማን ጋር እንኖር ነበር ። የሚችለን እርሱ ብቻ ነውና የኅሊናን ቁልፍ በእኛ በራሱ እጅ አደረገው ። በዚህም ምስጋናው ብዙ ነው ።

እግዚአብሔር በዝምታ ይመለካል ። ውለታው ሲበዛብን ከመዘመር መደነቅ ፣ ከመመስከር ዱዳ መሆን ይወድቅብናል ። ዝምታም ፣ ጸጥታም ለእግዚአብሔር መገዛት ነው ። ካላውካኩ ፣ ሰፈር ካልረበሹ የሚያመልኩ የማይመስላቸው ሰዎች አሉ ። ይህ የባርነት መንፈስ የሚወልደው ነው ። ነጻ የወጣ ሰው ጽሞናን ገንዘብ የሚያደርግ ነው ። የበታችነት ስሜቶች የበላይነት ስሜት ይወልዳሉ ። ይህም በሃይማኖት ስፍራም ይንጸባረቃል ። ነቢዩ የሠራውን ጌታ አሰበና በመደነቅ ጠፋ ። “አንተ ሠርተኸኛልና ዝም አልሁ አፌንም አልከፈትሁም ።” (መዝ. 38 ፡ 9 ።) ወደማንመለስበት ሳንሄድ የእግዚአብሔርን ሥራ እያስታወስን መመሰጥ ያስፈልገናል ። ባፈረሱን ነገሮች ሳይሆን በሠራን እግዚአብሔር ለመደነቅ ጥቂት ማረፍን ያድለን ! እኛ ገና አላረፍንም ፣ የበቀል በትር እየቆረጥን ነው ። የማንበላውን እየሰበሰብን ነው ። አገር አውድመን ቤት እየሠራን ነው ። ሚሊየኖችን አስርበን ሁለት ልጅ እያሳደግን ነው ። ገና አላረፍንም ። እግዚአብሔር ዕረፍትን ያድለን !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ኅዳር 10 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም