የትምህርቱ ርዕስ | ዘረ ቢስ ለተባልከው

“እውነተኛ የወይን ግንድ እኔ ነኝ፤ ገበሬውም አባቴ ነው ።” (ዮሐ. 15 ፡ 1)

የዘር ግንዳችን ከዚህ ይመዘዛል እያሉ ሰዎች ሲተርኩ ደስ ይላል ። በታሪክ መጻሕፍት ላይ የእርሱ ቤተሰቦች ተጠቅሰው ሲያገኝ ኩራት የሚሰማው ጥቂት አይደለም። የሚበዛው የዓለም ሕዝብ ግን የዘር ግንዱን በትክክል መናገር የሚችል አይደለም ። እስራኤላውያን በዚህ የተካኑ ናቸው ። እያንዳንዱ እስራኤላዊ ከየትኛው ነገድ መሆኑን መናገርና ወደ ኋላ መቍጠር ይችላል ። አንድን መምህር ለመቀበል የዘር ግንዱን ማወቅ ይፈልጋሉ ። አባቱንና አያቱን መናገር የማይችል በእነርሱ ዘንድ ክብር የለውም ። ቅዱስ ማቴዎስ ወንጌሉን ለአይሁዳውያን እንደ ጻፈው ይታወቃል ። ክርስቶስ የዳዊት ዘርና የዳዊት ልጅ ለመሆኑ ከዳዊትና ከአብርሃም ጀምሮ የሁለት ሺህ ዓመታት የዘር ቆጠራ አድርጓል ። ቅዱስ ሉቃስ ደግሞ ክርስቶስ የአዳም ልጅ መሆኑን ለመናገር የአምስት ሺህ አምስት መቶ ዓመታት የዘር ሐረግ ቆጠራ አካሂዷል (ማቴ. 1፡1-17፤ ሉቃ. 3፡23-38)።

ብዙ ልጆች በተለያየ ምክንያት ወላጆቻቸውን አያውቁም ። የልጅነት ጊዜያቸውን በሰላም አሳልፈው ሲያድጉ እኔ ከማን ነው የተወለድሁት ? የሚል ጥያቄ ያቀርባሉ ። በርግጥ ወላጆቻቸውን ያጡ እንጂ አሳዳጊ ያጡ አይደሉም ። ከወለደ ያሳደገ ክብሩ ትልቅ ነው ። የወለደ የእኔ የሚለውን ሲጥል ፣ ያሳደገ ግን የእኔ የማይለውን የእኔ ብሎ አሳድጓል ። እነዚህ ልጆች ወላጅ አልባ እንጂ ፈጣሪ አልባ አይደሉም ። ቢሆንም የእነዚህን ልጆች ሥነ ልቡና መጠበቅ ፣ ፍቅርን መስጠት ይገባል ። አንድ ልጅ ወላጅ ካለው የወላጁ ዕዳ ነው ፣ ከሌለው ግን የመላው ዓለም ስጦታ ነው ። የእኔ ነው የሚለው ከሌለ የእኛ ነው ማለት ነው ። በዚህ ዓለም ላይ ወላጅን ካለማወቅ በላይ እግዚአብሔርን አለማወቅ ለታላቅ ድባቴ አሳልፎ ይሰጣል ። ወላጅ ያጡ ልጆችን ማሳደግ ትልቁ አምልኮ ነው ። አምልኮ አቤት አቤት ማለት ብቻ አይደለም ። የተበተነውን መሰብሰብ ትልቅ አምልኮ ነው ። የእግዚአብሔር የአፍ ብቻ ወዳጅ ላለመሆን በጎ መሥራት ይገባል ። እንኳን እግዚአብሔር እኛም የአፍ ወዳጅ እየጠላን ነው ። በአፋቸው የሚያስተዛዝኑ ፣ በእጃቸው ምንም የማይሰጡ ባለ ዱሽ እጆች መንፈሳዊ ትዝብት ላይ የወደቁ ናቸው ። ቅዱስ ያዕቆብ በመልእክቱ፡- “ንጹሕ የሆነ ነውርም የሌለበት አምልኮ በእግዚአብሔር አብ ዘንድ ይህ ነው ፤ ወላጆች የሌላቸውን ልጆች ባልቴቶችንም በመከራቸው መጠየቅ ፥ በዓለምም ከሚገኝ እድፍ ሰውነቱን መጠበቅ ነው።” (ያዕ. 1፡ 27) ። አባት ለሌለው አባት ፣ እናት ለሌለው እናት መሆን ትልቅ አምልኮ ፣ የእግዚአብሔር ወኪል/ምስለኔ መሆን ነው ። ቆመው የሚዘምሩና የሚያዘምሩ ትልቅ አምልኮ ይህ መሆኑን ማወቅ አለባቸው ። እግዚአብሔር እጅ እግር የሌለውን ክርስትና አይወድም ። ወላጅ አልባም ፣ ሽማግሌም ብድር መመለስ የሚችሉ አይደሉም ። እውነተኛ አምልኮ ብድር መመለስ ለማይችል ቸርነት ማድረግ ነው ። ከእኩያ ጋር መገባበዝ ሳይሆን ከመከረኞች ጋር አብሮ መቍረስ እርሱ በእግዚአብሔር ፊት ንጹሕ መሥዋዕት ነው ።

ቅዱስ ዮሐንስ የንስሐ ጥምቀት ያጠምቅ ነበር ። በእርሱ ዘመንም አገሩን እንደ ወረርሽኝ የበከለው በሽታ ትዕቢት ነበር ። “በልባችሁም፡- አብርሃም አባት አለን እንደምትሉ አይምሰላችሁ ፤ እላችኋለሁና፡- ከነዚህ ድንጋዮች ለአብርሃም ልጆች ሊያስነሣለት እግዚአብሔር ይችላል” ይላቸው ነበር ። (ማቴ. 3 ፡ 9) ። የእኛ ዘመን ትምክሕት አድጓል ። ለእግዚአብሔር ከእኛ ውጭ ማን አለው ? የሚልና ሌላውን የሚንቅ የልብ ትዕቢት ውስጥ ነን ። እግዚአብሔር የሰው ድሀ የሆነ እየመሰለን ከእኛ ውጭ አማራጭ የለውም እያልን ነው ። አይሁዳውያን በልባቸው አብርሃም አባት አለን ይሉ ነበር ። የአብርሃም እውነተኛ ልጆች በሥጋ ከእርሱ የተወለዱት ሳይሆኑ በሃይማኖት የሚመስሉት ናቸው ። ሃይማኖት በዘመናት ፣ በሰማይና በምድር አንዲት ናት ። የምናምነው አብርሃም ራሱ ያመነውን ነው ፣ የምናምነው ቅዱሳን መላእክት የሚያምኑትን ነው ። በሃይማኖት አንድ ነን ። እግዚአብሔር የወደደው የአብርሃምን ሥጋዊ የዘር ሐረግ አይደለም ፣ የባረከውም እምነቱን ነው ። በአብርሃም እምነት የጸኑም የአብርሃምን በረከትይወርሳሉ ።

በጥንቱ እኔ እኮ የእገሌ ተማሪ ነኝ እያለ ተማሪው ይኮራል ። በዚህ ዘመንም ከዚህ ዩንቨርስቲ ተመርቄአለሁ ማለት ትልቅ የኩራት ምንጭ ነው ። መማር እጅግ ደስ ይላል ። አእምሮ ለማወቂያ የተሰጠን መሣሪያ ነው ። አእምሮ እውቀትን ካልሰበሰብንበት ይጎዳል ፣ ይጎዳናል ። ባዶ የሆኑ አእምሮዎች ባዶ ዓለምን ይፈጥራሉ ። ባዶነት የተጠላ ነው ። እግዚአብሔር የፈጠራት ዓለም በአእምሮ የምትመራ ናት ። አሊያ በሕገ አራዊት የበለጠ ገዳይ የበላይ ይሆንባታል ። እውቀት ግን ያልተማሩትን ለማገዝ ፣ ለምድር አስተዋጽኦ ለማድረግ እንጂ ለትምክሕት የሚሆን አይደለም ። ሁሉም አስፈላጊ ነውና ማን በማን ላይ ይኮራል ?

እነዚህ ሁሉ ትምክሕቶች እውነትነት የላቸውም ። እውነት በምድርም በሰማይም የጸናች ናት ። በእግዚአብሔር ፊት የማይቀርብን ነገር ገንዘቤ ማለት ማፈርን ያስከትላል ። በዘር ሐረጋችን ፣ በቋንቋ ጥራታችን ፣ በወላጆቻችን ትልቅነት ፣ ከፍ ባለው አስተዳደጋችን ፣ በታወቁት መምህራኖቻችን ፣ በከበረው የትምህርት ተቋማችን መመካት እውነትነት የለውም ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፡- “እውነተኛ የወይን ግንድ እኔ ነኝ ፤ ገበሬውም አባቴ ነው” አለ (ዮሐ. 15 ፡ 1) ። የዘር ሐረጋችሁን መናገር ቢያቅታችሁ ፣ ወላጆቻችሁ እነማን መሆናቸውን እንኳ በቅጡ ባታውቁ ፣ ከእገሌ መምህር የተማርኩ ነኝ ለማለት ባትበቁ አትጨነቁ ። እውነተኛው የወይን ሐረግ ክርስቶስ ነው ። ከእርሱ ጋር ለመግጠም ፣ ቅርንጫፍ ለመሆን ዛሬ ወስኑ ። በንስሐ ፣ በቅዱስ ቍርባን ከክርስቶስ ጋር ወገን ሁኑ ። የሚያኮራው ግንድ እርሱ ብቻ ነው ። አባቱን ለማያውቅ ፣ አያቱንም ለናፈቀ ክርስቶስ ትልቅ እርካታ ነው !

አንተ የአብ ልጅ ማንም የለኝም ለሚለው ሁሉን ትሆናለህ ፣ ብዙ አለኝ ለሚለው ያለኸው አንተ ብቻ ነህ ። ስመ መልካሙ ኢየሱስ ለስንቱ መልስ ነህ ! እኔም ብቸኛ ምርጫ አንተን አድርጌአለሁ ። ሲመሽ ሲነጋ የማገኝህ አንተን ብቻ ነው ። ከፍታ ዝቅታም የማያርቅህ ወዳጄ አንተ ነህ ። እስከ አዳም መቍጠር ባልችል ዘላለምን ባንተ እቆጥራለሁ ። ከሚቆጠረውና ከሚያልቀው ወደማይቆጠረው ባንተ ተሻግሬአለሁ ። አዳም ሆይ አልወቅስህም ፣ በዳግማዊ አዳም ተክሻሁ !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኮንን
ጥር 14 ቀን 2017 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም