መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » ብሉይ ኪዳን » መዝሙረ ዳዊት » ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (17)

የትምህርቱ ርዕስ | ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (17)

“መቅሠፍትህን ከእኔ አርቅ ፥ ከእጅህ ብርታት የተነሣ አልቄአለሁና ።” (መዝ. 38 ፡ 10 ።)

ኃያል እጅ ከያዘን ከዚያ ውስጥ ፈልቅቆ መውጣት የማይቻል ነው ። አጉል ትግል እጃችንን ከሚሰብረው እስኪለቀን መጠበቅ የተሻለ ነው ። ከተሸነፉለት ጨካኝ የሚባለው ሰው እንኳ ይራራል። እግዚአብሔር ኃያል ነው ። በቍጣው ከመጣ ማንም አይመልሰውም ። በጉልበት ከወጣ ማንም አያሸንፈውም ። በኃይል ከዘመተ ማንም አይመክተውም ። እርሱ ግን ሲሸነፉለት የሚሸነፍ ፍቅር ነው ። አንዳንድ ነገሮች እንደሆነ እንጂ ለምን እንደሆኑ በቂ እውቀት የለንም ። ችግር ያልሠሩትን ኃጢአት የሚያናዝዝ ነው ። ምን ሠርቼ ይሆን ? እያሉ የሚያማርሩበት ነው ። አንዳንድ ጊዜ ለዛሬው ችግራችን የአስተዳደጋችንን ሁኔታ በማሰብ ወላጆቻችንን እንቀየማለን ። ሌላ ጊዜም የትምህርት ቤት መምህራችን ያለ ጥፋታችን ስለ ቀጣን ለዚህ ሁሉ የተዳረግን መስሎ ይሰማናል ። በተፈጥሮዬ ችግር ሳይኖርብኝ አይቀርም ። እኔ ስወለድ ጀምሮ የተረገምሁ ነኝ በማለት ብዙ መላ እንመታለን ። ሥጋችንን ከስረን ነፍሳችንን ለማትረፍ ስንነሣ ደግሞ መልሰን በኃጢአት እንወድቃለን ። በሚያዳልጥ ስፍራ እንደሚሮጥ ሰው ደጋግመን መውደቅ ይሰለቸናል ። እኛ ለተሸከምነው ጓደኞቻንን ስለ ችግራችን እናፍራለን ። የቤታችን ገመና የታየ እየመሰለን ከመጠን በላይ ተሽቀርቅረን እንወጣለን ። የቤቱን ቅባት ዘቅዝቀን እንቀባለን ።

ልጆቻችን የጎዱንን ፣ በመሥዋዕትነት አሳድገናቸው በጭካኔ ዓይን ያዩንን ለማን እንደምናወራው ምጥ ይይዘናል ። ለፍቶ መና የመሆን ስሜት ያንገላታናል ። ጤናችን እንደ ማታ ጀምበር እያዘቀዘቀ ሲመጣ ከመታመማችን “ማን ያስታምመኛል?”ሰ እያልን እንፈራለን ። ማራኪ ፈገግታችን ከራቀ ዓመታት ተቆጥረው ይሆናል ። አገር እንደ በድን ሆኖ እየታየን መብረር መጥፋት ያምረናል ። ጥቂት ቀን እንኳ ለማረፍ ፈልገን እርሱም እንደ ሰማይ መራቁ ፣ እንደ አድማስ መወርወሩ ግራ ይገባናል ። ለዚህ ያበቃኝ የትዳሬ ተጽእኖ ነው ፣ የፖለቲካው እድፈት ነው እያልን ብዙ ማመካኛ እንፈልጋለን ። የካብነው ሁሉ እስከ መሠረቱ የተናደ እየመሰለን የመሞከር ተስፋችን ይሟጠጥብናል ። ልባዊ የሆኑ ወዳጆች ትላንት ላይ እንጂ ዛሬና ነገ ላይ አልታይ ሲሉን ጭልም ይልብናል ። መንገዶች ሁሉ ወደ ፍላጎታችን እንደማያደርሱን ሲሰማን ከመጀመሪያው ለመጀመር እንፈልጋለን ። የኖርነውን ኑሮ ግን በዜሮ ማባዛት እንቸገራለን ።

ሁሉም ነገራችን ያለቀ መስሎ ይሰማናል ። እግራችን ደኅና ቢሆንም ለመራመድ የዛለ ፣ ለመቆም የሰለለ መስሎ ይሰማናል ። ጉንፋንን በካንሰር ልክ ፣ ሳልን በሞት ሠረገላነት እናየዋለን ። ደቃቁ ነገር እኛ ጋ ሲመጣ ተራራ ሆኖ ይታየናል ። አለማመን ረቂቁን ተራራ ሲያደርገው ፣ ማመን ደግሞ ተራራውን ደልዳላ ሜዳ አድርጎ ያየዋል ። አንድ ቀን ባደርን ቍጥር ጉልበትና የማስታወስ አቅም እየደከመ ይመጣል ። በዚህም ፈሪ እንሆናለን ። እግዚአብሔር ሰብሮኛል ማንም አይጠግነኝም የሚል ኀዘን ውስጥ እንጠመቃለን ። አእምሮአችንም እውቀትን ለመቀበል ይሰንፍብናል ። ትምህርቶች የቅንጦት ወሬ ይሆኑብናል ። ችግር ላይ በማፍጠጥ ችግር እንደማይወገድ እንዘነጋለን ። ጨለማን ቁራጭ ሻማ እንደሚያሸንፈው ረስተን ለጨለማው እናዜማለን ። መርሳት እየደጋገመ ያላግጥብናል ። እየቀለዳችሁ ነው ወይ ? እስክንባል የቅርብ ክስተቶችን ሳይቀር እንረሳለን ። ችግሩ የፈጠረብን ጭንቀት የአእምሮ ብቃታችንን ይጋፋዋል ። በግዴለሽ ሰው እንቀናለን ። አንዳንድ ጊዜም በዓለማውያን ሳይቀር ምነው እንደ እነርሱ በሆንኩኝ እንላለን ። እነርሱ ደግሞ በእኛ ኑሮ ይቀናሉ ።

ጸሎት ርቆኛል የምንልበት ጊዜ ጥቂት አይደለም ። “በእግዚአብሔር ፊት ወድቄ ምን እንዳወራሁ ሳላውቀው እነሣለሁ ፣ አንዳንዴ ዝም ብዬ እቆያለሁ ። ለመጸለይም ቃላትና ጉልበት አጥቻለሁ ። አንዳንድ ጉዳዬ ስጸልይ እየባሰ መጣ እንጂ ምንም ለውጥ አላገኘሁም” በማለት ጸሎትን ለመተው እንዳዳለን ። ወደ እግዚአብሔር ቤት በመሄድ የውሸት ፈገግታ የምንሰጥ እየመሰለን መቅረትን እንመርጣለን ። አገልጋዮቹን እንቀየማለን ። ለሌላው ችግር ሲሮጡ የእኔ ነገር ምንም አይሰማቸውም እንላለን ። እዚህ ነኝ ለማለት ስልክ አጥፍተን ለምን አልፈለጉኝም? በማለት ድብብቆሽ እንጫወታለን ። ሁለመናችን ያለቀ መስሎ ይሰማናል ። ከዚህ በኋላ የምንመኘው ቢሆን እንኳ ልብሱ በየትኛው ገላ ይለበሳል ? ትምህርቱ በየትኛው ጭንቅላት ይያዛል ? አገልግሎቱ በየትኛው አትሮኖንስ ይቀጥላል እንላለን ። ኑሮን መኖር ስላቃተን ሞትን የምንኖርበት ጊዜ አያሌ ነው ።

ሽሮና በርበሬ አለቀብኝ ማለት እንኳ ያሳቅቃል ። ራሴ አልቆብኛል ማለት ከባድ ነው ። የምናምነው ጌታ ግን ሞትን ልደት ፣ መቃብርን ሰርግ ማድረግ የሚችል ነው ። እንኳን በሰዎች ላይ በራሳችን ላይ የሚከናወነውንም ምክንያቱን ማወቅ አንችልም ። እግዚአብሔር አምላክ ነውና ለእኛ ዝርዝር ምክንያት ማቅረብ አይጠበቅበትም ። አንዱ በችግር ሌላው በምቾት በሚሰቃይበት ዓለም ላይ ነን ። እኛ አርባ ኪሎ ሜትር ለመጓዝ ገንዘብ የለንም ። ከምድር ዳር እስከ ምድር ዳርቻ በጭንቀት የሚጓዙ ፣ ምድር የጠበባቸው ሀብታሞች አሉ ። የእነርሱን ስቃይ ማግኘት አይፈውሰውም ። በዚህ ዓለም ላይ የሌለውና ኖሮት እንደሌለው የሚሰማው ሁለት ዓይነት ረሀብተኞች አሉ ። ብቻ የድሀ ደስታው ቅርብ ነው ። ባለጠጎች ሳቅን ይገዛሉ ፣ ድሆች በዕለት ሲሳይ ይደሰታሉ ። መኖር ፈልገው የሞቱ አሉ ፣ ሞትን እየለመንን መኖራችን ሊደንቀን ይገባል ። በዚህ ሁሉ ውስጥ ታዲያ እንደ ዳዊት “መቅሠፍትህን ከእኔ አርቅ ፥ ከእጅህ ብርታት የተነሣ አልቄአለሁና” እንላለን ። (መዝ. 38 ፡ 10 ።) እያጉረመረምንም ከእግዚአብሔር ቤት አለመለየት መልካም ነው ። ወላጆቹን ስለ ዱላቸው ሲወቅስ የነበረ ወጣት ሲወልድ ዱላቸው ፍቅር መሆኑ ይገባዋል ። ወላጆች ለጥፋታችን አይተዉንም ። የእግዚአብሔር ዱላ ፍቅር መሆኑ የሚገባን ቆይቶ ፣ በእምነት ስንጎለምስ ነው ።

ደግሞም ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በልደት ተፈጥሮ ፣ በሰማዕትነት ጽዋ መግባት ግድ ነው ። ሰማዕትነቱ ይለያይ እንጂ ሁላችንም በበሽታ አሊያም በፈተና እያለፍን ለሽልማት እንበቃለን ። አማኑኤል ሆይ የሚሆንብኝ አልገባኝም በእውቀትህ አድነኝ !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ኅዳር 12 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም