የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (7)

“ኃጢአተኛ በፊቴ በተቃወመኝ ጊዜ በአፌ ላይ ጠባቂ አኖራለሁ አልሁ ።” (መዝ. 38 ፡ 1 )።

በዚህ ዘመን ከፍተኛ ገንዘብ የሚወጣው ለጥበቃ ነው ። አገሮች ፣ ቤቶች ፣ ግለሰቦች ይጠበቃሉ ። የሰለጠኑ ጠባቂዎች በመላው ዓለም እየፈሉ ነው ። በአገራችንም ሰዎችና ንብረቶች ጥበቃ ይደረግላቸዋል ። ጥበቃው ከደኅንነት ካሜራዎች ፣ በሰለጠኑ ውሾች ጭምር ይከናወናል ። አንዳንድ ለጥበቃ የሚውሉ ውሾች በመቶ ሺህዎች ዶላር ወጪ ይደረግባቸዋል ። የተለያዩ የጥበቃ ኤጀንሲዎች በየጊዜው የሥራ አድማሳቸውን ያሰፋሉ ። እነዚህ ሁሉ ጠባቂዎች አራዊትን የሚከላከሉ አይደሉም ፣ ሰው ሰውን የሚከላከልበት መሆኑ ያሳዝናል ። ከክፉ ሰው የሚጠብቁን ሌሎች ሰዎች መሆናቸው ደግሞ ሁሉ ጠላት አለመሆኑን ያሳያል ። ይህ ብቻ አይደለም ማን መሆኑን ከማናውቀው ጠላት በየቀኑ እንዲጠብቁን እንከፍላለን ። ሰው ጠላቱን እንኳ ለማወቅ ይቸገራል ። እነዚህ ሁሉ ጠባቂዎች እውነተኛውን ጠላት ሰይጣንን የሚከላከሉ አይደሉም ። የማይታየውን ጠላት የመመለስ አቅም የላቸውም ። አሁንም ሌላ የሚያስደንቀው ነገር ይህ ሁሉ ጥበቃ እየተከናወነ ወንጀል ሊወገድ አለመቻሉ ነው ። ቅጣቶች ወይም የጥበቃ ጓዶች ሰውን መቀደስ አይችሉም ። ስለዚህ ባላቸውን የሚጠብቁ ሚስቶች ፣ ሚስታቸው ላይ ሰላይ የሚልኩ ወንዶች አርፈው ቢቀመጡ መልካም ነው ። ሰው አገሩን ፣ ንብረቱን ፣ ራሱን ለመጠበቅ ጠባቂ ያኖራል ። ነቢዩ ዳዊት ግን “ለአፌ ጠባቂ አኖራለሁ” ይላል ።

እያለ ያለው ሁልጊዜ አልናገርም አይደለም ። ኃጢአተኛ በተቃወመኝ ጊዜ በአፌ ላይ ጠባቂ አኖራለሁ ይላል ። መንግሥታት ፣ ባለጠጎች ፣ ግለሰቦች ሊያቆሙት የሚገባው ጥበቃ ከንብረት ይልቅ አንደበታቸው ላይ ነው ። አንደበት የሚያፈርሰውን ያህል ጠላት ሊያፈርስ አይችልም ። ጠላት እንደውም የማስተሳሰር አቅም አለው ። የተለያዩ ሕዝቦች አንድ የሚሆኑት ጠላት ሲመጣ ነው ። ጠላት ባለውለታ የሚሆንበት ጊዜ አለ ። ጠላት “በተቃወመኝ ጊዜ” ይላል ። “ጊዜ” የሚለው ዘላለማዊ ጠላት ፣ ቋሚ ተቃውሞ እንደማይኖር ያሳያል ። ትላንት የሚቃወሙን ዛሬ የዓላማችን ተባባሪ ሆነዋል ። የሁልጊዜ ጠላት ፣ የሁልጊዜም ወዳጅ የለም ። ቀኖች የሚለዋወጡት ብቻቸውን አይደለም ፣ ሰውን ይዘው ነው ። መንፈሳዊ ሰው ግን በቀኑ ላይ ይኖራል እንጂ ቀኑ አይኖርበትም ። ራስን መግዛት ማለት ራስን መቆጠጠር ማለት ነው ። ራስን መግዛት በትልቁ የሚለካው አንደበት ላይ የበላይ በመሆን ነው ። አስቦ መናገር ካልተቻለ ፣ ተናግሮ ማሰብ ይመጣል ። ያ ደግሞ ጭንቀትን ይወልዳል ።

ዛሬ ሰዎች ያላቸው ግጭት ቦምብ ተወራውረው ፣ ጥይት ተተኳኩሰው አይደለም ። በክፉ ንግግር ተጎዳድተው ነው ። አንደበት ትንሽ የምትመስል ግን ትልቅ ጥፋት የምትሠራ ናት ። የኒውክለር ቁልፍ ትንሽ ናት ፣ ግን ዓለምን ልታጠፋ ትችላለች ። አንደበት በማነስዋ አትናቅም ። አንድ ስፖርተኛ እጁ ላይ ቆልመም ያለ ነገር ነበረው ። ግን ጎበዝ ተጫዋች ነው ። አሰልጣኙ “እኛ የአካል ጉዳተኛ ጣቢያ አይደለንም” የሚል ምጸትና ሞራል ነኪ ንግግር ተናገረው ። ያ ጎበዝ ወጣት በዚያው ደቂቃ ገብቶ ራሱን አጠፋ ። አንደበት ስንቱን እንደ ቀጨና ከሕይወት እንዳፈናቀለ የፈጠረው ጌታ ይቍጠረው ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥቅምት 20 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ