መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት (36)

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት (36)

21. አመስግን – ውለታ አይለፍብህ

ይህች ዓለም ለብዙ ሰው ከባድ የትግል ሜዳ ብትሆንም ለአመስጋኞች ግን ቀላል ናት ። ስናመሰግን ችግሩን ሳይሆን እግዚአብሔርን እናያለን ። ስናመሰግን ያጣነውን ሳይሆን ያተረፍነውን እናስባለን ። ስናመሰግን የሄደውን ሳይሆን ያለውን እንመለከታለን ። ማመስገን ዓይንን ያበራል ። ማመስገን ሁሉንም ነገር በዜሮ ከማባዛት ያድናል ። ማመስገን ከተራራው ጀርባ ያለውን መስክ ፣ ከዋሻ መጨረሻ ያለውን ቀና ማለት ያስተውላል ። ማመስገን ነገር ሁሉ ለበጎ ነው ብሎ ከማሰብ የመነጨ ነው ። ማመስገን እኔ ለእኔ ከመረጥሁት እግዚአብሔር ለእኔ የመረጠው ይበልጣል ብሎ መቀበል ነው ። ማመስገን አለማጣት ፣ አለመታመም ፣ አለመጎዳት አይደለም ። ደግ ደጉን የመቁጠር የሕይወት ጥበብ ነው ። የሚያመሰግኑ ሰዎች ልባቸውና ፊታቸው ይበራል ። በዚህ ጊዜ ሰይጣን ፈተና ይቀይራል እንጂ በቅድሙ ወጥመድ ላይ አይዘገይም ። ሰዎች እኛን የሚፈልጉት ብሩህ ፊታችንን ፣ ቅን ልባችንን በማየት ካለባቸው ችግር ለማረፍ ነው ። ምሬተኛ ስንሆን ሰላማቸውን ላለማጣት ይሸሹናል ። አሊያም ተጠንቅቀው ይቀርቡናል ።

የምናማርረው ምናልባት ችግርን በችግር ለመፍታት ተነሥተን ስላልተሳካልን ሊሆን ይችላል ። የምናማርረው ከመንቀሳቀስ ተአምር በመጠበቅ ደክሞን ሊሆን ይችላል ። የምናማርረው ትልቅ የምንለውን ነገር ጠብቀን ለዛሬ በሚበቃን ትንሽ ነገር ስላልረካን ሊሆን ይችላል ። የምናማርረው ከሰው የመላእክትን ግብር ጠብቀን ሊሆን ይችላል ። ማመስገን ሁሉንም ነገር በልኩ የማየት ውጤት ነው ። የምንፈልገውን ብናገኝም ሞት አይቀርም ። ከሞት የሚያድነው ግን አሁንም በእጃችን ነው ። በሕይወት ውስጥ አለኝ ከማለት አለሁ ማለት ይበልጣል ። የሚጎድልበትም በሕይወት ያለ ነው ። የለኝም ያልነው በሕይወት ስላለን ነው ።

ከሁሉ አስቀድሞ እግዚአብሔርን ማመስገን አስፈላጊ ነው ። ተኝተን የምንነቃው ጠባቂ ወታደር ስላለ ሳይሆን እግዚአብሔር በመንበሩ ስላለ ነው ። ዛሬን ያየነው ወጥተን የገባነው ፣ ዘርተን ያጨድነው ፣ ወልደን የሳምነው በእግዚአብሔር ቸርነት ነው ። ካሉት የሞቱት ቆንጆዎችና ጠቢባን ይበዛሉ ። በዚህ ቀን እንኳ ብዙ ደጋግ ሰዎች ይሞታሉ ። ክፉዎች ለጉድ ይቀመጣሉ ። ሞት በመንፈሳዊ ቋንቋ ምሕረት ነው ። እስረኛ በምሕረት ሲለቀቅ ደስ እንደሚለው በሰማይም የተጠራች ነፍስ በነጻነትዋ ደስ ይላታል ። ግን እስር ቤት ሰብሮ የወጣ ቅጣቱ ከባድ ነው ። እንዲሁም ራሱን ያጠፋ በሰማይ ስደተኛ ነው ። የሕይወት ባለቤት እግዚአብሔር ነውና ። እግዚአብሔርን ማመስገን ተገቢ ነው ። የዛሬው ስኬትህ ትልቅ ሰው የሆንህና አምላክ አያስፈልግህም የሚል እሳቤ አምጥቶ ከሆነ በጣም ልትጠነቀቅ የሚገባው ሰዓት ነው ። ምክንያቱም ቀጥሎ የሚመጣው ብልሽት ልክ የለውም ። ሰው መታበይ ሲጀምር ውድቀቱ በቅርብ ርቀት ላይ ነው ። እግዚአብሔር ትዕቢትን ፈጥኖ ይቀጣል ። ናቡከደነጾር በተመካበት ቅጽበት እንደ እንስሳ ሆነ ። ሄሮድስ ድምፁ የአምላክ ነው ሲሉት ስለሞቀው ወዲያው ተቀስፎ ሞተ (ዳዳ. 4፡30 ፤ የሐዋ. 12፡23)።

ብዙ ሰዎችን እንታዘባለን ። የእግዚአብሔርን ደጅ በእንባ ያጣበቡትን ሰዎች እናስታውሳለን ። የያዙትን ነገር በትክክል መጨበጣቸውን ሳያረጋግጡ እግዚአብሔርን ትተዋል ። ከቤቱ ርቀዋል ፣ ጸሎት አቁመዋል ። ለምን ሲባሉ ደርዘን ምክንያት ይደረድራሉ ። በምናመሰግንበት ቀን ከሀዲ መሆን ከባድ ኃጢአት ነው ።

ማመስገን አለብን ። በልጅነታችን በጣም የሚወዱን ፣ ይከብደዋል እያሉ የእኛን ሸክም የሚሸከሙልንን ፣ ትምህርታችንን ለማገዝ የሚያስጠኑንን ፣ ከረሜላ እየገዙ የሚስሙንን ፣ እናታችን ገበያ ስትወጣ የሚጠብቁንን ፣ ያሳደጉንን ሞግዚቶች ፣ ስለ እኛ ከሰዎች ጋር የተጣሉንን ተቆርቋሪዎች ዛሬ ማመስገን አለብን ። አዎ እኛ አድገን ሠላሳ ዓመታችን ነው ። እነርሱ ሃምሳ ገብተዋል ። ደግሞም ወልደው ከብደዋል ። ረስተውናል ። እኛ ግን አስታውሰን ምስጋና ማቅረብ አለብን ። ዕድሜ የሚሰጠን የምስጋና ዕዳችንን እንድንከፍል ነው ። እነዚያ ስንራብ ያጎረሱንን ፣ ከቤት ወጥተን ስንከራተት ያስጠጉንን ላንቀየማቸው መውደድ አለብን ። በሰማይ ስንሄድ ከሚያስፈሩ ጥያቄዎች አንዱ በጎ የዋሉልንን አለማመስገን ነው ። እነዚህ ሰዎች ዕድሜ ተጭኖአቸው ፣ ሁሉም ነገር ከብዷቸው ሊሆን ይችላል ። ያኔ በልጅነታችን ለእኛና ለቤተሰባችን ያደረጉትን ስንነግራቸው ደስ ይላቸዋል ። ደግሞም መታሰቢያ ይሆን ዘንድ ስጦታችንን መስጠት አለብን ። ሁሉን ላፌ አይባልም ፣ የተሰጠን ልንሰጥም ነው ። እነዚህ ሰዎች የማይታወሱን ከሆነ አውሬ ነን ። እነዚህ ሰዎች የሚታወሱን ከሆነ አእምሮአችን ባለ ዕዳ ነው ። ከዕዳ ጋር መዋል ፣ ማደር ራስን በሰንሰለት አስሮ መግረፍ ነው ። ዛሬ ማታ ባለውለታዎቻችሁን አስታውሱ ። ያለፈውን ነገር አስታውሳችሁ ንገሩአቸው ። አመስግኑ ። አመስጋኞች ዕድሜአቸው ረጅም ነው

አንተ ግን ስሟ የእንጀራ እናት ቢባልም በጣም ትወድህ የነበረችውን አሳዳጊህን አስብ ። ዛሬ እናትህን በማግኘትህ እርስዋን አትርሳ ። ሲመሽ ምን ሆነህ ነው ያሉህን ፣ ለመሸጥ ካስቀመጡት ዳቦ እየሰጡ ያሳደጉህን እማማ እገሌን ፈልጋቸው ። ጀንበራቸው ልትጠልቅ እያዘቀዘቀች ነውና ቶሎ ብለህ ውለታህን መልስ ። እኒያ የሚወዱህ መምህር ፣ ከዚያ ሁሉ ተማሪ ላንተ ፍቅር ነበራቸው ። እርሳቸው ናቸው አስተማሪ ጥሩ ነው ብለህ እንድትደመድም የረዱህ ። ዓለምን በበጎ ያሳዩህን ፣ የፍቅር መምህሮችህን ፣. የጠዋት ወዳጆችህን ፣ ገና ነፍስህን ሳትረዳት ያፈቀሩህን ፣ ራስህን መውደድ ሳትጀምር አንተ የእኔ ነህ ያሉህን አመስግን ። ስለ አንድ አምላክ ብለህ ምክሬን ስማ ። ራስህን ከታላቅ ጸጸት ትፈታታለህ ። እኔ ቀኑን እየተሻማሁ ነው ። ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ቤተ ክርስቲያን የወሰዱኝን ፣ ስማር ደብተር የገዙልኝን እያሰስሁ ነው ። አንዳንዶቹ ሞተዋል ። ልጆቻቸው ምስጋናውንና ውለታውን ለመቀበል እየጠበቁኝ ነው ። ግድ የለም የእኔን ልምድ ተወዉ እባክህን አመስግን ። ሰው ሐውልት አይደለም ቆሞ አይጠብቅህም ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሰኔ 28 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም