የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (5)

“ወደማልመለስበት ሳልሄድ ዐርፍ ዘንድ ተወኝ ።” (መዝ. 38፡13) ።

የቅዱስ ዳዊት ትግሎች ብዙ ነበሩ ።

4- በልጆች የተፈተነ ነበር

ልጆች እንደ አባት አይሆኑም ። ነጻ ፈቃድ ያላቸው ናቸውና እንደ ራሳቸው ናቸው ። ልጆች የአባትን አርአያ ይከተላሉ ። ዳዊት ብዙ ሚስቶችን አገባ ፣ ልጁ ሰሎሞን ሺህ ሚስቶች አገባ፤ ዳዊት እንደ ወንድሙ ያለውን ኦርዮንን አስገደለ ፣ ልጁ አቤሴሎም ወንድሙ አምኖንን ገደለ ። ልጆች እንደ ራሳቸው ናቸው ፣ መልካም ነገርን በሚመለከት ግን ላይከተሉ ይችላሉ ። ክፉ ነገርን ግን በግድ ይከተላሉ ። ዳዊት በሕይወቱ የዘራውን ማጨድ ያደከመው ሰው ነበረ ።

ቅዱስ ዳዊት በልጆቹ ሕይወት የተጎዳ ነበር ። ልጆቹ በሥነ ምግባር ውድቀት ፣ እርስ በርስ በመጋደል ፣ ወገን በመለየት ይፈተኑ ነበር ። እርሱ የእስራኤል ንጉሥ የሕግ አስከባሪ ነው ። በአገር ላይ ሊያየው የሚፈልገውን ሥነ ምግባር ከቤቱ አጥቶት ነበር ። አገር ተገዝቶለት ቤቱ ሸፍቶበት ፣ ሠራዊት እሺ ብሎት ልጆቹ አምጸውበት ነበር ። ሕዝቡ ዛሬስ ምን ይፈርድ ይሆን አላለውም ። ዳዊት ልቡን የሚረዳውና የሚያውቀው ሕዝብ ነበረው ። እርሱ ግን ቤቱ ከድቶት አገር ልግዛ ሲል ማፈር ይተናነቀው ይሆናል ። ልጆች እርስ በርስ ሲጋደሉ ከማየት የበለጠ ቅጣት የለም ። “የገደለው ባልሽ ፣ የሞተው ወንድምሽ ፤ ኀዘንሽ ቅጣ አጣ ከቤትሽ ልወጣ” የተባለው በዳዊት ላይ ደረሰ ። ከብዙ ሚስቶች ልጆች ሲወለዱ የአባቴ ልጅ ፣ የእናቴ ልጅ የሚል የባዕድነት ስሜት ያመጣሉ ። አቤሴሎም ለእኅቱ ትዕማር ሲቆጭ ፣ አምኖን ደግሞ የአባቴ ልጅ በማለት አቃለላት ። በቁምም በሞትም የአባቴና የእናቴ ልጅ እንደ ማለት የሚያስቀይም ነገር የለም ። ዳዊት ይህ ሁሉ ጦርነት ይካሄድ የነበረው በቤቱ ነበር ። የሚያየውን አላይም ፣ የሚሰማውን አልሰማም ማለት አይችልም ። ትልቅ ቤት ጉዱም ትልቅ ነውና ይህ በዳዊት ላይ ደረሰ ።

ልጅን መፍራት ከባድ ነው ። ቀጥሎ ምን ይሆን ? እያሉ መጠበቅ አስጨናቂ ነው ። ዳዊት ብዙ ኃላፊነት ቢኖረውም ልጆቹ እርስ በርስ የሚጣሉ ፣ ከጠላት ጋር የሚሻረኩ ፣ የራሳቸውን ክብር የጣሉ ነበሩ ። አዳም አቤልን ወልዶ ፣ ዳዊት አምኖንን መውለዱ የሚገርም ነው ። ኃጢአተኛው አዳም ጻድቁ አቤልን ፣ ጻድቁ ዳዊት መረን አምኖንን ወለደ ። ዳዊት ኦርዮንን ሲያስገድል ኃጢአቱን ለመደበቅ አስቦ ነበር ። በቆሻሻ ልብስ ላይ ሽቱ ማርከፍከፍ ክፉ ጠረኑን ማባስ ነው ። ኃጢአት በንስሐ እንጂ በሌላ ኃጢአት አይሸፈንም ። ዳዊትን ያጸናው የመጣው ነገር ይገባኛል ፣ በኃጢአቴ የመጣ ነው ብሎ በማመኑ ነበር ። ኃጢአት በመነሻው ትንሽ ነው ። ኃጢአት ትልቅ የሚሆነው ራሱን በሌላ ስህተት ለመሸፈን በሚያደርገው ጥረት ነው ።

ደግ አባት ፣ ልጆቹን የሚወድድ በቁሙም በሞቱም የሚፈራው የልጆቹን ሰላም ማጣት ነው ። አቤሴሎም አባቱን ዳዊት ከዙፋን አባሮታል ። ዳዊት ከዚህ በኋላ በምንም ላለመደነቅ የወሰነበት ክስተት ነው ። የገዛ ልጄ እንዲህ ካደረገኝ ከማንም ምንም አልጠብቅም ያለበት የሕይወት ልምድ ነው ። አቤሴሎም መድረክ ሠርቶ በአደባባይ የአባቱን ቁባቶች አስነወረ ። ዳዊት ያልሆነው ምን ነገር አለ ? (2ሳሙ. 16፡11) አኪጦፌል የዳዊት አማካሪ ነበር ። ዳዊትን እየደለለ ፣ አቤሴሎምን ደግሞ አባትህን ገልብጠው ይለው ነበር ። ሁለት ገጽ ያለው አኪጦፌል ላመነው ዳዊት ያልታመነ ሰው ነበር ። ሳይጎድልበት አባትና ልጅን አጣላ ። አገር አፈረሰ ። አቤሴሎም ላይነግሥ ዳዊት ኮበለለ ። “ሳይቸግር ጨው ብድር” እንዲሉ ነው ። ዳዊት በስንቱ ተጎዳ ፣ በስደቱ የተናቁ ሰዎች ትቢያ እየበተኑ ሲሰድቡት አልተከፋም ። አባትን በልጅ ላይ ጠላት አድርጎ የሚያስነሣ ጨካኝ ሰው ነው ። ተማሪን በመምህሩ ላይ የሚያዘምት የክፉዎች አውራ ነው ።
ራስ አዳል ልጃቸው መርዝ ጨምሮ ምግብ ሰጣቸው ይባላል ። ታማሚው አባትም እንዲህ ብለው ገጠሙ፡-

አለህም እንዳልል እንዲህ ይደረጋል ፣
የለህም እንዳልል ይመሻል ይነጋል ፤
ልጄ እንዴት ባባቱ መድኃኒት ይምሳል!?

ዳዊት በገናውን ይዞ ይህን የኀዘን እንጉርጉሮ ቢመታው በእውነት ይገልጠው ነበር ። ባለ ቅኔው ሐሰትና እውነት ፣ ትዕቢትና ትሕትና የሚያፈልቀው ፣ ሞቱን የረሳው የሰው ልጅ ቢገጥመው፡-

ጸላእኩ ሰብአ እምነ ርእስየ ፣ ሰውን ጠላሁት ከራሴ ጀምሮ ብሏል ። ቅዱስ ዳዊት ብዙ የዋሻ መንገዶችን ሄዷል ። ማንንም አልነካም ማለት ውጤታማ አያደርግም ። ሰዎች እኛን የመንካት ጥማት ሊኖራቸው ይችላል ። ልብን ማስፋት ግን ከመሰበር ይጠብቃል ።

ብዙ ሰው ቤተሰቡ ሰላም በማጣቱ ይታወካል ። አባትና እናቱን ለማስታረቅ ሽቅብ ቁልቁል የሚል ልጅ አለ ። እኅትና ወንድሞቹን ለማግባባት ሞክሮ ያልተሳካለት ፣ ከመሐል ላይ ሆኖ ከሁለት ወገን እሳት የሚነድበት አያሌ ነው ። ቤት የሸፈነው ጉድ ብዙ ነው ። አደባባይ እውነት የተደበቀበት ነው ። የሰው ሐቅ ያለው ቤቱ ነው ። በዚህ ሁሉ የዋሻ መንገድ እግዚአብሔር ቀና ያደርጋል ። አንዳንዴ ሰዎቹን በመለወጥ ይረዳናል ። ሌላ ጊዜ ደግሞ እኛን በመለወጥ ያድነናል ። አዎ ሰዎቹ ካልተለወጡ እኛ መለወጥ ግዳችን ነው ። ታዲያ ዳዊት “ዐርፍ ዘንድ ተወኝ” ቢል እውነቱን ነው!

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥቅምት 12 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ