መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት (15)

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት (15)

12- የመጣህበትን አትርሳ

ሕይወት መንገድ ነው ። መንገድ የመጣንበት ደግሞም የምንሄድበት ነው ። ሀብት ቢነጥፍ ፣ ጉልበት ቢከዳ ፣ ወዳጅ ጠላት ቢሆን ሕይወት ይቀጥላል ። ሁሉም ሰው የራሱ የሆነ ሕይወት አለው ። በእግዚአብሔር ፈቃድ የጀመረች ሕይወቱ በእርሱ ፈቃድ ትቆማለች ። ከበሽታ የተነሣ ቢመረር ፣ ከማጣት የተነሣ ቢያለቅስ ፣ ከወዳጅ ሞት የተነሣ ቢከፋው ሕይወት ትቀጥላለች ። አቀባበሉ ግን ቀጣዩን ብርሃን ወይም ጨለማ ያደርገዋል ። በአንድ ዓይነት መከራ ውስጥ የሚያልፉ ሁለት ሰዎች አንዱ ቢስቅ ሌላው ቢያለቅስ ጉዳዩ የአቀባበል ነው ። አቀባበሉ ያቀለዋል አሊያም ያከብደዋል ። ያመንነውን እንወርሳለንና “ይህ ክፉ ነገር ለበጎ ነው የመጣው” ስንል በጎ ይሆናል ። አቀባበል ጨለማውን ብርሃን ያደርጋል ። መንገድ ከፍታም ዝቅታም አለው ። ሕይወት መንገድ ናትና የክብር ዘመን እንዳለ ሁሉ የውርደት ዘመንም አለ ። አልጫ አልጫ የሚል ቃል ተናግረን እንደ ጥቅስ የሚነገርበት ዘመን አለ ። የጥበብ ቃል ተናግረን “ምነው ሞቶ ባረፈው” የምንባልበት ዘመን አለ ። አንዳንድ ሁኔታዎች መታገል ሳይሆን መታደል የሚያመጣቸው ሊሆኑ ይችላሉ ።

ተራራ የወጣው መንገደኛ ቁልቁለት እንደሚወርድ እርግጠኛ ነው ። ከተራራ ቀጥሎ ተራራ አይመጣምና ። የከበረም መዋረዱ አይቀርም ። “ፖለቲከኛና አትሌት በቃህ ካልተባሉ አያቆሙም” ይባላል ። እንደ ከበሩ ዞር ማለት ትልቅ ጥበብ ነው ። ከሐር መነሳንስ ወደ ጭቃ ጅራፍ ሳይለወጥ ዞር ማለት አዋቂነት ነው ። ይልቁንም በአገራችን ወረት በዙፋን ተቀምጦ እየገዛን ይመስላል ። “አንቱ” ያልነውን ሰውዬ “አንተ” ለማለት እንቸኩላለን ። መንገድ ተመዝማዛ ነው ። ቀጣዩ አልታይ እያለን የምንጨነቅበት ፣ ተስፋ ዘይቱ እንዳለቀ መቅረዝ ጭል ፣ ጭል የሚልበት ጊዜ ጥቂት አይደለም ። ተስፋ መቍረጥም የሕይወት አንድ አካል ነው ። ያልገባን ነገር ቢኖርም “እግዚአብሔር አዋቂ ነው” ማለት ያሳርፋል ። “እግዚአብሔር አዋቂ ነው” ማለት “እግዚአብሔር ያውቅልኛል” ማለት ነው ። መንገድ ሸካራ ነው ። ውስጣችን በሰዎች ክፋት የሚበከልበት ፣ ጥርጣሬ ቀናችንን የሚዋጋበት ጊዜ ብዙ ነው ። ሰዎችን ይቅር ለማለት ከራሳችን ጋር ግብ ግብ ውስጥ የምንገባበት ፣ ቂመኝነትን ዳግም ላለመጎዳት የሚጋረድ ጋሻ አድርገን የምንመለከትበት ጊዜ አያሌ ነው ። “ተበድዬስ ይቅር አልልም” እያልን እንዘፍናለን ። ይቅር የምንለውማ ስንበደል ነው ። ፍቅር የመበደል አጥር ሲሻገር እውነተኛ ይሆናል ።

ሕይወት መንገድ ነው ። መንገድ መነሻ አለው ፣ መንገድ መድረሻ አለው ። እግዚአብሔርን ማመን ያስፈለገን መነሻና መድረሻ ያለው ሕይወት ለመያዝ ነው ። እግዚአብሔርን ካላመንን ሕይወታችን መነሻና መድረሻ የሌላት ፣ መሐል ባሕር ላይ ያለ መቅዘፊያ የተለቀቀች ጀልባ ትሆናለች ። የመጣንበት የምንሄድበትን ይወስነዋል ። የመጣንበትን በትክክል ማሰብ ከቻልን ምስጋና በአፋችን ይሞላል ። ሰውን መበደል እንጸየፋለን ። ሌሎችን ለመርዳት እንነሣሣለን ። መካሪ ሁነን አዲስ ትውልድን እናበረታታለን ። ግፍን እንጸየፋለን ። ማንንም አንንቅም ። አዎ ሕፃናት ነበርን ። ሕፃናትን መውደድና ማክበር አለብን ። አዎ ዕራቁታችንን ተወልደናል ። ስለዚህ ድሀ ነበርኩ ማለት የሚያሳፍር አይደለም ። ያለ ፍትሕ ታስረናል ። ስለዚህ ያለ ፍትሕ ሌሎችን መጉዳት አይገባንም ። አንድ ድቃቂ ሣንቲም ሊቸግር እንደሚችል ኑሮአችን ምስክር ነው ። የመጣንበትን ብናስብ እጆቻችን ለመርዳት ይዘረጉ ነበር ።

አዎ የመጣህበትን አትርሳ ። የመጣኸው ካፈር ነው ። አንድ ቀን ወደ አፈር ትመለሳለህና ኩራትን ተው ። ፊደል ለማወቅ ብዙ ወራት የፈጀብህ ፣ በብዙ ጥረት አዋቂ የሆንህ ፣ የብዙዎችን ጉልበት የጨረስህ ነህና ሰውን “ደንቆሮ” ብለህ ለመሳደብ አትድፈር ። ዕድሉን ቢያገኝ ሁሉም ሊቅ ይሆን ነበር ። ያደግህበት ሰፈር ዛሬ ካየሃቸው ውብ ከተሞች የሚበልጥ ትዝታ ያለው ነውና ያደግክበትን ቀዬ ዞር ብለህ ተመልከት ። ያሳደጉህ እናቶች ፣ ዛሬም ረሀብ ዘመድ ሆኖ አልላቀቅ ያላቸው የአባትህና የእናትህ ጓደኞች አሉና ሄደህ ጠይቃቸው ፣ ካለህ ላይ አካፍላቸው ። ትንሹ ማሙሽ አድገህ ለመስጠት በመብቃትህ ፈጣሪያቸውን ባንተ ምክንያት ያመስግኑት ። መምህራኖችህ ዛሬ ከእነርሱ የበለጠ እውቀት ብትይዝም የወጣህባቸው መሰላል ናቸውና አክብራቸው ። ዋጋቸውንም ሂደህ ንገራቸው ። የወጣህበት መሰላል ለመውረድም ይረዳልና ወጣሁ ብለህ ገፍተህ አትጣለው ። አንተን አንቱ ያሰኘህ ሕዝብ ነውና ሕዝብህን አትናቅ ። ሕዝብ ያንተ ሎሌ ሳይሆን አንተ የሕዝብ አሽከር መሆንህን እመን ። የሥልጣን በትር አንድ ቀን ከእጅ ያመልጣል ። የደጁን ስትገፋ ልጅህ እንደ አቤሴሎም ለሞት ይፈልግሃል ። ሥልጣን ፀሐይ ነው ። ምንም ቢደምቅ መጥለቁ አይቀርም ። አዎ የድሀ ልጅ ነበርህና የመጣህበትን አትርሳ ። በማጣት ዘመንህ ፣ በእስር ወራትህ የገባኸውን ቃል ኪዳን አትዘንጋ ። ዛሬ ሽቱ ስለተቀባህ ሰው ሁሉ የሚሸት መስሎህ አትጸየፈው ። የአንድ ቀን ውኃ ስታጣ አንተም ለመበላሸት ቅርብ ነህ ። የመጣህበትን አትርሳ ። ይህችን ከተማ ስትቀላቀል የነበረህን መደናገር አትዘንጋ ። ስለዚህ ማንንም መጤ ብለህ አትናገር ። ሁሉም ሰው መጤ ነው ። አንድ ቀን ይሄዳል ። በዚህ ዓለም ላይ መሰንበት እንጂ መቅረት የለም ።

የመጣህበትን አትርሳ ። እግዚአብሔር ብቻውን አስተማረኝ ብለህ ያስተማሩህን አትካድ ። እግዚአብሔር ብቻውን ረዳኝ በሚል ዘይቤ የሰውን ውለታ አታጥፋ ። የእናቴን ጡት አልጠባሁም ፣ የማንም ውለታ አላለፈብኝም ብለህ አትገበዝ ። ያልተቀበልከው ምንም ነገር የለም ። ከተቀበልህም የምትመካበት አንዳች ነገር የለህም (1ቆሮ. 4 ፡ 7) ። የዛሬ ስኬትህ የሁልጊዜ ስኬት አይደለምና እንዳረጀ ወዳጅ በበላህበት ቤት ጓሮ አትለፍ ። እንደ ጎርፍ በመንገድ ያገኘኸውን ተሸክመህ አትጓዝ ። አንገት የተሠራው ለጌጥ ሳይሆን ዞሮ ለማየት ነው ። ከስንት ሞት አምልጠህ ፣ የወዳጅህን ሞት አትመኝ ። ካልጨመሩበት ይቀንሳልና ወዳጅህን ወዳጅ አገኘሁ ብለህ አትግፋው ። ወረት የሰይጣን ልጅ ያደርጋል ። እወድሃለሁ ያለህ ሁሉ አይወድህምና ወላጆችህን አትግፋ ። “የወረት ውሻ ስሟ ወለተ ጴጥሮስ ነው” ይባላል ። እፍ ለማንደድ ፣ እፍ ለማጥፋት ነውና ዛሬ ካገኘኸው ጋር እፍ አትበል ። የፊት ወዳጅህን ጨርሰህ ክፉ ነው አትበል ፣ የኋላው ይታዘብሃል ። አዎ የመጣህበትን ታውቀዋለህ የመጣህበትን አትርሳ ። የመጣህበት ሲጠፋህ የምትሄድበት ይጠፋሃል ። ወዳጅ በብር አይለወጥም ፣ ወዳጅ ውድ ነው ፣ በወርቅ አይለወጥም !

ከወዳጅህ ጋር ለማርጀት ያብቃህ !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሚያዝያ 17 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም