መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » ብሉይ ኪዳን » መዝሙረ ዳዊት » ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (6)

የትምህርቱ ርዕስ | ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (6)

“ወደማልመለስበት ሳልሄድ ዐርፍ ዘንድ ተወኝ ።” (መዝ. 38፡13) ።

ነቢዩ ዳዊት ልጁ አቤሴሎም ባሳደደው ጊዜ፡- “አቤቱ ፥ የሚያስጨንቁኝ ምንኛ በዙ ! በኔ ላይ የሚቆሙት ብዙ ናቸው” በማለት ወደ እግዚአብሔር ጩኸቱን አሰምቷል ። (መዝ. 3 ፡ 1) ። በአጭር ዕድሜው ብዙ ጭንቀት ፣ በተሰፈረ ዘመኑ ያልተሰፈረ ጠላት በማስተናገዱ እንዲህ አለ ። ንጉሡ ዳዊት አደባባዩን ለመሸሽ ቤት የለው ፣ ቤቱን ለመሸሽ አደባባዩ በእነ አኪጦፌል የተሞላ ነበር ። አገራዊ ግጥማችን በዳዊት ላይ የደረሰበት ይመስላል፡-

እከክ ብቻ ሁኗል እግሬን ብዳብሰው ፣
እንዴት መቀመጫ መሄጃ ያጣል ሰው ፤

ደግሞም፡-

እሾህ ብቻ ሆነ እግሬን ብዳብሰው ፣
እንዴት መራመጃ መሄጃ ያጣል ሰው !?

ማኩረፊያ ያጣው ዳዊት ፣ በር ሲንኳኳ እየደነገጠ ፣ የልጆቼን ክፉ ልሰማ ነው ወይ ? ብሎ እየፈራ የሚኖር ሆነ ፤ የአደባባዩ ጀግና በትንሽ ልጅ እያነሰ የሚኖር ነበር ። አገሩንም ሲጎበኝ በሚያየው ያዝን ነበር ። ነገር ግን ወደ “እግዚአብሔር ቤት እንሂድ ባሉኝ ጊዜ ደስ አለኝ” በማለት ተናገረ ። (መዝ. 121 ፡ 1) ። ወደ እግዚአብሔር ቤት እንሂድ ሲባል የሚከፋው ፣ ነገር ግን ቤተ መንግሥት ለመሄድ የጋባዥ ያለ የሚለው አያሌ ሰው ነው ። ቤተ መንግሥት የነበረው ዳዊት ወደ እግዚአብሔር ቤት እንሂድ ባሉት ጊዜ ደስ ይለው ነበረ ። መንፈሳዊ ስሜቱን ሳይደብቅ የሚናገር ንጉሥ ዳዊት ብቻ ይመስላል ። ቤተ መንግሥት የማይገኘው ደስታ እግዚአብሔር ቤት ይገኛል ። ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ አዝማደ መንግሥቱን ይዘው ፣ ሚኒስትሮችን አስከትለው ወደ እግዚአብሔር ቤት ሲሄዱ ልዩ ውበት ነበረው ። ከእርሳቸው በኋላ የተነሡት ቤተ እግዚአብሔርን የሚዘጉ ፣ ቤተ ክርስቲያንን ሙዝየም እናድርግ እያሉ የሚገዳደሩ ሆኑ ። ነቢዩ ዳዊት መንፈሳዊ ጓደኞች ነበሩት ። ወደ እግዚአብሔር ቤት እንሂድ ብለው በቤተ መንግሥቱ ደጃፍ ቆመው በር ያንኳኩ ነበር ። የነገሥታት መንፈሳዊ ጓደኞች ወደ መልካም ነገር ይመራሉ ። ንጉሡ ወደ መልካም ነገር ሲሄድ አገርም ወደ መልካም ግብ ትጓዛለች ።

የእግዚአብሔር ቤት ከባሕሩ ዓለም እግራችን መርገጫ የሚያገኝበት ደሴት ነው ። ማዕበሉን የምናሳልፍበት ፣ እፎይ ብለን እንደገና ጉዞ የምንጀምርበት መካነ ሰላም ነው ። ነቢዩ ዳዊት “ዐርፍ ዘንድ ተወኝ” ባለበት ምዕራፍ ብዙ ነገሮችን አንሥቷል ። ይህን በየቍጥሩ እናያለን ፡-

“በአንደበቴ እንዳልስት መንገዴን እጠብቃለሁ ኃጢአተኛ በፊቴ በተቃወመኝ ጊዜ በአፌ ላይ ጠባቂ አኖራለሁ አልሁ።” (መዝ. 38 ፡ 1) ።

አንደበት በመንገድ ይመሰላል ። ስለዚህ “እገሌ በአፉ ይስታል” ይባላል ። “እገሌ ሲናገር ድንቅፍ አይለውም” ይላሉ ። “እገሌ ፍሰቱን የጠበቀ ንግግር ይናገራል ።” “እገሌ ንግግር ያረዝማል ፣ ለመጠቅለል ሠላሳ ደቂቃ ይፈጅበታል” ይባላል ። ይህ ሁሉ ዘይቤ አንደበት በመንገድ ተመስሎ ሲነገር ነው። የምንጓዘው ወደ ተናገርነው ነው ። “ወልደው ሳያበቁ ፣ በሰው ልጅ አይስቁ” ይባላል ። ሳቅ ስላቅ መናገር የነገ ትውልድን ሊበድል ይችላል ። ምላስ ብዙ ተናግሮ አንድ ቀን ተመትቶ አያውቅም ። ምላስ በተናገረ ሌላው አካል ሲመታ ይኖራል ። በምላሳችንም ለትውልድ መከራ እናመጣለን ። በንቀት ንግግር ትውልድ ዋጋ ይከፍላል ። በግጥም ፣ በሙሾ ፣ በፉከራ ፣ በሰርግ ዘፈን የምንጥላቸው ቃላት ብርቱ ስቃይ ያመጣሉ ። እኛ እየደከምን ስንመጣ የናቅነው ግን ወደ ክብር ለመድረስ ሲታገል ያድራል ፣ ያን ቀን የንቀትን ዋጋ ያስከፍለናል ። “ሰውን እግሩን ስትረግጠው ክንፍ አበጀህለት” በማለት ካህሊል ጅብራን ተናግሯል ።

“አትፍረዱ” የተባለው ፍርድ የአንደበት ኃጢአት ስለሆነ ነው ። የፈረድነውን መሆናችን አይቀርም ። በሰው ኃጢአት ሲፈርድ የሚውል በዚያ ነገር መፈተን ይጀምራል ። እንደውም አንድን ነገር ደጋግመው የሚያወሩ ያንን ለመሸመት እያሰቡ ነው ። ቤት የሚገዛ ሰው ስለ ቤት ብቻ ያወራል ። መኪና የሚገዛም እንዲሁ ነው ። ስለ አንድ ኃጢአት ደጋግሞ የሚያወራም በዚያ ኃጢአት ይያዛል ። ስንፈርድ ደግፎን የነበረው የእግዚአብሔር እጅ ይነሣል ። ያን ጊዜ ሰዎቹ ከሆኑት በላይ ጭቃ ውስጥ እንለወሳለን ። “ፐ” የሚለው የግነት ምላሽ መፍረድ ነው ። “አቤት ይቅር ይበለን ፣ በእነርሱ የደረሰ ውርደት በእኛ አይድረስ” የሚለው ንግግር ፍርድን መንፈሳዊ ለዛ ለመስጠት የሚደረግ ሙከራ ነው ። ስንፈርድ ማድረግ የሚገባንን ነገር አናደርገውም ። የወሬ ማጣፈጫ ፣ የመጽናኛ ርእስ እናደርገዋለን ። የወደቀ ሰው ስናይ መወዳጀት ፣ እንዲነሣ መርዳት ፣ ከሰው አፍ መሰወር ይገባናል ። መፍረድ ግን ይህን ሁሉ ግዳጅ እንዳንወጣ ያደርገናል ። “እንዴት እርሱ ይህን ያደርጋል” የሚለው በሰዎች የመገረም ንግግር ፍርድ ነው ። በዚህ ዘመን እንኳን በአንደበት የፈረዱት ፣ በልብ የታዘቡት ይደርሳል ።

አዎ የምንጓዘው ወደ ተናገርነው ነው ። ስለዚህ ነቢዩ የነገ መንገዴን እንዳላበላሽ አንደበቴን እጠብቃለሁ አለ ። ያውም የንጉሥ ንግግር ተግባር የመሆን ዕድሉ ሰፊ ነው ። በአንድ ቃል አገር የሚያረጋ ፣ በአንድ ቃል አገር የሚያፈርስ ነውና ንጉሥ ዳዊት አንደበቴን እጠብቃለሁ አለ ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥቅምት 15 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም