መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » ብሉይ ኪዳን » መዝሙረ ዳዊት » ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (4)

የትምህርቱ ርዕስ | ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (4)

“ወደማልመለስበት ሳልሄድ ዐርፍ ዘንድ ተወኝ ።” (መዝ. 38፡13) ።

የቅዱስ ዳዊት ትግሎች ብዙ ነበሩ ።

3- ማንም ያልተረዳው ሰው ነበረ

ነቢዩ ዳዊት ያለበትን ሁኔታ ተቀብሎ የሚኖር ሰው ነበረ ። ቤተሰቡ አራዊት ካሉበት ዱር ፣ በጎች ይጠብቅ ብሎ ሲሰደው የመጨረሻ ልጅ ቢሆንም የተጨከነበት ነበረ ። ዳዊት ግን ወደ ዱር ሲገባ በገናውን ይዞ የገባ ነበር ። ሰዎች ደስታውን ይቀሙት ዘንድ አይፈቅድላቸውም ነበር ። ተጽናንቶ ያጽናና ፣ ለመጽናናትም ያጽናና ሰው ነበር ። በሕይወት ውስጥ ተጽናንቶ ማጽናናት ፣ ለመጽናናትም ማጽናናት መልካም ነው ። ታመን ከሆነ ስለ ታመሙት መጸለይ ፣ የታመሙትን ማገዝ የእኛን በሽታ እያቀለለው ይመጣል ። የራስን ችግር በአጉሊ መነጽር ማየት “የእኔ ነገር” እያሉ ማዜም አንዳች ጥቅም የለውም ። ዳዊት በመጣው ነገር ሁሉ ይደሰት ነበር ። ጉዳዩ የሚያስደስት ሆኖ ሳይሆን ማንም የማይቀማው ደስታ እግዚአብሔር ስለሆነለት ነው ። ስለዚህም ሊጎዱት የፈለጉት ገና ነው እያሉ ሌላ ሸክም ይጭኑበት ነበር ። እያለቀሰ ሲስቅ ፣ እያመመው ደኅና ነው ሲል ቢደላው ነው እያሉ አዳዲስ መስቀል ያሸክሙት ነበር ። ራሱን ሳቅን ካልተወዳጁ በቀር በዓለም ላይ የሚያስቅ ነገር የለም ።

አንዳንድ ሰዎች ሁሉን ለእግዚአብሔር ሰጥተው ይደሰታሉ ። የእስራታቸውን ሰንሰለት እንደ ወርቅ ጌጥ ፣ መስቀላቸውንም እንደ ማዕረግ ይቆጥሩታል ። ሊያሳዝኑን ለመጡ ሰዎችና ሁኔታዎች አለማዘን ትልቅነት ነው ። ተጎድተን ካልጠበቅነው በቀር ማንም ሊጎዳን አይችልም !!!

ዳዊት የወንድሞቹን ደኅንነት ለማወቅ ወደ ጦር ሜዳ ነፍሱን ሸጦ ሲመጣ ፣ የእስራኤል የውርደት ዘመኑ እንዲያጥር ራሱን ለማሰለፍ ሲዳዳ ወንድሞቹ ፍቅሩን እርባና ቢስነት ፣ እምነቱን ትዕቢት ብለው ይተረጕሙት ነበር ። በጦር ሜዳ መሐል ያገኘው ታላቅ ወንድሙ ኤልያብ፡- “እኔ ኵራትህንና የልብህን ክፋት አውቃለሁና ሰልፉን ለማየት መጥተሃል አለው።” (1ሳሙ. 17፡28) ። ዳዊት ግን የመጣው የአባቱን ልብ ለማሳረፍ ፣ የወንድሞቹን ጤንነት ለማወቅ ነው ። ዳዊት ከቤት ወደ ዱር ሲልኩት ፣ የአንበሳና የድብ ጓደኛ ሲያደርጉት ትንሽ ነው አላሉትም ፣ ለአገሩ ሲያስብ ግን ትንሽነቱ ታያቸው ። ዳዊት እምነቱ እንደ ትዕቢት ፣ ፍቅሩ እንደ አስብቶ አራጅ የሚታይበት ፣ ስንዴ ዘርቶ እንክርዳድ ያጨደ ሰው ነበር ። ወንድሙ ልበ ክፉ ይለዋል ፣ እግዚአብሔር ግን እንደ ልቤ የሆነ ይለዋል ። በምድር ላይ የሚያስደስተው ሰዎች የሚሉንን እግዚአብሔር የማይለን መሆኑ ነው ።

ዳዊት ጎልያድን በጠጠር ባሸነፈ ጊዜ ሳኦል ሺህ ገዳይ ፣ ዳዊት እልፍ ገዳይ በማለት ሴቶች ዘፈኑ ። ሴቶቹም ሕዝቡም ዘፍነው ገቡ ። የተዘፈነለት ሰው ግን በሳኦል ተመረዘ ። ሳኦልም ከጎልያድ በላይ ዳዊትን ጠላው ። (1ሳሙ. 18 ፡ 7)። ዳዊት የዜማው ደራሲ ፣ የግጥም ገጣሚ አልነበረም ። ሕዝብን ማፈን አይቻልም ። በሰዎች ስሜትም እርሱ አይለካም ። ሳኦል የቀረው ዙፋኔ ነው ብሎ በቅንዓት ተነሣበት ፣ የንጉሥ ቅንዓት እሳት ይተፋልና ዳዊት በሞትና በእርሱ መካከል አንድ እርምጃ እስኪቀር ድረስ ብዙ ጊዜ ተሰቃየ ። ስደት ኑሮው ሆነ ። በደስታ በግ ሲጠብቅና በስደት ዱር ሲገባ ልዩነት አለው ። ነጻ ድሀ የነበረው ፣ አሁን ነጻነት የሌለው ድሀ ሆነ ። ኑሮው ያው ነው ፣ መከራው ግን ያው አልነበረም ። ዳዊት ሥልጣን ፈላጊ አልነበረም ። በእግዚአብሔር ተቀብቶ ነበረ ፣ ግን አሁንም ባሪያ ነኝ ብሎ የሚያስብ ነበረ ። ዳዊት ሰዎች ያልተረዱት ሰው ነበረ ።

የሳኦል ልጅ ዮናታን ዳዊትን እጅግ ወደደው ። ነፍስ የሚሰጣጡ ባልጀሮች ሆኑ ። አባት ያሳድደዋል ፣ ልጅ ይደብቀዋል ። እንኳን ከአንድ አገር ፣ ከአንድ ቤትም ክፉና ደግ አለ ። ልጅ በአባቱ አይለካም ። “የመጥረቢያ ልጅ መዘለፊያ” እንላለን ። አባት ሌላ ፣ ልጅ ሌላ ነው ። ሳኦል ልጄንም ዳዊት ቀማኝ ብሎ እንደገና ተነሣበት ። ፍቅር ከሥልጣን በላይ ነውና አልጋ ወራሽ የነበረው ዮናታን ወንበሩ ያንተ ነው እያለ ያበረታታው ነበር ። ፍቅር ለሚወደው ዙፋን ይለቅቃል ።

ዳዊት የገዛ ልጆቹ አልተረዱትም ነበር ። አንዱ ልጅ አሞኛል እኅቴ ታስታመኝ ይለዋል ። በአባት ፈቃድ የመጣችውን ልጅ አምኖን ይደፍራታል ፣ አባቱንም ያሸማቅቃል (2ሳሙ. 13.)። አቤሴሎም አባትና ልጅ እኅቴን አዋረዱ በማለት አምኖንን ይገድላል ። የአባቴን ልብ ሰበርኩት ብሎ አንጀቱ ቅቤ ይጠጣል ። ዳዊት ለማልቀስም ለመፍረድም እስኪቸገር ስሜት አልባ አደረጉት ። ነቢዩ ዳዊት ከልቡ ያምናል ፣ የሚታመንለት አላገኘም ። ከእረኝነት እስከ ንጉሥነት ዘመን የልቡን የሚረዳለት አጣ ። ስለዚህ አፍ እያለው ዱዳ ቢሆን “ዐርፍ ዘንድ ተወኝ” አለ ። ሥልጣን እያለሁ ተጠቃ ። የጎዱት ልጆቹና ወዳጆቹ ነበሩና ሥልጣን ወዳጅና ልጅን ለመቅጣት አይረዳም ። እጅ እያለው ሽባ ነበረ ። ስለዚህ “ዐርፍ ዘንድ ተወኝ” ብሎ ጸለየ ።

እናንተስ ሰው የማይረዳችሁ ሆናችሁ ይሆናል ። ስለምትዘምሩ የምትከፉ አይመስላቸው ፣ ችግራችሁን ስለማታወሩ እንዳልተቸገራችሁ ታስባችሁ ይሆናል ። ሕመማችሁን መቻላችሁ እንዳልታመመ ሰው ፣ ንጹሕ መልበሳችሁ እንዳልተጎዳ ሰው ተገምቶባችሁ ይሆናል ። ሊገባቸው በማይፈልጉ ፣ ስለ እናንተ ትክክለኛውን ሐቅ መረዳት በማይቻላቸው ሰዎች ፣ ለእናንተ በጎ ሊደረግ ሲል “ምን ጎደለባቸው ?” እያሉ በሚያከላክሉ ወገኖች ግራ ተጋብታችሁ ይሆናል ። በዚህ ሁሉ ግራ መጋባት ውስጥ የልብ አውቃ መድኃኔ ዓለም ከእናንተ ጋር መሆኑን እናበስራለን ። ከነቢዩ ዳዊት ጋር “ዐርፍ ዘንድ ተወኝ” ብላችሁ መጸለይ ትችላላችሁ ። እንደ ሰውነታችሁ ጸልዩ ፣ እንደ አምላክነቱ ይመልስላችኋል ።
ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥቅምት 10 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም