መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » ብሉይ ኪዳን » መዝሙረ ዳዊት » ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (18)

የትምህርቱ ርዕስ | ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (18)

“በተግሣጽህ ስለ ኃጢአቱ ሰውን ዘለፍኸው፥ ነፍሱም እንደ ሸረሪት ድር ታልቃለች በእውነት ሰው ሁሉ ከንቱ ነው ።” (መዝ. 38 ፡ 11 ።)

ወላጆች በልጃቸው እጅ ላይ ገዳይ ነገር ሲያዩ በቍጣ ያስደነግጡታል ፣ በኃይለ ቃል ይነጥቁታል እንጂ አያባብሉትም ። ማባበል ለፈነዳ ቦምብ እንጂ ለሚፈነዳ ፈንጂ አይደለም ። አደጋው ከደረሰ በኋላ “አይዞህ” ብሎ ማባበል ተገቢ ነው ። በቦምብ የተመከረን ሰው በተግሣጽ ልምከር ማለት ቃላት ማባከን ነው ። እጁ ላይ ትልቅ ጥፋት የያዘን ሰው ግን መገሠጽ ከቀጣዩ ውድመት አይብስም ። እግዚአብሔር ሕይወታችን የሚበላሽባቸውን ነገሮች ከእጃችን ላይ በቍጣውና በተግሣጹ ያስጥለናል ። ነቢዩ ዮናስ ወደ ምሥራቅ ነነዌ ወይም ኢራቅ-ሞሱል ተልኮ ወደ ምዕራብ ተርሴስ ወይም ወደ እስፔን ጉዞ ሲያደርግ እግዚአብሔር በተግሣጹ ምርጫውን ከእጁ አስጣለው ። በተርሴስ እንዴት ሁኖ ይኖራል ? ሕይወቱንም ኑሮውንም ያበላሻል ። ስለዚህ ነቢዩን በማዕበል መከረው ። በምንሄድባቸው የግል መዳረሻዎቻችን ላይ ማዕበል ሊነሣ ይችላል ። አንዳንድ ነገሮችን ገና ስንመኛቸው ጦርነት ይፋፋምባቸዋል ። እግዚአብሔር ይህ መንገድ አይሆንም እያለን ሊሆን ይችላል ። በዚያ ስፍራ ላይ የዘመናት ድካማችንን ልናባክን ፣ የአገልግሎታችንን ክብር ልናስነጥቅ እንችላለን ። እኛ የዛሬውን እርሱ የወደፊቱን ያያል ፣ እኛ ምኞታችንን ስንከተል እርሱ እውነቱን ተመልክቶ ይነጥቀናል ። በምክር ልንመለስ ስለማንችል በከባድ ማዕበል ወደ አቅጣጫችን ይመልሰናል ።

ጊዜያዊ በሆኑ ነገሮች እንማረካለን ። እውነትን ከሐሰት መለየት አቅቶን ፣ የዛሬው ፍቅር የሁልጊዜ መስሎን ፣ ሀብታችንን የዘመናት ልፋታችንን ልንበትን እንነሣለን ። አንዳንድ ጊዜ “ዘመኑን ዋጁ” በሚል ጥቅስ ያለ ዐውዱ ተርጉመን ዘመኑን እንመስላለን ። ዘመን ለመማረክ በሚመስል ፉከራ ዘመን ይማርከናል ። “እሺ” ብለናቸው “እሺ እናሰኛቸዋለን” በሚል የሞኝ ፈሊጥ ነጩን ልብሳችንን እናሳድፋለን ። እግዚአብሔር በተግሣጹ ፣ በቍጣው ከእጃችን ላይ ያስጥለናል ። የተመቸን ነገር እንዲጎረብጠን ፣ የጠለለን ነገር እንዲያራቁተን ያደርጋል ። በገንዘባችን ተመክተን እግዚአብሔርን ለመደበቅ ስንሞክር ፣ እርሱ ግን ተአምራት በሚከተለው ቍጣው ይመልሰናል ። ራሳችንን እስከ ሰጠነው ፣ ልጆቹ ነን ብለን እስካወጅን ድረስ እያለቀስን ይነጥቀናል ። እኛን ለእኛ የተወን ቀን ለማጉረምረምም ዕድል አይኖረንም ። ሕፃን ልጅ ገዳዩን ነገር ሲነጥቁት መጀመሪያ ያለቅሳል ፣ ቀጥሎ ያማርራል ። የወላጆቹ ፍቅር የሚገባው ምናልባት ከሃያ ዓመት በኋላ ነው ። ወላጆቹ እስኪገባው ብለው ቢጠብቁት ፣ በራሱ ሂደት ይማር ብለው ለራሱ ቢተዉት ኖሮ እንኳን መማር መኖር አይሆንለትም ነበር ። እግዚአብሔር አንዳንድ ነገሮችን እስኪገባን ሳይጠብቅ ይነጥቀናል ። እግዚአብሔር ከስሜታችን ለእውነቱ ቅድሚያ ይሰጣል ። በእውነት ስሜታውያን ነን ። ሰውን የማያድግ ልጅ የሚያሰኘው ስሜታዊነቱ ነው ። እየካበ የሚንደው ፣ እየጨረሰ የሚጀምረው በስሜት ጉዞው ነው ።

ነቢዩ ዳዊት የአንድ ቀን ስሜቱን ቤርሳቤህን ማየቱን ቢታገሥ ኖሮ ረጅሙ የሕይወት ዘመኑ የስብራት ባልሆነ ነበር ። አዳም በገነት ፣ ዳዊት በሰገነቱ ላይ ወደቁ ። ሁለቱም ሴትን የሚቀበሉበትን መድረክ መንፈሳዊ አላደረጉትም ። አንዳንድ ጊዜ ጸልየን ስለወጣን ወደ ገደል ብንሄድም ገደሉ እንደሚቀደስ እናስብ ይሆናል ። መጸለይ ኃላፊነትን አያስጥልም ።

እኛ ሰውን ስለ መልካምነቱ አናመሰግነውም ፣ አንመርቀውም ። ስለ ጥፋቱ ግን እንዘልፈዋለን ። እግዚአብሔር ግን ሰውን ስለኃጢአቱ ይዘልፈዋል ። “ጻድቃን ሆይ ደስ ይበላችሁ” ይላል ። እኛ ሰውን ስለ መልካምነቱ እንዘልፈዋለን ። “ለዚህ ያበቃህ ደግነትህ ነው” እንለዋለን ። ፖለቲካዊ ጽድቅን እንደ እኛ እንዲለማመድ እንመክረዋለን ። እግዚአብሔር ግን የሚዘልፈው ሰውን ስለ ኃጢአቱ ነው ። የተቆጡን ፣ የገሠጹን ሰዎች ካሉ እኛን እንደ ራሳቸው ያዩን ሰዎች ናቸው ። በዚህ ዘመን ማንም ስለማንም ማሰብ አይፈልግም ።

ኃጢአት የሰውን ነፍስ እንደ ሸረሪት ድር ይጨርሰዋል ። የሸረሪት ድር በውስጡ ያለው ጥበብና ውስብስብነት መግለጥ አይቻልም ። ለእርስዋ የመጨረሻ ቤትዋ ነው ። ሌላው ግን ቆሻሻ ነውና ይጠርገዋል ። እግዚአብሔር የሌለበት ጥበብ ሁሉ ተጠርጎ የሚጣል የሸረሪት ድር ነው ። በምድር ላይ ትልቅ ጥበብ የመሰለን ከሰማይ ሲታይ ትልቅ ሞኝነት ሊሆን ይችላል ። የሸረሪት ድር ለሸረሪትዋ የማይደፈር ምሽግ መስሎ ይሰማታል ፣ ለዚህም ብዙ ደክማለች ። ሰውም ብልጠትን መኖሪያ ያደርገዋል ፣ ውስብስብ ነገሮችን ይፈጥራል ። ነገር ግን ብልጠት የሞኝነት ያህል ሁሉ ሰው ያውቀዋል ። “እግዚአብሔርን የሚረሱ ሁሉ ፍጻሜአቸው እንዲሁ ነው የዝንጉም ሰው ተስፋ ይጠፋል ። ተስፋው ይቈረጣል ፥ እምነቱም እንደ ሸረሪት ቤት ይሆናል ። ቤቱን ይደግፈዋል ፥ አይቆምለትም ይይዘውማል ፥ አይጸናለትም ።” (ኢዮ. 8 ፡13-15 ።)

በርግጥም ሰው ከንቱ ነው ። ሥጋውን በኃጢአት ፣ ነፍሱን በውስብስብነት የሚያስጨንቅ ነው ። የቀናውን መንገድ ለመከተል ፣ ደግሞም ጥቂት ለማረፍ ነቢዩ ይለምናል ። የራስ መንገድ ያደክማል ፣ የእግዚአብሔር መንገድ ያሳርፋል ።

አሜን!

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ኅዳር 15 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም