የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (9)

“ከዝምታ የተነሣ እንደ ዲዳ ሆንሁ፥ ለበጎ እንኳ ዝም አልሁ፥ ቍስሌም ታደሰብኝ ። ልቤም በውስጤ ሞቀብኝ ከማሰቤም የተነሣ እሳት ነደደ፥ በአንደበቴም ተናገርሁ ።” መዝ. 38፡2-3 ።

“ጨርሰህ ብላ እንጂ ጨርሰህ አትናገር” ይባላል ። ደግሞም፡- “ሁሉን ቢናገሩት ሆድ ባዶ ይቀራል” ይላሉ ። ወላጆች፡- “ሆድ ብዙ ቆሻሻ ነገር እንኳ ተሸክሟልና ምሥጢርን መቋጠር ፣ የሰውን ገመና መደበቅ ልመዱ” እያሉ ይመክራሉ ። ጨርሶ መናገር አብሮ ለመቀጠልም ለመለያየትም አይሆንም ። ብንቀጥል ፍቅር ፣ ብንለያይ ትዝታ ይሆናልና ጨርሶ ከመናገር መቆጠብ ያስፈልጋል ። ሁሉም ነገር ኢኮኖሚ በሆነበት በእኛ ዘመን ንግግር ኢኮኖሚ አለመሆኑ ይገርማል ። ቆጥቦ መናገር የሰውነት ክብር ነው ። ሰው አእምሮው ትክክለኛ ነው የሚባለው ቆጥቦ መናገር ሲችል ነው ። ብዙ ሰው ልብስ ለብሷል ፣ ግን ሁሉን ያወራል ። ልብስ የለበሰው የሚደበቅ ነገር ስላለው ነው ። ቤት የሠራው የራሱን ነገር መሸፈን ስለሚፈልግ ነው ። ቤት አደባባይ ፣ አደባባይም ቤት መሆን የለበትም ። ሁሉም ነገር ውበት የሚኖረው በመልኩ ሲቀመጥ ነው ።

የመጨረሻው ዘመን ትልቅ ፈተና አንደበት ነው ። ስለ ሐሳዊ መሢሕ በተነገረበት አንቀጽ፡- “ታላቅንም ነገርና ስድብን የሚናገርበት አፍ ተሰጠው፥ በአርባ ሁለት ወርም እንዲሠራ ሥልጣን ተሰጠው። እግዚአብሔርንም ለመሳደብ ስሙንና ማደሪያውንም በሰማይም የሚያድሩትን ሊሳደብ አፉን ከፈተ” ይላል ። (ራእ. 13 ፡ 5-6 ።) የስድብ አፍ የመጨረሻው ዘመን መገለጫ ነው ። የአውሬው መንፈስ እንደ ገነነ ምልክቱ የስድብ አፍ ሲከፈት ነው ። አውሬው በስድብ አፍ የከበሩትን ማዋረድ ይፈልጋል ። የከበረን ማዋረድ አይቻልም ። የከበረን ማዋረድ ለመዋረድ ነው። ሁለተኛው በነገድ በቋንቋ መካከል መለያየትን ይዘራል ። እነዚህ ምልክቶች በዚህ ዘመን እየታዩ ነው ። የከበሩትን ሲያዋርዱ የሚውሉ ትንሽነት የሚሰማቸው ሰዎች እየበዙ ነው ። ደግሞም ዘረኝነትን እንደ ቀላል የሚያወሩ ፣ ድልድይ ከመዘርጋት ግንብ ሲገነቡ የሚውሉ ብዙ የአውሬው ቅጥረኞችን እያየን እየሰማን ነው ።

ነቢዩ ዱዳ እስኪመስል ድረስ ዝም ብሎ ነበር ። በዝምታ አቅምን ማጠናከር ይቻላል ። የሰውነት አቅም ከሚባክንባቸው በሮች አንዱ አንደበት ነው ። ስንናገር ብዙ ኃይል እናባክናለን ። ያለንበትን አድራሻ ለጠላት እናሳውቃለን ። ልባችንን አደባባይ እናደርገዋለን ። መከራን ወደ ሕይወታችን እንጋብዛለን ። የፈረድንባቸውን ሰዎች ጾር ወይም ፈተና ወደ ራሳችን እንጠራለን ። ለጠላት ፍላጻ ተላልፈን እንሰጣለን ። ዝም ስንል ግን ውስጣችንን ማዳመጥ እንችላለን ። ለእግዚአብሔር አገልጋይነት እንታጫለን ። መንግሥት እንኳ ለጥብቅ ሥራ የሚፈልገው ምሥጢር የሚውልለት የሚያድርለትን ሰው ነው ። ዘርዛራ ወንፌት የሆነ ፣ ለማን ልናገር ላብድ ነው ለሚል ሰው ምሥጢር አይነገርም ። የእግዚአብሔር ሰው ለመናገር ቦታን ፣ ጊዜን ፣ ሰውን መለየት አለበት ። ዝምታ አያጸጽትም ። ቅዱስ አርሳዮስ፡- “ብዙ ጊዜ በመናገሬ ተጸጽቻለሁ ፣ በዝምታ ውስጥ ግን ተጸጽቼ አላውቅም” ብሏል ።

ልዑል ራስ ካሳ ኃይሉ ፍኖተ አእምሮ (የዕውቀት ጎዳና) በተሰኘ መጽሐፋቸው፡- “ከመናገር ከሚሠራው ጽድቅና በዝምታ ከሚሠራው ጽድቅሳ ማናቸው ይበልጣል ። ሁለት እጅ የሚሆነው የአንደበታችን ኃጢአት ግን ሐሰት ፣ ሐሜት ፣ ፅርፈት ፣ ሙግት ፣ ቧልት ፣ የዘፈን ጨዋታ የስንፍና ተረት ፣ የክርክር ድፍረት ይህን ፰ቱን ኃጢአት እንሠራበታለንና ስለዚህ መጻሕፍተ ጥበብ ዝምታ ወርቅ ነው መናገር ብር ነው ሲሉ የጥቅማቸውን መበላለጥ ነግረውናል ። በዚህ ዓለም ኑሮ ቢሆን የነገር አራቃቂዎች ይደኸዩበታል ፣ የሥራ አራቃቂዎች ይከብሩበታልና ዝም እንበል” ይላሉ ። (ገጽ 204 ) ።

ዝምታ ብዙ ዓይነት ነው ። አርምሞ የሚባል የዝምታ ኑሮ አለ ። ጸጥታ የሚባል የጨዋነት መገለጫ አለ ። እውቀት በማጣት የሚናገረው አጥቶም ዝም የሚል አለ ። የደበቀው ምሥጢር እንዳይወጣበት ፣ ብዙ ከመናገር የተነሣ እንዳይሳሳት የሚሞክር የብልጥ መለጎም አለ ። “ጅብ እስኪነክስ ያነክስ” እንዲሉ የራሱ እስኪያደርግ ድረስ ለማታለል ዝም የሚል የቀበሮ ባሕታዊ አለ ። ጊዜ እስኪያልፍ ብሎ ለቅሶውን ውጦ ዝም የሚል አለ ። ራስ ጉግሣ ወሌ ኑሮአቸውን ተቀምተው በቁጭት ኖረው ፣ ተዋግተው በመሞታቸው ቀኛዝማች ምስጋናው እንዲህ ብለው ገጠሙላቸው፡-

አባ ደልድል ጉግሣ ጣሉህ እንደ ማንም
እንዳላለቅስልህ ያለ ቀን አይሆንም ።

ለራስ ጉግሣ ወሌ ለማልቀስ ጃንሆይ እስኪሞቱ መጠበቅ ያስፈልጋል ። በጣይቱ የወንድም ልጅነት ምኒልክ ልጃቸውን ዘውዲቱን ዳሩለት ። ጣይቱ ሲጋዙ እንደገና እስረኛ አደረጉት ። በ1909 ዓ.ም. ንግሥት ዘውዲቱ ሲነግሡ እንዳይመክር ፣ እንዳይዘክር ተፈርቶ ትዳሩን አፋቱት ። አርቀውም ሾሙት ። በቁጭት ተዋግቶ ቢሞት ለማልቀስም ዘመኑ አልፈቀደም ። ጃንሆይ የወረዱት በ1967 ዓ.ም ነው ። ራስ ጉግሣ የሞተው በ1922 ነው ። ደርግ ሲወድቅ ለዓመታት ታፍነው የኖሩ ለልጆቻቸውና ለዘመዶቻቸው ሞት አልቅሰዋል ። ማልቀስ መቻልም ለካ በረከት ነው ። አዎ ቀኑን በመጠበቅ ልቅሶአቸውን ያፈኑ ዝምተኞች አሉ ። ነቢዩ ዳዊት ዱዳ እስኪመስል ድረስ ዝም አለ ። ለሰው ዝም አለ እንጂ ለእግዚአብሔር ዝም አላለም ። አንዳንድ ዘመንን በዝምታ እናሸንፈዋለን ።

የማርያም ልጅ አስችለን !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥቅምት 23 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ