የትምህርቱ ርዕስ | ዛሬ ና

 በውስጤ ሳለህ ብዙ ዘመን በአፍኣ ፈለግሁህ ። የወደድኸኝ አንተ እያለህ የሚወዱኝን ለማየት ዓይኔን አማተርሁ ። ቃልህን እያሰማኸኝ የሰዎችን የድምፅ ቅላፄና ቃና መረመርሁ ። በራሳቸው ጉዳይ ሲያኮርፉ በእኔ ጉዳይ መሰለኝ ። ፊትህን ገሸሽ ብዬ የፍጡራንን ፊት አሰስሁ ። ስትከተለኝ ጀርባዬን ሰጠሁህ ። ስትጠራኝ የባልንጀሮቼን ጨዋታ ወደ መስማት አዘነበልሁ ። ሞተህልኝ ሳለ በጥቂት ፍላጎቴ ጠረጠርሁህ ። ደምህን አፍስሰህልኝ ሳለ ዋጋዬን አሳንሼ ኖርሁ ። አኗኗርህ የከበረ ፣ ሳይሾሙህ የምትሾመው ንጉሥ ፣ ካንተ ፊት ቀደምሁ ፣ ካንተ ኋላ ቀረሁ የሚልህ የለምና የነግህ ምስጋና አቀርብልሃለሁ ። የጦር መሪዎች ሰማዕታት ፣ ቆነጃጅት ደናግላን ፣ ነገሥታት መናንያን ፣ ገዳዮች ሟች ፣ ተቃዋሚዎች ሐዋርያት ፣ አሳዳጆች ወንጌላውያን የሆኑልህ ሁሉን በፍቅር የረታህ አንተ ጌታዬ ነህ ። አንተ በአንድ ቀን የተቀበልከውን መከራ እኔ በሕይወት ዘመኔ በየተራ ብቀበለው ይከብደኛል ። መከራዬ በመከራህ ፊት የማይወራ ብናኝ ነው ። ወደ አገሬ ስደርስ ፣ ወደ ቤቴ ስመለስ የምትቀበለኝ ፣ በሰማይ አዳራሽ ሰርግን ፣ በመንግሥተ ሰማያት እልፍኝ መኖሪያን ያዘጋጀህልኝ የምድር ኑሮዬ ቢፈርስ ባንተ እጽናናለሁ ። ማን ይቀበለኛል ? ብዬ አልሰጋም ። በምድርም በሰማይም ያለኸው አንተ ነህ ።
ነፍሴን ከጽኑ ቊጣ በራስህ ውስጥ የሸሸግሃት ፣ በፍቅር ብርሃንም ያረጋጋሃት አንተ ነህ ። ለኃይልህ ጠፈር ፣ ለክብርህም ጉልላት የለውም ። የተሠሩ ከተሞች ሲፈርሱ ፣ ያማሩ እንዳልነበሩ ሲሆኑ ያንተ ሥራ ግን ጸንቶ ይኖራል ። ስንት አምፑል ሲቃጠል ያንተ ፀሐይ ግን ታበራለች ። ስንት እቅድ ከመንገድ ሲቀር ያንተ ወንጌል ግን ዛሬም ይሠራል ። በማጣትም በማግኘትም ነፍሳቸው የተጨነቀችባቸውን እባክህ አሳርፍ ። ነፍሶችን ለማዳን የሚሮጠውን ያንተን አገልጋይ ሩጫውን ባርክለት ። ልነቀል ፣ ልነቀል የምትለውን የምእመን ነፍስ አንተ አጽና ። ሕይወት የመረረውን አንተ አጣፍጥለት ። አሳቡ እየባከነ ማንበብ ፣ መጸለይ ያቃተውን አንተ አረጋጋው ።
የበሰለ በረከት ያለህ ፣ በሰማያዊ ማዕድም ገና የምታጠግበን ፣ ለመኖራችን ትርጉም ፣ ለሞታችንም አድራሻ የሰጠኸው ጌታ አንተ እግዚአብሔር ነህ ። እችላለሁ ብዬ ብቻዬን የተጓዝሁበት ፣ አውቀዋለሁ ብዬ መንገዱን የጀመርሁበት ፣ ጀግና ነኝ ብዬ ጦርነት ውስጥ የገባሁበት ፣ ጠቢብ ነኝ ብዬ መድረክ የፈለግሁበት ያን ሁሉ ዘመን አንተ ካሰው ። አንተ ከሌለህበት ነገር ሁሉ ባዶና አሰልቺ ነው ። እጅህን ጭነህ ባርከኝ ፣ በእፍታህም ሕይወት ዝራብኝ ። ከአፈርነት ሰው አድርገኝ ። ዕድል ፈንታዬን ከማዕድህ ከሚቆርሱት ልጆችህ አድርግልኝ ። የቡችሎችን ፍርፋሪ ገንዘብና ጤናን ብቻ መሻት ከእኔ ይራቅ ። የልጆችህን ገበታ የነፍስ መዳንን አድለኝ ።
ሰው ቢጨክን አይራራም ። አንተ ግን ብትቀጣም ትመለሳለህ ። ሰው እየለመኑት ይገድላል ። አንተ ግን የለመኑህን ታድናለህ ። በምሠራው ላይ ልትሠራ ፣ በምኖረው ሕይወት ላይ ልትኖር ዛሬ ና ። አሜን ።
የነግህ ምስጋና /5
የካቲት 19 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም