የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

የሕይወት ሥነ ሥርዓት (25)

13. ንግግርህ ብቁ ይሁን (በ)

20. ኃይለ ቃል አትጠቀም

“እፍ ያነዳል ፣ እፍ ያጠፋል” ይባላል ። እሳቱን የምናቀጣጥለው እፍ በማለት ሲሆን የምናጠፋውም እፍ በማለት ነው ። ንግግር የተኛውን በሬ ቀስቅሶ አውሬ ያደርገዋል ፣ በተቃራኒው ንግግር የተመዘዘ ሰይፍን ወደ አፎቱ ይመልሳል ። ናባል ያነደደውን እሳት ፣ አቢግያ አጠፋችው (1ሳሙ. 25)። እፍ ያነደደውን እፍ ባያጠፋው ኖሮ ዳዊት የብዙ ንጹሐንን ደም ያፈስስ ነበር ። አቢግያን የመሰለች የኋላ ሚስቱንም ይገድል ነበር ። ባለጌዎች የሚኖሩት እጅግ መልካም በሆኑ ሰዎች መካከል ነው ። ባለጌውን ላጥፋ ስንል ብዙ መልካሞችን እናጠፋለን ። አንዳንዴ ስለምጣዱ አይጧ ትለፍ ትክክለኛ መርሕ ይሆናል ፤ ባለጌዎች ይህን ስለሚያውቁ ጨዋውን ወገን ይጠጋሉ ። ጨዋ ሰውን የሚያስተዋውቀን ባለጌ ነው ። ባለጌ እንኳ የሚፈራው ባለጌን ነው ። ባለጌው ስለሚያውቅበት ፣ ከእርሱ የባሰ ክፉ ምላሽ ስለሚሰጠው ባለጌ ባለጌን ይሸሻል ። እጅግ ነውረኛ የሚባሉ ሰዎች የሚያገቡት ሚስት በጣም መልካም ሴትን ነው ። ጨካኝ ነገሥታት ሚስቶቻቸው ጸሎተኛ ፣ ግፍን የሚፈሩ ነበሩ ። ናባል እፍ ብሎ ያነደደውም አቢግያ ባታጠፋው ኖሮ የዳዊት የወደፊት ዘመኑ በጸጸት የተሞላ ይሆን ነበር ። ናባልና አቢግያ ባልና ሚስት ነበሩ ። እሳትና ውኃ አንድ ላይ አደሩ ። እስከ ዕለተ ሞቱ የአቢግያ ጠባይ ናባልን አለወጠውም ፣ እስከ ዕለተ ሞትዋ የናባል ጠባይ አቢግያን አለወጣትም ። እንደ ውኃና ዘይት ሳይዋሐዱ አብረው የኖሩ ነበሩ ።

ባልና ሚስት ብዙ ጊዜ በሥጋ ይዋሐዳል ፤ በነፍስና በመንፈስ ግን ሳይዋሐዱ እስከ ዕለተ ሞት ይዘልቃሉ ፣ ግማሽ ጋብቻ ማለት ይህ ነው ። የሥጋ ውሕደት የባልና የሚስት ነው ። ይህ ከባልና ሚስት ውጭ ለማንም አይፈቀድም ። የነፍስ ተዋሕዶ የአሳብ መግባባት ፣ የመንፈስ ተዋሕዶ በአምልኮተ እግዚአብሔር አንድ መሆን ነው ። ይህ የነፍስና የመንፈስ አንድነት ከሰው ዘር ሁሉ ጋር ሊሆን የሚገባው ነው ። የሰሎሞን ልጅ ሮብዓም ለእስራኤል መከፋፈል ምክንያት የሆነው በኃይለኛ ንግግሩ ነው (1ነገሥ. 12)። ሕዝቡን በእውነት ብቻ አይደለም ፣ ቢሸነግለውም ለጊዜው እስራኤል ለሁለት ከመከፈልና ከማነስ ይድኑ ነበር ። መከፋፈሎችና የአገር መሰንጠቆች የሚገጥሙት በኃይለ ቃል ነው ። ቃል ረቂቅ ሲሆን ግዙፉን አገር ማፍረስ አቅም አለው ። ይልቁንም በነገሥታት አንደበት የሚወጣው ኃይለ ቃል ፣ ቃል ብቻ ሳይሆን አንቀጽም ፣ ሕግም ሆኖ ለብዙዎች መነሣትና መውደቅ ምክንያት ይሆናል ። የብዙ ትዳር መራበሽ ምክንያት ኃይለ ቃል ነው ። ሰው አንደበቱን መግዛት ከቻለ ሌላው ኃጢአት ቀላል ነው ። አንደበታችንን ስንገዛ ዝሙትም ስርቆትም እየደከሙ ይመጣሉ ።

አንዳንድ ሰዎች ድንገት እንደሚባርቅ መሣሪያ ኃይለ ቃል ያወጣሉ ፣ መልሰው ሲጸጸቱ ይኖራሉ ። መሣሪያ የሚባርቀው መጠበቂያው ካልተዘጋ ነው ። ነቢዩ፡- “አቤቱ ፥ ለአፌ ጠባቂ አኑር” ያለው ለዚህ ነው ። (መዝ. 140 ፡ 3።) ተፈጥሮአቸው እንደ ግስላ ፣ እሳት የሆነ ፍቅራቸውንም ጠባቸውንም የሚገልጡት በኃይለ ቃል ነው ። በአካባቢ ፣ በአስተዳደግ ፣ በሃይማኖት ሰዎች ቍጠኛ ሊሆኑ ይችላሉ ። ከተቆጣ ልብ ውስጥ ኃይለ ቃል ይወጣል ። በውስጣቸው ፍርሃት ያለባቸው ሰዎች ፍርሃታቸው በሰዎች ታውቆ እንዳይናቁ በቍጠኝነትና በኃይለ ቃል ራሳቸውን ለመሸፈን ሙከራ ያደርጋሉ ። ሰው ሁሉ ሲርድላቸው የነገሡ የሚመስላቸው ሰዎች ኃይለ ቃል መናገር ይወዳሉ ። በደጅ ኃይለ ቃልን ሲያስተናግዱ መልስ ለመስጠት የሚፈሩ ቤታቸው ሲደርሱ ኃይለኛ ይሆናሉ ። ሰውዬው ማንን ታሸንፋለህ ? ቢሉት ሚስቴን አለ ይባላል ። የበላይ አለቆችን ቍጣ በሥር ሠራተኞች ላይ የሚገልጡ ብዙ ኃላፊዎች አሉ ። ግን ስሙም “ኃላፊ” ነውና እንደሚያልፉ አውቀው ዝቅ ማለት ይገባል ። የመውጣት ሁሉ መጨረሻው መውረድ ነው ። አንድ ቀን የረገጡት ሕዝብ እጅ ላይ ይወድቃሉ ። በሌላ በኩል በራሳቸው የሚናደዱ ለመለወጥ አቅም ያጡ ሰዎች ቍጡና ኃይለ ቃል የሚያወጡ ይሆናሉ ።

አንተ ግን ኃይለ ቃል አትጠቀም ። የመናገርህ ዓላማ ለመግባባት እንጂ ለመባላት መሆን የለበትም ። “ምክርና ቡጢ ለሰጪ ቀላል ነው” እንዲሉ ኃይለ ቃልህ ልጆችህን የሕሊና እስረኛ ሊያደርጋቸው ፣ ትዳርህን ጨለማ ውስጥ ሊከተው ይችላል ። ኃይለ ቃልህ አገር ሊያፈርስ ፣ ቤተ ክርስቲያንን አደጋ ላይ ሊጥል ይችላል ። በዚህ ዘመን ባለሥልጣኖች እንደ ወንደ ላጤ ይናገራሉ ፣ ወንደ ላጤው ደግሞ እንደ መንግሥት ያወራል ። በዚህ ምክንያት ተከታዩ ሕዝብ መሪ ያደረገው ራሳቸውን የማይመሩ አላዋቂዎችን ነው ። “አውራ ዶሮ ራሱ ሳይነቃ ሰው አያነቃም” ይባላል ። ሳይነቁ የሚያነቁ ሰዎችን ሕዝብ እየተከተለ ይገኛል ። ንጉሥ እንደ አባት መናገር አለበት ። ዜጋም እንደ ዜጋነቱ መናገር አለበት ። ኃይለ ቃል ፣ ኃይለ ቃልን ይወልዳል ። ዘር ነውና ዓመፅን ያበቅላል ። ብሽሽቅን ፣ ፌዝን ፣ ጦርንና ጠብን እየወለደ ይመጣል ። ስለዚህ ስትናገር ኃይለ ቃል አትጠቀም ። እውነት ያለ ቍጣ ብቻዋን ኃያል ናት ። በዓለም ላይ ለማሸነፍ ከፈለግህ ተሸነፍ ፣ ለመሸነፍ ከፈለግህ አሸንፍ የሚባለው ለዚህ ነው ። ይልቁንም አንተ ስለተቆጣህ ሰው ኃጢአት ትቶ ጽድቅን አያደርግምና ሰባኪ ስትሆን አትቆጣ ። እግዚአብሔር የሚያፈቅርለት እንጂ የሚናደድለት አገልጋይ አይፈልግም ። “የሰው ቍጣ የእግዚአብሔርን ጽድቅ አይሠራምና።” (ያዕ. 1 ፡ 20) ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ግንቦት 16 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ