መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » ብሉይ ኪዳን » መዝሙረ ዳዊት » ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (20)

የትምህርቱ ርዕስ | ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (20)

የመጨረሻው ክፍል

“ወደማልመለስበት ሳልሄድ ዐርፍ ዘንድ ተወኝ ።” (መዝ. 38 ፡ 13 ።)

ወደ ተለያዩ አገራት ለመሄድ የኤምባሲዎችን ደጃፍ ስናንኳኳ እንደምንመለስ ማረጋገጫ ይፈልጋሉ ። የደርሶ መልስ ትኬታችንን ያያሉ ። አገራቸው እንዲጎበኝ እንጂ ሌላ ዜጋ እንዲቀርበት አይፈልጉም ። የሰማይ መንገድ ግን መሄጃ እንጂ መመለሻ የለውም ። የሰማይ መንገድን የጀመረው ምእመን የመሄጃ እንጂ የመመለሻ ትኬት አይቆርጥም ። የሰማይ አገር ከገቡ መውጣት ፣ ካረፉ መንከራተት ፣ ከተደሰቱ ማዘን ፣ ከተወዳጁ መከዳዳት የለበትም ። በምድር ላይ ያፈራነውን ሀብትና ንብረት ጥሎ መሄድ ከባድ ነው ። ይዞ የሄደ ሰውም ፣ ወርቁ የተከተለውን ባለጠጋም አናውቅም ። የድሆች ሆድ ፣ የአገልጋዮች የታረዘ ጀርባ ግን ንብረታችንን ወደ ሰማይ የምንልክበት ነው ። አገር የሚለውጥ ሰው አስቀድሞ ንብረቱን በመርከብ ይልካል ። በመጨረሻ ራሱ ይሄዳል ። ሰማይ ስንደርስ ንብረታችን ቀድሞ ሄዶ ከሆነ ዋጋ እናገኛለን ። ከእኛ በኋላ የሚላከው ንብረት ግን ጥቅም የለውም ። ቆመን የመጸወትነው እንጂ ሞተን የሰጡልን ገንዘባችን ሽልማት አያሰጥም ። በእኛ ቤት ክርስቶስን የምንጋብዘው በድሆች አማካይነት ነው ። ያን ጊዜ በሰማይ አገሩ ክርስቶስ ይጋብዘናል ።

የሞተውን ወገናችንን ስናስብ ዳግም በዚህ ምድር አናገኘውም ። ዳግም በዚህ ምድር ላንገናኝ እንለያያለንና ለምን በምድራዊ ነገር እንፋጃለን ። ነቢዩ ዳዊት ልጁ በታመመ ጊዜ ጽኑ የሆነ ሱባዔ ያዘ ። ደኅና ነው ፣ በርታ ቢሉትም እሺ አላለም ። ያ ልጅ በሞተ ጊዜ ሊነግሩት ፈሩ ። እርሱ ግን በሁኔታቸው የልጁን ሞት ተረድቶ ማቁን ቀደደ ፣ ወርቅ ለበሰ ፤ አመዱን አራገፈ ፣ ዙፋኑ ላይ ነገሠ ። ሲታመም ያዘነው ፣ ሲሞት የበረታው ለምንድነው ? ብለው ግራ ቢገባቸው ዳዊት እንዲህ ሲል መለሰ፡- “ሕፃኑ ሕያው ሳለ፡- እግዚአብሔር ይምረኝ ፥ ሕፃኑም በሕይወት ይኖር እንደ ሆነ ማን ያውቃል ? ብዬ ጾምሁ አለቅሰሁም ። አሁን ግን ሞቶአል የምጾመው ስለ ምንድር ነው ? በውኑ እንግዲህ እመልሰው ዘንድ ይቻለኛልን ? እኔ ወደ እርሱ እሄዳለሁ እንጂ እርሱ ወደ እኔ አይመለስም አለ ።” (2ሳሙ. 12 ፡ 23 ።)

መቃብር ላይ ቲያትር ከምንሠራ በቁም መጠያየቅ ተገቢ ነው ። ሲሞት በሬ የምናርድለት ድሀ በቁሙ አንድ ዳቦ ያጣ ሊሆን ይችላል ። በሬ ያረድነውም ለራሳችን ክብር ፣ መሰሎቻችን ጋር ለመወዳደር ነው ። እስከ መቼ የሬሳ ሚዜ እንደምንሆን ግራ ያጋባል ። ሲሞት ልብሰተክህኖ ለብሰው የመጡ ካህናት ሲታመም ያልጸለዩለት ፣ ሲባዝን ያላጽናኑት ሊሆኑ ይችላሉ ። ከሞት በኋላ ምንም ልናደርግለት አንችልምና ሰውን በቁሙ መውደድ ፣ መቀበልና ማገዝ ተገቢ ነው ። በቁሙ ለወዳጁ የለፋ ልቅሶው ትንሽ ነው ። ሲቸገር አብረነው የደከምንለት ሲሞት ብዙ አናለቅስለትም ። የሰውነት ድርሻችንን ከተወጣን ሞት የእግዚአብሔር ጥሪ ነው ። ወደማይመለሱበት እየሄዱ ነውና ሰዎችን ማስከፋት አይገባም ። አሁን የምናወራውን ሰው የምናገኘው ለመጨረሻ ጊዜ ሊሆን ይችላል ። ማንም አዝኖብን ሊሞት አይደለም ፣ ወደ እንቅልፍ ሊሄድ አይገባውም ። ጀምበር ሳይጠልቅ የተቋጠረውን ነገር መፍታት ያስፈልጋል ።

ሞት መንገድ ነው ። ወደ እግዚአብሔር መንግሥት የሚያደርስ መንገድ ነው ። የፍጡር ሁሉ መንገድ ነው ። ማንም ሰው መቼ መሞቱን አናውቅም እንጂ እንደሚሞት እርግጠኞች ነን ። ሞት መጥፋት አይደለም ። የኑሮ ለውጥ ነው ። ደግሞም ክርስቶስ ትንሣኤና ሕይወት ነው ። ወደማንመለስበት ሳንሄድ ጥቂት ማረፍን እንመኛለን ። ሕይወታችን ከጭንቀት ነጻ ወጥቶ ፣ ቤተሰባችን በሰላም ተባርኮ ፣ ልጆቻችን መልካም ውሳኔ አድርገው ፣ አገራችን በልጽጋ ፣ ቤተ ክርስቲያን ተከብራ ማየት እንመኛለን ። ከዚህ ሁሉ በላይ እውነተኛው የሕይወት ሰንበት ክርስቶስ ነውና በእርሱ ማረፍ ይገባል ። በንስሐ ሸክምን ማራገፍ ፣ በመድኃኒትነቱ መዳን ያስፈልገናል ። እርሱ ራሱ፡- “እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ ፥ ወደ እኔ ኑ ፥ እኔም አሳርፋችኋለሁ ። ቀንበሬን በላያችሁ ተሸከሙ ከእኔም ተማሩ ፥ እኔ የዋህ በልቤም ትሑት ነኝና ፥ ለነፍሳችሁም ዕረፍት ታገኛላችሁ ፤” ብሏል ። (ማቴ. 11 ፡ 28-29 ።) ደግሞም፡- “ዕረፉ፥ እኔም አምላክ እንደ ሆንሁ እወቁ” ይላል ። (መዝ. 45 ፡ 10 ።) የጌታ ዕረፍት ኃላፊነት አለበት ። ማረፍ በእምነት ለእግዚአብሔር መንገድ መልቀቅ ነው ። በዚህ ዓለም ላይ ጥቂት ማረፍ ይኖር ይሆናል ። የዘላለም ዕረፍት ግን በሰማይ ነው ።

ነቢዩ ዳዊት እግዚአብሔርን ደጅ ጠና ። ጥቂት ማረፍን ለመነ ። እግዚአብሔርም ስሙንና ዝክሩን ሊያጠፉ በተመኙት ፊት አከበረው ። የዳዊት ጸሎት ላለፉት ሦስት ሺህ ዓመታት በቤተ አይሁድና በቤተ ክርስቲያን ዕለታዊ ምስጋና ነው ። ከዘር ሐረጉም የቀጠለው ሥርዓተ ንግሥ ለአራት መቶ ዓመታት ዘለቀ ። ወልደ እግዚአብሔር ክርስቶስ ወልደ ዳዊት ተብሎ መጣ ። እስራኤል ዛሬም ትልቅ መሪዋ ዳዊት ነው ። ዓርማዋ የዳዊት ኮከብ የሚባለው ነው ። በዓለም ላይ በብዛት ከተሰየሙት ስሞች “ዳዊት” የሚለው ተጠቃሽ ነው ። የዳዊት በገና በየቤቱ ይገኛል ።

የነቢዩ ዳዊትን በረከት ያሳድርብን !

ተፈጸመ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ኅዳር 18 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም