መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » ብሉይ ኪዳን » መዝሙረ ዳዊት » ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (8)

የትምህርቱ ርዕስ | ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (8)

“ኃጢአተኛ በፊቴ በተቃወመኝ ጊዜ በአፌ ላይ ጠባቂ አኖራለሁ አልሁ ።” (መዝ. 38 ፡ 1 )።

ንጉሥ ዳዊት ጥበቃ ማለት ምን ማለት መሆኑን ድሮ በአርበኝነት ዘመኑ ፣ አሁን በንግሥናው ክብሩ ያውቀዋል ። በአርበኝነት ዘመኑ ለሕይወቱ ይጠበቃል ፣ አሁን ለክብሩ ይጠበቃል ። ሰዎች ተጋፍተው እንዳይጨብጡትም ጥበቃዎቹ ይከለክላሉ ። ሰው መጠበቅ ያለበት ከሰዎች ጥቃት ብቻ ሳይሆን ከውዳሴ ከንቱም ነው ። ለቤታቸው ጥበቃ ያላቸው አፋቸው ግን ጥበቃ የሌለው ሰዎች ይህን መዝሙር ቢጸልዩ መልካም ነው ። ለሱሪ ቀበቶ ፣ ለቀሚስ መቀነት ያደረጉ ሰዎች ለአፋቸው ጠባቂ ማድረግ አለባቸው ። መኪና ፍሬን ባይኖረው ከመድረስ ይልቅ መንገድ መቅረት ዕጣው ይሆን ነበር ፣ መንገድ መቅረትም መልካም ነው ፤ አደጋም ያስከትላል ። ፍሪሲዮን የሌላቸው መኪናዎች መጥተዋል ፣ ፍሬን የሌለው መኪና ግን የለም ። ለመኪና ፍሬን ካለ ፣ ለአንደበት መቆጣጠሪያ ያስፈልገዋል ። ቆጥረው የማይናገሩ ሰዎች ይፈርሳሉ ፣ ያፈርሳሉ ። መቼም የፈረሰ ነው የሚያፈርሰው ። ሠራዊቱ ሁሉ የዳዊትን አንደበት መጠበቅ አይችልም ። ዳዊት ግን ራሱ አንደበቱን ይጠብቃል ። አንደበት የባለቤቱ ኃላፊነት ነው ።

ሰው አንደበት የሚጠበቀው እንዴት ነው ? ብሎ ሊያስብ ይችላል ። አፍ ጸሎት ከያዘ አንደበት መናገር አይችልም ። ጸሎት የሚያበዙ ወሬ ይቀንሳሉ ። አንደበትን ለመጠበቅ የሚናገሩበትንና ዝም የሚሉበትን ቦታ ማወቅ ያስፈልጋል ። አንደበትን ለመመቆጣጠር ኃይለ መንፈስ ቅዱስን መለመን ያሻል ።

አፍ ያለው ካፋፍ ነው ፣
ላዩም ታቹም ገደል።

መንገድ አላሳልፍ የሚል ኃጢአተኛ ነው ። እስራኤል ወደ ከነዓን ጉዞ በጀመሩ ጊዜ መንገድ አልሰጥ ብሎ እንቢ አለ ። በዚህ ምክንያት የአማሌቅ ዝክር እንዲደመሰስ ታወጀ (ዘጸ. 17 ፡ 14) ። የሰውን ተስፋ ማጨለም ፣ ግቡ ላይ እንቅፋት መሆን ፣ ዓላማውን ማኮላሸት ፣ አካላዊ ሥነ ልቡናዊ ጫናዎች ማሳደር ፣ ማሸበር ፣ በያዘው በጎ ነገር ግራ እንዲጋባ ማድረግ ፣ አድማ ማሥነሣት ትልቅ ኃጢአተኝነት ነው ። ኃጢአተኛ ዓላማ የለሽ ነው ። ትልቁ ኃጢአት ሌሎችንም ከዓላማ ማስቀረት ነው ። “እኛም አንገባ ፣ ሰውም አናስገባ” ማለት ትልቅ በደል ነው ። ስም ማጥፋት ፣ ማውገዝ ፣ ማኮሰስ ትልቅ ኃጢአት ነው ። እግዚአብሔርን እኔም አልበጅህም ፣ እገሌም ሊበጅህ አይገባውም ብሎ በእርሱ ላይ ጠላት ማብዛት ነው ። ለሰው መሰናክል መሆን የበደል በደል ነው ።

መቃወም ጽድቅ የሚመስላቸው ብዙ ሰዎች ናቸው ። መቃወም የሐቀኝነት ምልክት ተደርጎ በመታሰቡ ዝም ብለው የሚቃወሙ ሰዎች አሉ ። ሥሩ ተብለው ቢሰጣቸው ግራ የሚጋቡ ለመቃወም ግን ከእግዚአብሔር እንደ ተቀቡ የሚናገሩ አይታጡም ። ሰዎች የራሳቸውን የሕሊና ወቀሳ ለማምለጥ የሌሎችን ስህተት ሊያወሩ ይችላሉ ። እኔ ብቻ አይደለሁም እገሌም ስቷል በማለት ለመጽናናት ይሞክራሉ ። የሚያጽናናው ግን የክርስቶስ ምሕረት እንጂ የሌሎች በደል አይደለም ።

ነቢዩ ዳዊት ወይም ንጉሥ ዳዊት ተቃዋሚዎች ነበሩት ። “ንጉሥ በግንቡም ሳይታማ አይውልም” እንዲሉ ። ንጉሥ ዳዊት በጦር ኃይሉ ማጥፋት ሲችል ክፉ እንኳ እንዳይናገራቸው ይጨነቅ ነበር ። እነዚያ ተቃዋሚዎች ስህተትን የሚያጎሉበት ፣ የሌለውን በደል በልበ ወለድ የሚጽፉበት ነበሩ ። ለእነዚህ ሰዎች መልስ መስጠት ደምን በደም ለማጥራት መሞከር ነው ። ሁለተኛ ሰምቻችኋለሁ እንደ ማለት ነው ። ሦስተኛ የባለጌ ክብሩ መልስ ማግኘቱ ነው ። አራተኛ ትልቅ ዱላ ዝምታ ነው። አምስተኛ እኛ ስንናገር እግዚአብሔር ዝም ይላል ። ደግሞም ተቃዋሚዎች ብዙ ናቸው ። ለሁሉ መልስ መስጠት ቆሞ መቅረት ነው ። የእነርሱ መደበኛ ሥራ መቃወም ነው ። ሥራችሁን ሠራችሁ ብለን መውቀስ አይገባንም ። የእኛ መደበኛ ተግባር ግን ሌላ ነው ። “ዶሮ ባልበላውም ጭሬ ልበትነው” አለች ይባላል ። ለእኛ ካልሆነ ለማንም አይሁን የሚል እሳቤ እየበዛ ነው ። “ይህን ሁሉ እየተባልህ እንዴት መልስ አትሰጥም?” የሚሉ ተቆርቋሪ ሰዎች ይኖራሉ ። ወዳጅ ለወዳጁ አምባሳደር ነው ። ስለ ወዳጁ መመስከር ይገባው ነበር ። ያልደረሰበት መላ ለማቅረብ አይቸገርም ። ነቢዩ ለአፉ ጠባቂ ነበረው ። ሠራዊቱን አፌን ጠብቁልኝ ማለት አይችልም ። አንደበት በባለቤቱ የሚጠበቅ ነውና ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥቅምት 21 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም