መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት (31)

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት (31)

16. ዜማ

ዜማ በሰው ነፍስ ውስጥ የተቀመጠ ጥልቅ ፍላጎት ነው ። ዜማ ምድራዊውን ሰው ሰማያዊ የሚያደርግ ነው ። የነፍስ ሀልዎት መገለጫ ነው ። ነፍስ ስትታደስ ሥጋም አብሮ እንደሚታደስ ዜማ ይነግረናል ። ዜማ ሰዎችና እንስሳት የሚካፈሉት የጋራ ፍላጎት ነው ። ዜማ ሲሰሙ አደገኛ የሚባሉ አራዊት ይመሰጣሉ ። ዜማ ጨካኙን የማራራት አቅም አለው ። ቀሳውስት ቸገረኝ እንጂ ጨነቀኝ ሲሉ አይሰማም ። ጭንቀትም በጉልህ አይታይባቸውም ። የዚህ ምሥጢሩ ዜማ ነው ። ዜማ ያድሳል ። የከበደንን ደመና ያነሣል ። ዜማ ደስታን ፣ የአእምሮ መፍታታትን ፣ ጣዕምን ፣ ተደማጭነትን ፣ ተወዳጅነትን ያጎናጽፋል ። በዜማ ውስጥ ብዙ መልእክቶች አሉ ። ዜማ ምስጋናንና ትምህርትን በጣዕም ለማስተላለፍ የሚረዳ ነው ። ዜማ የታላቅ ፍልስፍና መገለጫ ነው ። ዜማ በሰማይ የሚጠብቀን ድግስ ነው ። ቅዱስ ያሬድ የዜማው ባላባት እስከ ዛሬ ድረስ ተሰምተው የማይጠገቡ ዜማዎችን ለቤተ ክርስቲያን አበርክቷል ። በርግጥ መንፈሳውያን እንደ መሆናችን እግዚአብሔር እንደ ገለጠለት እናምናለን ፤ የስጦታውን ምንጭም አንስትም ። ቅዱስ ያሬድ እንዲህ ተቀብሮ መቅረቱ ኢትዮጵያዊ መሆኑ ነው ። የሌላው ዓለም ሀብት ቢሆን ኖሮ የየቀኑ ርእስ ይሆን ነበር ።

ዜማ የትልቅ ሥልጣኔ መገለጫ ነው ። ዜማን በኖታ ዓለም ከማቅረቡ በፊት ቅዱስ ያሬድ አዘጋጅቶታል ። ዜማ ቋንቋ ነው ። ስብሐተ እግዚአብሔር የሚደርስበት ሰረገላ ነው ። ዜማ ክንፍ ነው ፣ ወደ ሰማየ ሰማያት የምንወጣበት ነው ። ጸሎታችንን በዜማ ብናደርስ የምንጸልየውን እናስተውለዋለን ፣ እንባ በዓይናችን ይሞላል ፣ ልባችን በመለኮት ፍቅር መቅለጥ ይጀምራል ። ጮክ ብለን ማዜምና መዘመር በጣም ወሳኝ ነው ። በሳምንት አንድ ቀን እንኳ አፍ አውጥተን ብናዜም የከበደን ነገር ይቀለናል ። ዜማ የነፍስ ምግብ ፣ የጭንቀት ዱላ ነው ። ማንጎራጎር የሚወድዱ ሰዎች ደስተኞች ናቸው ። እያንጎራጎሩ ሲያለቅሱ ይታደሳሉ ። እንባ ወደ ውጭ ካልፈሰሰ ወደ ውስጥ ይፈሳል ። ያን ጊዜ ሰባራ ሰው ያደርገናል ። ዜማ ስብሐተ እግዚአብሔር የሚቀርብበት መሠዊያ ነው ። እግዚአብሔርን የሚማርከው ዜማው ሳይሆን የልባችን መቃጠል ነው ። ዜማ ግን ምድራዊነታችንን ሰማያዊ ያደርገዋል ።

የሚያዜሙ ሰዎች ብዙ ጊዜ እውቀት አይወድዱም ። በዚህ ምክንያት “ድምፅና ቁንጫ ባዶ ቤት ይወዳል” እየተባሉ ይተቻሉ ። የሚያዜም ሰው ግጥም ፣ ቅኔ ፣ የንግግር ችሎታን ማዳበር አለበት ። በርግጥ የሊቃውንቱን ቅኔ ለዓለም የሚያደርሱት ዜመኞች ናቸው ። የሚያዜሙም ከእውቀት መራቅ አይገባቸውም ። ዜማ ሙያ ሲሆን ለጥቂቶች ነው ። አምልኮ ሲሆን ግን ለሰው ልጆች ሁሉ ነው ። አእዋፋት በማለዳ ያዜማሉ ። ባናያቸውም እንወዳቸዋለን ፣ ዜማ እንደሚያነቃም እንረዳለን ። የሚያዜሙ ሰዎች በሰው ነፍስ ውስጥ አሉ ። ሰው ከውጫዊ አካሉ ይልቅ ነፍሱ ስፋት እንዳላት ዜማና ተጽእኖው ይገልጥልናል ። ዜማ የተለያየ መልእክት አለው ብለናል ። የማኅበረሰብ መግባቢያ ቋንቋ ነው ። ሰርግን ፣ ጦርነትን ፣ ደስታን ፣ ኀዘንን በዜማ እንወጣለን ። ሥርዓት ያላቸው ዜማዎች ፣ የማኅበረሰቡ ግኝት የሆኑ ግጥሞች ለሰርግ መዋል አለባቸው ። ዜማ የዝሙት ማስታወቂያ ሲሆንና እጅና እግርን ማወደሻ ሁኖ ሲቀር ይተቻል ። መንፈሳዊነት ማኅበረሰብን የሚደፈጥጥ አይደለም ። በሰርጌ ጌታ ይክበር የሚሉ አሉ ፣ ጥሩ ነው ። ጌታ ግን የሚከብረው በሁለት ሰዓት ፕሮግራም ብቻ ሳይሆን በኑሮ ውስጥ ነው ። ሚስትህን በአጋፔ ፍቅር ስትወዳት ፣ ባልሽን እንደ ራስ ስታከብሪው ያን ጊዜ እግዚአብሔር ይከብራል ።

በዜማ መለቀስ ፣ ኀዘን መተንፈስ አለበት ። ያልወጡ ኀዘኖች ብዙዎችን ለድባቴ እየዳረጉ ይገኛሉ ። አገራችን ታላላቅ ሰዎች የነበሩባትና ያሉባት አገር ናትና ደስታንም ኀዘንንም መግለጫ አበጅተዋል ። ደግሞም የባሕላችን ማሳያ ነውና ሊከበር ይገባዋል ። አለማልቀስ ዘመናዊነትም መንፈሳዊነትም አይደለም ። ሬሳ አስቀምጦ አላለቅስም ማለት ጉራ ሲሆን አብረው የሚያላቅሱ ሲሄዱ ውጋቱ ይጀምራቸዋል ። እንዴት ሰው ሞትን እያስተናገደ ለማልቀስ ይሳሳል ?

አገርን የሚያወድሱ ፣ ጀግንነትን የሚያነሣሡ ዜማዎች አንድን ትውልድ የአገር ዘብ አድርጎ የማቆም አቅም አላቸው ። እዚህ የምንጽፈውና የምናመልከው በዳር ድንበር የሚጠብቅ ወታደር ስላለ መሆኑን ማወቅና ክብር መስጠት ይገባናል ። ከዜማ ጋር የዜማ መሣሪያዎችን መለማመድ ግድ ይላል ። ቢያንስ አንድ የዜማ መሣሪያ ማወቅ ለቀጣዩ ዕድሜ ፣ ለእርጅና ብቸኝነት ወሳኝ ነው ። ዜማ ለማኞች እንኳ ጨካኙን የሚያራሩበት ነው ። የዜማ ዕቃ ይዘው የሚያዜሙም ከመንገዳችን ቆም ያደርጉናል ። ዘወትር ከጸሎታችን ጋር ድምፅ አውጥተን ብንዘምር ላሉብን ውጥረቶች ቅለት ይሰጠናል ። ነገር ግን አጠገባችን ያለውን ሰው እንዳንረብሽ ፣ ተወዳጁን አምላክ በእኛ ረባሽነት እንዳናስጠላው መጠንቀቅ ያስፈልጋል ። ዜማ የራሱ ሥርዓት አለውና ሊጠና ፣ ሊያድግና ሊበረታታ ይገባዋል ። ከሕይወት ሥነ ሥርዓት አንዱ ዜማ ማዜም ነው ። በቤተ ክርስቲያን የሊቃውንት የዜማ ዕቃ ጸናጽል ፣ መቋሚያና ከበሮ ነው ። የምእመናን የዜማ ዕቃ በገና ፣ መሰንቆ ፣ ክራር ፣ እንዚራ ተጠቃሽ ናቸው ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሰኔ 10 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም