መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት (35)

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት (35)

20. ያየኸውን ገመና አትናገር

“አዋላጅና አዋቂ ያየውን ሁሉ አይናገርም” ይባላል ። ሰውን ሰው ያሰኘው ገመና ያለው ፍጡር መሆኑ ነው ። በሙሉ ማንነቱ አውቆ የሚያፈቅረው እግዚአብሔር ብቻ ነው ። የሠሩትን የጭካኔ ተግባር የነገሩንን ፣ ያደረጉትን ኃጢአት ለእኛ ብቻ ያወሩትን ምናልባት ከዚያ ቀን ጀምሮ ጠልተናቸው ፣ ተጠራጥረናቸው ፣ እነርሱን ባየን ቍጥር ስህተታቸው እየታየን ይሆናል ። የሰዎችን ጉድለት ለማየት ሥልጠናና ሥልጣን ይፈልጋል ። በዚህ ምክንያት ካህን ተምሮ የሰውን ገመና ያያል ። የሥነ ልቡና አማካሪ ብዙ አጥንቶ የሰውን ውስጣዊ ትግል ከባለቤቱ አፍ ይሰማል ። ሐኪምም ተመራምሮ የሰውን ልብስ ገልጦ ያያል ። የሰዎችን ስህተት ከሌሎች ብንሰማ ካህን መሆን አንችልም ። ምክንያቱም ካህን ከራሱ ከባለቤቱ ሰምቶ መንገድ ያመለክታል ። የሥነ ልቡና አማካሪም ስለ እገሌ ከእገሊት ቢሰማ እውቀቱን መተርጎም አይችልም ። ሐኪምም መንገድ ላይ የተራቆተ ሰውን ቢያይ ሙያውን መጠቀም አይችልም ። ምሥጢር የባለቤቱ ሀብት ነው ። ያንን ምሥጢር በራሱ አንደበት ሲናገረው መፍትሔ ያገኛል ። ፖሊሶች ወንጀልንና ወንጀለኛን ያነፈንፋሉ ። ዓላማቸው ንጹሑንና አዳፋውን ለይቶ እርምጃ ለመውሰድ ነው ። ፖሊስ ምሽት ላይ ለአለቃው ዛሬ ሚስቱን ሲያስቀድም ያየሁት ባል ፣ ችግረኞችን ሲያጥብ ያየሁት ወጣት ብሎ ሪፖርት አያቀርብም ። ካህን ለምሕረት ፣ ሌላው ደግሞ ለፍርድ ይሰማል ።

አንድ ሰው ገመናውን ከነገረን ትልቅ ሹመት እየሰጠን ነው ። አንተ ካህኔ ፣ አማካሪዬ ፣ ሐኪሜ ነህ እያለን ነው ። እኛ ብንሆን ለዚያ ሰው ገመናችንን አንገልጥለትም ነበር ። ከምናከብረው በላይ ያ ሰው ያከብረናል ። ሰዎች ምሥጢራቸውን ከነገሩን በነገሩን ገመና ምክንያት አደጋ ቢደርስባቸው ልንደግፋቸው ይገባናል ። ቀድሞ መስማት ለመርዳት ባለ ዕዳ መሆን ነው ። በመከራ ቀን አጋዥ ለማግኘት ምሥጢርን ለሚገባው ሰው መንገር ይገባል ። አስቀድሞ በመስማቱ ከጀማው ጋር ሁኖ ይሰቀል አይለንም ። አይዞህ ብሎ ያበረታናል ። በዚህ ዘመን በሰው ገመና መነገድ የተለመደ ተግባር ሆኗል ። በዚህ የተካኑት ከዓለማውያን ይልቅ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተቀመጡት ጨካኞች ናቸው ። ወንጌል ገባኝ ባዮች የዚህ አበሳ ተሸካሚዎች ናቸው ። እርስ በርሳቸው በምሥጢር ያወሩትን አደባባይ ያወሩታል ። አንዱ አንዱን ያጋልጣል ። እንኳን ኢየሱስ የመከራቸው ጨዋ ያሳደጋቸው አይመስሉም ። በገመናቸው እስረኛ በማድረግ ብዙዎችን ለሞት ያበቁ ሰዎች አሁንም አሉ ። እንዲህ ስታደርግ ቀርጸንሃል እያሉ ያንን ሰው መጫኛ አህያ ፣ መጓጓዣ ፈረስ በማድረግ ይሰብሩታል ። ያም ሰው መሸከም ሲከብደው ራሱን ያጠፋል ። በጣም ሞኝ ነው ።

ብዙ ራሳቸውን የሚያጠፉ ሰዎች በገመናቸው እስረኛ የተደረጉ ሰዎች ናቸው ። በእውነት እንዲህ ያለውን ክፋት አንዳንድ ጊዜ ዓለማውያንም ላያደርጉት ይችላሉ ። አንድ አማኝ የወንድሙን ገመና በአደባባይ ካወጣ ክርስቶስ ኃጢአተኞችን ሊያድን መጣ የሚለውን ቃል በግልጥ ክዷል ። የሚያማክሩትን ሰው በመቅረፀ ድምፅ የሚቀርጹ ፣ ከዚያም የሚያስፈራሩ ወንጌላዊ ነን ባዮች እንዳሉ እናውቃለን ። አውቀንም ዝም ብለናል ። አንዳንድ ጉባዔዎች የገመናቸው እስረኞች የተሰባሰቡበት ነው ። እረኛ ነኝ ባዩ በምሕረት በትር ሳይሆን በገመናቸው አስሮ የራሱ አገልጋይ ያደርጋቸዋል ። በእውነት ከምንደኛ እረኛው በላይ በፍርሃት የተቀመጠው ሰው ያሳዝናል ። ራስን ነጻ ማውጣት ይገባል ። አልሠራኸው እንደሆነ ስምህ ቢጠፋ ክብርህ ነው ። በድለህ እንደሆነ ንስሐ የተዘጋጀው ላንተው ነው ። ራስህን በዚህች ጀምበር ነጻ አውጣ ። የአእምሮ የለሾች መጫወቻ ሆነህ አትኑር ። በባርነት ከመኖር በነጻነት መሞት ይሻላል ።

ፍርድ ቤት አካባቢ የማይጠፉ የሐሰት ምስክሮች አሉ ። እነዚህ ሰዎች “ክፈሉኝ ፣ አየሁ ሰማሁ ብዬ እመሰክርላችኋለሁ” የሚሉ ናቸው ። በኢትዮጵያ ባሕል የተጠሉ የሚባሉ የመጀመሪያዎቹ የሐሰት ምስክሮች ናቸው ። ቀጥሎ የሰውን ገመና የሚያወጡ ነውረኞች ናቸው ። ካህን ምሥጢር ካወጣ መቃብር አፍ አወጣ ይባላል ። አዋቂና ሥልጣን ያለው ያየውን ሁሉ አያወራም ። ለራሱም ክብር አይመጥነውም ። መቃብር የያዘውን ሬሳ ሲሸት ፣ ሲፈርስ ፣ ሲበሰብስ አንድም ቀን አውርቶ አያውቅም ። የእግዚአብሔር ልጆችም እንደ መቃብር አበሳን የሚሸፍኑ ናቸው ። ከመቃብር አንሰን የማውቀውን ሁሉ ማውራት አለብኝ ማለት ተገቢ አይደለም ። ይህ ዘመን ትዳር አደባባይ የወጣበት ነው ። የልጁን እናት ፣ የልጇን አባት ገመና በአደባባይ ያወራሉ ። ሲፋቀሩ ያልነገሩንን ሲጣሉ ለምንድነው የሚነግሩን ? ብለን መጠየቅ አለብን ። ለአቅራቢዎቹ ወሬው እንጀራቸው ነው ። እኛ ግን ለትዳር ክብር ስንል ገመና በአደባባይ መውጣት የለበትም ብለን ጆሮን መንሣት ያስፈልገናል ። ይህ ምሥጢር የሚነገርበት ቦታ አለ ። አንድ ማኅበረሰብ የመፍረስ አደጋ ውስጥ ነው የሚባለው የቤት ችግር እየገነፈለ አደባባዩን ሲበክል ነው ። የመንገድ የቆሻሻ መፍሰሻዎች ሲፈነዱ እንሳቀቃለን ። ከዚያ በላይ የሰው ምሥጢር ሲባክን መሳቀቅ አለብን ።

አንተ ግን ያየኸውንና የሰማኸውን ገመና አትግለጥ ። ያንተም ተሸፍኖልህ እንደምትኖር እወቅ ። ስለ ሰው ፣ ሰው ቢናገር ውሸት ነው ። ስለ ሰው እግዚአብሔር ቢናገር ተገቢ ነው ። ብዙ የሚያየውና የሚያውቀው እግዚአብሔር ዝም ብሎ ጥቂት የምታውቀውና ያየኸው አንተ ለፍላፊ አትሁን ። አምኖ የነገረህ ምሥጢር ምናልባት ሚስቱ ፣ ልጆቹም የማያውቁት ሊሆን ይችላል ። ይህን ያህል ክብር ተጥሎብህ ወርደህ እንዳትገኝ ተጠንቀቅ ። በሰማኸው ምሥጢር ያ ሰው ተፈርዶበት ወኅኒ ቢወርድ ተግተህ ጠይቀው ። ጓደኝነት ልኩ አንዱ የአንዱን ምሥጢር መጠበቁ ነው ። ከሁሉ በላይ የእግዚአብሔር ሰው ለሰማው ገመና ይጸልያል ። ምናልባት ማንም ያላየውን ያየኸው የጸሎት ርእስህ እንዲሆን ነው ። ያ ሰው ገመናውን ገልጦልህ አንተ ብታወጣው የሰውዬው በደል ባንተ ላይ ይቆጠርና ሰውዬው ነጻ ይወጣል ። ሆድ ብዙ ቆሻሻ ተሸክሟል ፣ እንኳን የሰውን ገመና ። በሆድ የሚይዙት በአፍ አይነገርም ። በምንም መንገድ ሁለት ሆናችሁ ያደረጋችሁት ለሦስተኛ ሰው አይወራም ። ብታወራ የሚሰማህ ሰው ይፈራሃል ፣ ይጠነቀቅሃል ። ነግ ለእኔ ነው ይልሃል ። ይልቁንም መንግሥታዊ ምሥጢርን ሰማህ ማለት ሰይፍ ባንገትህ አስረህ እንደ መዞር ነው ። ምሥጢሩን ከጠበቅኸው ይጠብቅሃል ፣ አሊያ ያጠፋሃል ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሰኔ 24 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም