መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ዓይን የሌለው እግር ፣ እግር የሌለው ዓይን

የትምህርቱ ርዕስ | ዓይን የሌለው እግር ፣ እግር የሌለው ዓይን

 አንድ ዓይነ ሸውራራ ሰውዬ መንገድ ሲያቋርጥ ሳያስብ በድንገት ፊት ለፊት ይመጣ የነበረው ሰው ገፍቶት ጣለው ። በዚህ ጊዜ ተናደደና “ሰማህ ወንድሜ ! ምነው የምትሄድበትን ብታይ !” ቢለው ፤ ተጋፊውም ሰውዬ፡- “ምነው አንተስ ወደምታይበት ብትሄድ” ብሎ መለሰለት ይባላል ። 

አንዱ የሚሄድበትን አያይም ፣ ሌላውም ወደሚያየው አይሄድም ። በዚህ ምክንያት ግጭቶች ይፈጠራሉ ። እግሩ የሚጓዝ ዓይኑ ግን የማያይ ብዙ ሰው አለ ። ይህ ሰው እግሩ በመጓዙ ብቻ ልቡ ቢተማመንም ዓይኑ ባለማየቱ ግን ሌላውን ገፍትሮ ይጥላል ፣ ወደ ገደልም ይገባል ። ሌላኛውም የሚያየውና የሚሄድበት ተለያይቶበታል ። የሚያየው ሌላ ነው ፣ የሚሄደው ግን ወዳላየው ነው ። የሚሄዱበትን የማያዩ ግብታውያን ናቸው ። የዘራፍ አብዮት አራማጆች ናቸው ። ያለ ርእሱ የሚጠቅሱ ፣ በብሔሬማ አትምጣብኝ ፣ በባንዲራዬ ድርድር የለኝም ፣ ሃይማኖቴንም አላስነካም ፣ በእመቤቴ ቀልድ የለም ፣ በጌታ አልደራደርም በማለት የተነሣው ጉዳይና የሚመልሱት መልስ ፍጹም የተለያየ ነው ። እንኳን የሰሙትን ነገር የሚናገሩትንም አያስተውሉትም ። ብሔር ማለት ምን ማለት ነው ? ባንዲራ ማለትስ ? ጌታስ ማነው ? ቢባሉ መልስ የላቸውም ። እየተጓዙ ነው ። የሚጓዙበትን እንዲያውቁት ሲነገራቸው ግን ፈቃደኛ አይደሉም ። “ምርምር ማብዛት ያሳብዳል” ይላሉ ። እንኳን ለምርምሩ ለሀሁ አልደረሱም ። የሚያውቁት አንድ ጥቅስ አለ ፣ እርሱን ሁሉ ቦታ ይጠቅሱታል ። መጽሐፉ አይልም ይላሉ ። መጽሐፉ የሚለውን አያውቁም ። ሕገ መንግሥቱ አይፈቅድም ይላሉ ፣ ሕገ መንግሥቱ ስለዚያ ነገር የሚተነፍሰው ምንም ነገር የለም ። ሁሉን ማርከስ ፣ ሁሉን መከልከል ፣ የሚቻልበትን ሳይሆን የማይቻልበትን ነገር መፈለግ የእውቀት መለኪያ ያደርጉታል ። 

እነዚህ ሰዎች የሚሄዱበትን አያዩም ። ስለዚህ ይጋጫሉ ። አገር የጋራ ሳለ የእኔ ብቻ ነው ብለው ያስባሉ ። ሃይማኖት ፍቅር ሳለ “ኧረ ጎራው ተነሥ” ይላሉ ። ለማወቅ አይፈቅዱም ። ነገር ግን ደፋር ሃይማኖተኛ ናቸው ። ደፋር ፖለቲከኛም ናቸው ። ለመማር አይመጡም ፣ “ችግር ካለ ጥሩኝ” ይላሉ ። ራሳቸውን እንደ እሳት አደጋ ሠራተኛ ፣ እንደ አድማ በታኝ ፖሊስ ይቆጥራሉ ። በግርግር ቢሞቱ ታሪካቸው ከአርበኞች ጋር እንደሚነሣ ፣ ሲኖዶስ ተቀምጦ የቅዱስነት ማዕረግ እንደሚሰጣቸው ያስባሉ ። ሞቅ ሞቅ ሲል ደስ ይላቸዋል ። ዓይናቸውን ጨፍነው የሚነዱ ፣ ለተከተላቸው ሰው ኃላፊነት የማይሰማቸው ፣ ቀጥሎ ምን ይሆናል ? በዚህ ንግግሬ ምን ይፈጠራል ? የሚል ልቡና የራቃቸው ሰዎች ናቸው ። የሚሄዱበትን አያዩም ። ያየም ቢነግራቸው አይሰሙም ።

የሚሄዱበትን የማያዩ ሰዎች ብዙ እውቀት ጠል የሆኑ ሰዎችን ማስከተል ይችላሉ ። መምህር ኤስድሮስ፡- “ከመሃይም አትጣላ ፣ ደጋፊው ብዙ ነው ያሸንፍሃል” ብለዋል ። እነዚህ የሚሄዱበትን የማያዩ ሰዎች “አድማ ይሰምርልኛል” በማለት በጽድቁ ቀርቶ በኃጢአቱ ይመካሉ ። ክፋት የምስክር ወረቀት ቢኖረው ይንበሸበሹ ነበር ። የሰሙትን ቁምነገር ከማሰላሰል ቀድሞ ለማስተላለፍ ፣ ከመኖር ያንን ተናገሮ አዋቂ መባልን ይፈልጋሉ ። በሚወስዱት እርምጃ ቤተሰባቸው ምን ጉዳት እንደሚደርስበት ለማሰብ ጊዜ የላቸውም ። እብደታቸውን በብዙኃኑ አጸድቀው ቢሳደቡ “ተናዶ ነው ፣” ቢያዋርዱ “ልማዱ ነው ተዉት” ተብለው ቅድመ ይቅርታ አግኝተው የሚኖሩ ናቸው ። የሚናገሩትን ዓለም ሁሉ ይስማልኝ ይላሉ ። የሰማም እየመሰላቸው በደስታ ይሞላሉ ። ዓለም ግን ኢትዮጵያ የምትባል አገር መኖሯን ለማወቅ እንኳ ይቸገራል ። ኢትዮጵያዊ ነኝ ስንል እንኳ ግር የሚላቸው ፣ አፍሪካ ስንላቸው ኦ ብለው የሚሰሙን አያሌ የዓለም ሕዝቦች ናቸው ። ለራሳችን የሰጠነው ግምት ትልቅ ነው ። እንኳን አማራነትና ኦሮሞነታችንን ኢትዮጵያዊነታችን የማያውቅ የዓለም ሕዝብ አያሌ ነው ። እነዚህ የሚሄዱበትን የማያዩ ሰዎች የሚያዳምጣቸው ሰው ከኢትዮጵያውያን እንኳ ሦስት ፐርሰንት የማይሞላ ነው ። እነርሱ ሲያስነጥሱ ግን ዓለም ሁሉ “ይማርህ” የሚላቸው ይመስላቸዋል ። አዎ የሚሄዱበትን አለማየት ግጭት ያመጣል ። 

የምናምነውን ነገር ማወቅ ቀዳሚ ሲሆን ለዚያ ነገር መታመንም ተከታይ ነገር ነው ። ያለ እውቀት የሚደረግ ነገር በመጀመሪያ ኃጢአት ነው ። ሁለተኛ ወደ እውነተኛ እምነት አያደርስም ። የሚሄዱበትን የማያውቁ ሰዎች ስለሁሉም ነገር የሚመለከታቸው ይመስላቸዋል ። ስለዚህ ርእስ ይዘው እገሌ ትዳሯን ፈታች ፣ እገሌ ባለመውለዱ ምክንያት ሚስቱን ተወ ይላሉ ። ከእውቅ ሰዎች ጋር ያለን ግንኙነት ከሙያቸው እንጂ ከኑሮአቸው ጋር አይደለም ። ትልቁ ችግራችን ድንበራችንን አለማወቃችን ነው ። የትኛውም ሰው የቱንም ያህል ቢቀርበን የግል ሕይወት እንዳለው ማመንና መቀበል አለብን ። እርሱነቱን እንጂ ነጻነቱን መወዳጀት አይገባንም ። የሚሄዱበትን የማያውቁ ሰዎች የሚመለከታቸውን ርእስ አያውቁትም ። ሰው ሲያዳምጣቸው በርግጥ እንደ አዋቂ የቆጠራቸው ይመስላቸዋል ። ሰው ግን የሚሰማቸው ቀጥተኛ የሆነው ኑሮ ሲሰለቸው ለመዝናናት ብሎ ነው ። የሚሰማቸውም የእብደታቸው ልኩ ምን ያህል እንደ ደረሰ ሊገመግም ነው ። 

“አባቴ” ይላቸዋል ሞኙ ። 

ሽማግሌውም፡- “አቤት” ይሉታል ።

“ሰው ሁሉ ይወደኛል” አላቸው ።

እርሳቸውም፡- “አይ ልጄ ጅልን ማን ይጠላዋል?” ብለህ ነው አሉት ይባላል ።

ወደሚያዩበት የማይሄዱ ብዙ ሰዎች አሉ ። የባከነ እውቀት ማለት ይህ ነው ። ተምሮ ወገንን መሰብሰብ ሲገባ ሕዝብ መበተን ፣ ተመራምሮ አገር መጥቀም ሲገባ ትውልድን መበከል ይህ የባከነ እውቀት ነው ። የሚያዩት ክርስቶስን ፣ የሚሄዱት ግን ወደ አረመኔነት የሆነ ብዙ ሰዎች አሉ ። “ክርስቶስን ወደድኩት ፣ ክርስቲያኖችን ግን ጠላሁ” የተባለው ለዚህ ነው ። በእግዚአብሔር ቤት ከዓለም ስለመውጣታቸው የሚያወሩ ብዙ ሰዎች አሉ ። ዓለም ግን ከልባቸው አልወጣችምና ይኸው የእግዚአብሔርን ቤት ያምሳሉ ። “ጀበና ጥዬ ነው የመጣሁት” በማለት ከጣዖት ቤት መምጣታቸውን ዘላለም የሚተርኩ ሰዎች አሉ ። ጀበናው ግን ከእጃቸው እንጂ ከልባቸው አልወደቀም ። ቅንጣት ፍቅር ለሰው የሌላቸው ፣ በአረመኔነት የሚወዳደሩ ፣ የጌታዬ ፍቅር እያሉ ነገር ግን ዘረኝነትን የሚያራምዱ ወደሚያዩት የማይሄዱ ናቸው ። እነዚህ ሰዎች ከሌላው ጋር ሲጋጩ ይኖራሉ ። ሰላም የላቸውም ፣ ከሁሉ ሰው ጋር ይነታረካሉ ። ጠባቸውን መንፈሳዊ ያደርጉታል ። “ስለ ጌታ ብዬ ተሰደድሁ” ይላሉ ። ያሳደዱአቸውን ሲረግሙ ይውላሉ ። ያለቀሱ እንደሆነ እንባቸው ከአዲሱ የዓባይ ግድብ ይልቃል ። “የውሸታም/የዓባይ እንባ ባቄላ ባቄላ ያህላል” ይባላል ። ቀላል ልብ ያላቸው ሰዎች በእንባቸው ይማረካሉ ። በግላቸው ሲጸልዩ እንባ የማይመጣላቸው ፣ ሰው ፊት ሲቆሙ ግን በእንባ የሚታጠቡ ብዙ ናቸው ። እግረ መስቀሉ ሥር ቆመን ያልመጣ እንባ ፣ ሰው ፊት ስንቆም ከመጣ የልመና ስልት እንጂ የክርስትና ፍቅር አይደለም ። 

አዎ ይህች ዓለም የግጭት ስፍራ የሆነችው የሚሄዱበትን በማያዩ እውቀት ጠሎችና ያወቁትን በማይኖሩበት የአፍ አማኞች ነው ። ዓይን የሌለው እግር ወደ ገደል ይሄዳል ፣ እግር የሌለው ዓይን ሲመኝ ይኖራል ። 

ጌታ ሆይ ወዳሳየኸን ዕለት ዕለት መጓዝ ይሁንልን ። 

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ነሐሴ 16 ቀን 2012 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም