መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት (24)

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት (24)

14. ንግግርህ ብቁ ይሁን (ቀ)

18. አትፎክር

አንድ ሰው በእግዚአብሔር ሲያምን በዘመድ ፣ በሥልጣን ፣ በጉልበት ይፎክር እንደሆነ ወዲያው “በኃይለ እግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ” ይላል ። ሠራዊትም ሠረገላም ፣ የአየር ኃይል የምድር ታንክ እንደማያድን በቀይ ባሕር የሰጠመው ፈርዖን ፣ ሰባት ዓመት ሣር የጋጠው ናቡከደነፆር ፣ ዓለምን አስገብሮ በዕድሜ ድህነት በ32 ዓመቱ የሞተው ታላቁ እስክንድር ምስክሮች ናቸው ። የማይናወጥ የሥላሴ መንግሥት ብቻ ነው ። ስመጥሮቹ ስማቸው ጠፋ ፣ ነጭ ልብሳቸው አስታብዮአቸው መሬት ለመርገጥ ይጸየፉ የነበሩ ጭቃ ሆኑ ። የድሀ ልጅ ብለው ይሳደቡ የነበሩ ዕራቁታቸውን ወደ መቃብር ወረዱ ። ሀብትም ፣ ሥልጣንም ፣ ዝናም ፣ ከበሬታም አያድንም ። የሚያድነው በችንካር ብዕር ፣ በደሙ ቀለም ፣ በሥጋው ሰሌዳ ፣ በቃልነቱ ንባብ ቀራንዮ የተነበበው የእግዚአብሔር ፍቅር ብቻ ነው ።

ፉከራ የትምክሕት ልጅ ነው ። የተፈቀደ ትምክሕት አለ ። በእግዚአብሔር መመካት ተፈቅዷል። ያልተፈቀደው ፉክራ ሌላውን ለማሳነስ ፣ ለማስጨነቅ ፣ አፍ እያለው ዲዳ ፣ እግር እያለው ሽባ ለማድረግ የሚሞክር ነው ። ትልቅ ሃይማኖት አለኝ ፣ እርሱም ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ነው ። ቢመኩበት የሚያስመካ ነው ። ተዋሕዶ ምሥጢር ነው ። እኛ ኢየሱስን የተዋሐድን እንጂ የተቀበልን አይደለንም ። መቀበል ጅማሮ ፣ በአፍአ ያለ ግንኙነት ነው ። መዋሐድ ግን ክርስቶስ በእኛ ፣ እኛ በክርስቶስ ውስጥ መሆናችን ነው ። ታዲያ ሃይማኖታችን የምንኖረው እንጂ የምንፎክርበት አይደለም ። ሃይማኖተኛ በወንድሙ መጥፋት ያዝናል ፤ ፎካሪ ግን በውድቀቱ ይደስታል ። ሃይማኖተኛ “ምነው እኔ የቀመስኩትን ወንድሜ በቀመሰ” ይላል ፣ ፎካሪ ግን እኔ ከቆምሁበት አትቆምም ብሎ ጦር ይወዘውዛል ። ዛሬ ብዙ ፎካሪ ስላተረፍን ንስሐ ገብቶ የሚመለስ ቢመጣ እንኳ ደግመህ ውጣ እንለዋለን ።

ብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደ ሥላሴ “ለልጅ ምክር ለአባት መታሰቢያ” በተሰኘው መጽሐፋቸው፡-

ልጄ ሆይ ! ለእኔ ለአባትህ እንደ መሰለኝ ከመጻሕፍት ሁሉ ወንጌል ትበልጣለች።
ይህንም ማለቴ አንተ በወንጌል ተምረህ ክርስቲያን ሆነህ እንድትኖር ብዬ ነው እንጂ ፤ የእኔ ሃይማኖት ይበልጣል የእኔ መጽሐፍ ወንጌል ትበልጣለች እያልህ ክርክርን ከሚወዱ ሰዎች እንድትከራከር ብዬ አይደለም” ብለዋል ።

ፉከራ የጦርነት የመጋደል ዋዜማ ላይ የሚሰማ ንግግርና ዜማ ነው ። ንግግር በፉከራ የሚቃኝበት ጊዜ አለ ። ፉከራ ዛቻ ፣ ማስፈራሪያ ያለው ነው ። በትዳር ፣ በወዳጅነት ውስጥ እየፎከረ የሚኖር ሰው አያሌ ነው ። ፎካሪ ደመ ሙቅ ቢሆንም ሌላውን ግን ይጎዳል ። ፎካሪን ሰው መልመድ ከባድ ነው ። ፉከራ ያለማድረግ ወንድም ነው ። የሚፎክር ሰው ስለማያደርግ በመጨረሻ እየተናቀ ይመጣል ። ውስጣዊ ኃይላችን የሚባክነው በዋናነት በአንደበታችን ነው ። የምናደርገውን መናገር ፣ ያደረግነውንም መናገር ተገቢ አይደለም ። ሰባኪ አዋጅ ነጋሪ እንጂ ፎካሪ አይደለም ። አዋጅ አትሳሳቱ የሚል ማስጠንቀቂያ ነው ፤ ፉከራ ግን “ምነው በተሳሳተና በዘመትኩበት” ባይ ነው ። የሃይማኖት አቀበትን ፎካሪዎች አይወጧትም ፣ ጸሎተኞች ግን ይወጡአታል ።

መዝሙሩ ወደ ፉከራ ከተለወጠ አምልኮ መሆኑ ይቀራል ። መዝሙር ወደ ላይ የሚያርግ ሲሆን ፉከራ ግን ወደ ጎን የሚምዘገዘግ ወንድምን ሰባሪ ዘንግ ነው ። ዛሬ አንዳንድ መዝሙር ፣ አንዳንድ ቅኔ ስንሰማ ብሽሽቅ ፣ ለጠላነው ሰው የአደባባይ ደብዳቤ መላላኪያ ይመስላል ። ራስን መግዛት ከሌለ ፣ ሰው በመዝሙርም እንኳ ይወራረፋል ። ሰባኪውም በቅዱስ ፍርሃት ፣ በሥላሴ ትምክሕት መቆምና መስበክ አለበት ። ያናደደውን ሰው ለመንቆር መቆም ክብርን ያሳንሳል ። በርግጥ ሰባኪ ሰው ነውና ስሜት አለው ፣ እግዚአብሔር በውጣ-ውረድ ውስጥ ካስተማረው ላይ የሚያስተምር መሆኑን መርሳት አይገባንም ።

ፉከራ አገር ሲወረር ፣ ድንበር ሲደፈር ፣ ሥርዓተ መንግሥት ሲናቅ ወንዱን ሴቱን ለማጀገን ታሪክን ማንነትን ጠቅሶ ማነቃቃት የተለመደ ባሕላችን ነው ። በኑሮ ላይ ደግሞም በወንድም ላይ ፉከራ ግን ከፍቅር መጉደል ነው ። ከፉከራው ትንሽ ላሰማህ፡-

ቢብለጨለጩ እንደ ቅቤ ቅል ፣
መተኮስና መምታት ለየቅል ፤
ቢብለጨለጩ በልብስ በጫማ ፣
ሊፈረጥጡ ድምፄ ሲሰማ ።

እምቢ!!!

በለው በለውና አሳጣው መድረሻ ፣
ማዕረግ አያውቅም ወንበዴና ውሻ ፤
ያመጣል መንገድ ይወስዳል መንገድ ፣
አንድ የሚጠላ አንድ የሚወደድ ፤
ሀገር አስነካሽ ልጅ አይወለድ ።

ስንፎክር ሌላውን እናሳንሳለን ። በእግዚአብሔር ሳይሆን በራሳችንና በልምዳችን መመካት እንጀምራለን ። ጸሎት እናቆማለን ፣ ሰልፋችን ሥጋዊ ይሆንና ሰይፍ መምዘዝ እንጀምራለን ። ይህ በሐዋርያው ጴጥሮስ የታየ ነው ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ግንቦት 12 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም