የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

የትምህርቱ ርዕስ | ዛሬ

“በውድ ልጁም እንዲያው የሰጠን የጸጋው ክብር ይመሰገን ዘንድ ይህን አደረገ ።” ኤፌ. 1 ፡ 6 ።

ክርስቶስ ውድ ልጅ ብቻ ሳይሆን ስሙም “ውዴ” የተባለ ነው ። “ውዴ የእኔ ነው ፥ እኔም የእርሱ ነኝ” መኃ. 2 ፡ 16 ። የዚህ ቅኔ አቅራቢ የታደለ ነው ። ምክንያቱም ውዴ የእኔ ነው ፣ እኔም የእርሱ ነኝ ለማለት በቅቷል ። ወደ እኛ ዘመን ብንለውጠው “ውዴ የእኔ ነው ፣ እኔ ግን የእርሱ አይደለሁም” የሚል ቅኔ ይወጣዋል ። ውዴ ማለት የሚወደኝ ፣ የምወደው ፣ የመኖሬ ምሥጢር ፣ በዚህ ዓለም ካሉኝ ነገሮች በላይ የሆነ ትርፌ ፣ ካለፈው ከሚመጣው ነገር በላይ የሆነ ደስታዬ ማለት ነው ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህን ሁሉ ነው ። እኛን በመውደዱ አይጠረጠርም ። እኛ እርሱን ለመውደድ በትግል ውስጥ ነን ። መኖር ምሥጢር ከሆነ ምሥጢሩ ክርስቶስ ነው ። እንዴት እንዳኖረን የሚያውቀው እርሱ ብቻ ነው ። መንገዱ ሁሉ እግር እግር የሚያይ እባብና ጊንጥ ፣ ሕያው እንቅፋት ባለበት ዓለም ላይ ዛሬን ማየት ተአምር ነው ። በዚህ ዓለም ያለው ነገር ሳይነጋ የሚጨልም ፣ ሳይጀመር የሚያልቅ ነው ። ደስታው ፍጹምነትና ዕድሜ እያጣ በአንድ ዓይን እየሳቁ በአንድ ዓይን እያለቀሱ የሚኖሩበት ዓለም ነው ። ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ ግን የዕንባውን ክረምት የምንወጣበት ደስታችን ነው ። ጥያቄ መልሱን ሲናፍቅ መልሱ ጥያቄ በሚሆንበት ዓለም ላይ ፣ እየተራቡ ማልቀስ አልፎ እየበሉ ማንባት በሚቀጥልበት ምድር ውስጥ ከእርሱ በቀር ለልብ ድጋፍ የሚሆን ፣ የነፍስን ማዕበል ገሥጾ ሰላም የሚሰጥ የለም ።

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የአባቱ ውድ ልጅ ነው ። እርሱ የአማንያንም ውድ ነው ። እርሱ ውዴ ተብሎ የሚጠራ ነው ። ውድ የተወደደ ፣ ከፍ ያለ ፣ የከበረ ፣ ሕይወት የሚሰጡለት ነው ። እግዚአብሔር አብ ለዓለም የሰጠው ውድ ልጁን ነው ። ላገኘናቸው ስጦታዎች ሁሉ መሠረቱ ክርስቶስ እንጂ የእኛ መልካምነት አይደለም ። ወደ ዓለም ያመጣው የእኛ ጽድቅ ሳይሆን በተቃራኒው ኃጢአታችን ነው ። ዲያብሎስ አሳተን እንጂ ኃጢአተኛ አላደረገንም ። ኃጢአተኛ ያደረገን ምርጫችን ነው ። እኛ ብቻ ሳይሆን የምንኖርባት ምድር ተረግማ ሳለ የእኛን ሥጋ በመልበስ ፣ የእኛን ምድር በመርገጥ ሊቀድሰን መጣ ። ነገረ ሥጋዌ ሰው ለእግዚአብሔር ያለውን ፍቅር ሳይሆን እግዚአብሔር ለሰው ያለውን ፍቅር አመልካች ነው ። ትእዛዛት እንደማይገዙን ፣ ፍቅርም እንደማያሸንፈን ቢያውቅም ትእዛዛቱን የፍቅሩ መገለጫ ፣ ሞቱንም የፍቅሩ ፍጻሜ አድርጎ ለዓለም ገለጠ ። መስፈርት ከመጣ ልንወደድ የማንችል ፣ መንገድ የምንቀር ፣ ሚዛን የማንሞላ ነን ። እንዲያው በሚለው መስፈርት በከንቱ ፣ ያለ መለኪያ አዳነን ።

እንዲያው ሲል ርካሽ ማለት አይደለም ። እንዲያው ሲልም ምላሽ የማይሻ ማለት አይደለም ። አዳም በገነት አንዲት ሕግ ተሰጠችው ፣ በአዲስ ኪዳን ደግሞ አንዲት እምነት ተሰጠች ። ዕፀ በለስን አትብላ በሚል ሕግ የወደቀው የሰው ልጅ ኅብስተ ሕይወት ክርስቶስን ብላ የሚል እምነት ተሰጠው ። ላለ መብላት መታዘዝ ፣ ለመብላትም እምነት ያስፈልጋል ። የሰው ልጅ አትብላ ተብሎ በመብላቱ ሕግ አፍራሽ ሆነ ። ብላ ተብሎ ባለመብላቱ ኢአማኒ ሆነ ።

ጸጋው በሙላት የፈሰሰው እንዲሁ አይደለም ። በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ነው ። ጸጋ ተራ ነገር አይደለም ። ክብር ያለው ነው ። መጣያ ጠፍቶ የተሰጠ አይደለም ፣ የወደቀውን የሚያነሣ አቅም ነው ። ለጉራም የተቸረ አይደለም ፣ የፍቅር ማብራሪያ ነው ። በአደባባይ ቢሰጥም በልባችን ጓዳ የምንቀበለው ነው ። ጸጋው የቁሳቁስና የምድራዊ ነገሮች ስብስብ አይደለም ። ክርስትና የሕይወት እንጂ የቁሳቁስ ዋስትና መስጠት ባሕርይው አይደለም ። ጸጋው ክብር ያለው ነው ። ጸጋው ክብር ሊሰጠው የሚገባም ነው ። ስጦታ ሰጪውን የሚያስደስተው ተቀባዩንም የሚጠቅመው አክብረው ሲወስዱት ነው ። እግዚአብሔር ባለ ጸጋ ሳለ ራሱን የሰጠበት ፣ እግዚአብሔር ከእግዚአብሔርነቱ ጋር እኛን ያስማማበት ምሥጢር ትልቅ ነው ።

ይህን ጸጋ ባለን ንብረት ልንገዛው ፣ ብድርም ልንመልስ አንችልም ። የጸጋውንም ክብር ግን ማመስገን ያስፈልገናል ። ዝማሬአችን ነገረ ድኅነትን ፣ ስብከታችንም ነገረ መስቀሉን ማዕከል ማድረግ ያስፈልገዋል ። በአሁንነት ከልደቱ እስከ ሞቱ ያለውን ክንውን ማሰብ እርሱ እምነት ይባላል ። እምነት አሁን ነውና ። በልደቱ “ቤዛ ኩሉ ዓለም ዮም ተወልደ ፣ የዓለም ሁሉ ቤዛ ዛሬ ተወለደ” እያለች ቤተ ክርስቲያን የምትዘምረው እምነት አሁን ስለሆነ ነው ። ሥርዓተ ቅዳሴም ቀራንዮን ዛሬ የሚያደርግ ፣ ትኩስ መሥዋዕት የሚቀርብበት ነው ። ታሪክ ለመዘከር የምትቀድስ ቤተ ክርስቲያን ሳትሆን ዕለተ ዓርብን ዛሬ አድርጋ ፣ በእግረ ሕሊና ቀራንዮና ሰማይ አማኞቿን የምትወስድ ሕያዊት ቤተ ክርስቲያን ናት ።

የኤፌሶን መልእክት ትርጓሜ /13

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 23 ቀን 2014 ዓ.ም.

እባካችሁ ለሌሎች አካፍሉት

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም