“አቤቱ ፥ የሆነብንን አስብ ተመልከት ስድባችንንም እይ ።” ሰቆ. 5፡1።
እውነት ከያዘው ፣ ስሜት የወዘወዘው በበዛበት ፣ ጥቅስ የሕይወት ፈርጥ ሳይሆን የግድግዳ ጌጥ በሆነበት ፣ አቋም በአቋቋም በተተካበት ፣ የገባውና የገባው የመሰለው በማይለይበት ፣ እጅ ለድሀ ለመቸር እየሰሰተ ፣ አፍ ጮማ በሚቆርጥበት ፣ ጆሮ የሰማውን መቋቋም አቅቶት ሌላ ጉድ በሚናፍቅበት ፣ የወደቁ በወደቁት በሚስቁበት ፣ አገር ከጽንፍ እስከ ጽንፍ በከሸፈበት ፣ ያቀፈ እየነቀፈ ባስቸገረበት ፣ ምላስ ልብን ለመደለል በሚሞክርበት ፣ ቃለ ሰብእ እና ቃለ እግዚአብሔር በተቀላቀሉበት ፣ በቅብዐት የተሾሙ በብረት በትር በሚገዙበት ፤ ቂም በዓለት ላይ ፣ ፍቅር በአሸዋ ላይ በሚጻፍበት ፣ ጉዳይን ከመፍታት ባለ ጉዳይ በሚገደልበት ፤ ባለ መድኃኒት ገዳይ ፣ ዳኛ ወንጀለኛ በሆኑበት ፣ መብል በሽታ ሁኖ ፣ በሽታም ፈውስ ባጣበት በእኛ ዘመን አቤቱ በመልካም አስበን ።
በአደባባይ ጅራፍ የምንገረፈውን ፣ በማይደበቅ ጦርነትና ረሀብ የክፉ ምሳሌ የሆነውን አቤቱ ስድባችንን ተመልከት ። ከሰውነታችን ገንዘባችን በሚፈለግበት ፣ ከእኛነታችን ይልቅ የአንድ እንስሳ ዋጋ በበለጠበት ፣ ጽጌረዳ አበባ ዙፋን ላይ ወጥታ ሰው እንደ ጥራጊ በሚደፋበት ምድር ላይ አቤቱ የሆነብንን አስብ ። እያሸበርን አሸባሪ የምንፈራውን ፣ እየገደልን እገሌ አገር ገዳይ ነው የምንለውን ግብዞች አቤቱ በፍቅርህ አስበን ። የሚያድነውን ንስሐ እባክህ አሳየን ። ሰውን ሰው ባደረገው ምሕረትህ ለዘላለሙ አሜን!
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 17 ቀን 2015 ዓ.ም.