መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት (39)

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት (39)

23. ከሰዎች ጋር ግንኙነትህን አሳምር

“ቢቻላችሁስ በእናንተ በኩል ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ።” ሮሜ. 12፡18 ። ሐዋርያው “ቢቻላችሁስ” አለ ። ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም መኖር ከባድ ነውና ። ቢቻለን ከሁሉም ነገድ ፣ ከሁሉም ሃይማኖት ጋር በሰላም መኖር ይገባናል ። ምድር የሁሉም እንጂ የአንድ ሃይማኖትና የአንድ ወገን አይደለችምና ። ለሁሉም እንደ ሥራው የሚፈርድ አምላክ አለና ሳንፈራረድ ከሁሉም ጋር በሰላም መኖር መታደል ነው ። በዚህ ምድር ላይ ልከኛ ነዋሪ የሚባለው ከሰዎች ጋር ያለውን ግንኙነት የሚያሳምር ነው ። ከሰዎች ጋር የዝምድና ፣ የሃይማኖት ፣ የጓደኝነት ፣ የሥራ ባልደረባነት ፣ የነጻነት ትግል ፣ የአገር ፍቅር ሊያገናኘን ይችላል ። መቼም ሃይማኖት ላለው ሰው ከዝምድና ሁሉ የሚበልጠው በክርስቶስ ያወቁት ወንድምና እኅት ነው ። ምድራዊ ዝምድና ሁሉ መቃብር ይገታዋል ። በክርስቶስ መዛመድ ግን ከሞትም ባሻገር የሚዘልቅ ነው ። በኖርኩበት ዘመን መንፈሳዊ ዝምድናን የሚያከብር ብዙ አላየሁም ። የሥጋ አባቱን ምሥጢር ደብቆ የሃይማኖት አባቱን እንከን በአደባባይ የሚያወራ ብዙ ነው ። የሥጋ ወንድሙ ቢበድለው ይቅር እያለ የሃይማኖት ወንድሙን ግን ጠልቶ የሚቀር አያሌ ነው ። የእግዚአብሔር ፈቃድ ሰው ከሰው ጋር እንዲኖር ነው ። ከሌላው ጋር ለማበር ሰው መሆን በቂ ነው ። በሽታው ሲመጣ ጥቁርና ነጩን በአንድነት ይፈጀዋል ። በአንድ ዓይነት በሽታ እየታመምን በአንድ ዓይነት ፍቅር መኖር አለመቻል ያሳዝናል ።

ከሰዎች ጋር ያለንን ግንኙነት ለማሳመር ከልብ ሰዎችን መውደድ ቀዳሚው ነው ። ልባዊ ፍቅር ባለበት የመለኮት መገኘት አለ ። በዚህ ዓለም ላይ ብዙ ዓይነት ፍቅሮች አሉ ። እግዚአብሔርን መነሻ ያደረገ የአጋፔ ፍቅር አለ ። ሥጋዊ ስሜትን መነሻ ያደረገ የወንድና የሴት ፍቅር አለ ። ይቅርታን ገንዘብ ያደረገ ጠላትን የምንወድበት ፍቅር አለ ። እኩያነትን ያገናዘበ የጓደኝነት ፍቅር አለ ። ሰዎችን ከልብ ስንወድድ ውስጣችን እውነተኛ እንደ ሆንን ይመሰክርልናል ። ሰዎች በዚህ ዘመን ሲወድዱን እንጠራጠራለን ፣ ሲጠሉን ግን ከልብ እናምናለን ። ፍቅርን መስጠት ብቻ ሳይሆን መቀበል አልቻልንም ። ደግነት እያጠራጠረን ፣ ለምን ቸር ሆኑ እያልን ነው ። መልሰን ደግ ሰው ጠፋ እያልን እናማርራለን ። ስለ ብርቅዬ እንስሳት መጥፋት የሚያለቅሰው ያጠፋቸው ያው የሰው ልጅ ነው ። የገፋነው ደግነት ዛሬ በስእለት የማይገኝ እየሆነ ነው ። ሰውዬው እኔን ከመውደዱ በፊት ቀድሜ መውደድ ታላቅነት ነው ። የእግዚአብሔር ፍቅር መፍሰሻ ይፈልጋል ፣ በእኛ ወደ ሌሎች ለመፍሰስ ይሽቀዳደማል ። ሰዎችን በሁለተኛ ደረጃ በግልጽነት መቅረብ ያስፈልጋል ። በዚህ ዓለም ላይ ተሸፍኖ የሚሰነብት እንጂ ተከድኖ የሚቀር ምንም ነገር የለም ። ግልጽነታችን ግን የእብደት ታናሽ ወንድም እንዳይሆን መጠንቀቅ አለብን ።

ለሰዎች መገኘት አለብን ። ይህ ሦስተኛው የግንኙነት መርህ ነው ። ሰዎች ለእኛ የሚያስፈልጉን ቀን እንዳለ ሁሉ እኛ በምናስፈልጋቸው ቀን ሳይጠሩን መገኘት አለብን ። እግዚአብሔር መከራችንን በተለያየ ቀን ያደረገው አጽናኝ እንዳይታጣ ብሎ ነው ። ሲታመሙ ፣ ሲታሰሩ ፣ እንግድነት ሲመጡ ፣ ኀዘን ላይ ሲቀመጡ አለሁ ማለት አለብን ። በዚህ ዓለም የቅርብ ዘመድ የሥጋው ሳይሆን የቅርብ ጎረቤት ነው ። ኑሮአችን ገለልተኛ መሆን የለበትም ። ማንም እንዳይደርስብኝ ብለን በር ዘግተን መኖር ሕይወትንም ሞትም የሚያበላሽ ነው ። የሰለጠነው ዓለም የፈጠረው የግለኝነት ኑሮ ሰውዬው ሞቶ እንኳ ሬሳው እንዲበላሽ ያደረገ ነው ። መሰልጠን የምንለው ገደብ ከሌለው ለዚህ የሚያደርስ ነው ።

ሁሉን ነገር ክፍት ማድረግ የለብንም ። ይህ ዓለም የልክ ዓለም ነውና ለወዳጆችም ልክ መስጠት አለብን ። ሁሉም ነገር የሚወራው ፣ ሁሉም ነገር ክፍት የሚደረገው ለእግዚአብሔርና ለእግዚአብሔር ሰው ብቻ ነው ። አንዳንድ ጊዜ የትዳር ጓድም የማያውቁትና የማይሸከሙት የሕይወት ምሥጢር ይኖረናል ። ሰዎች ሁሉንም ነገራችንን የማወቅ መብት የላቸውም ። ንስሐና ጸሎት የሰውን ምሥጢራዊ ሕይወት የሚያግዙ ናቸው ። ሄደው እንዲመለሱ መፍቀድ አለብን ። ሰዎች በጣም መልካም ስንሆንላቸው ከዚህ የተሻለ መልካም ሌላ ቦታ አለና ልሂድ ብለው ያስባሉ ። ሄደው እንዲመለሱ መፍቀድ አለብን ። አንዳንድ መልካሞች ግን ከሸኙ በኋላ በሩን ዳግም አይከፍቱምና መጠንቀቅና አክብሮ መያዝ ይገባል ። ሰዎች እንዲሄዱ ካልፈቀድንላቸው ብዙ ነገሮች ይከሰታሉ ። የመጀመሪያው በልቡ የሄደን ሰው በአካል መያዝ በድን ታቅፎ መኖር ነው ። ሁለተኛ እኛ በእግዚአብሔር ብቻ እንደምንኖር ሁሉም ማወቅ አለበት ። እየወደዱን እንጂ እያስፈራሩን መኖር የለባቸውም ። ይህ ልካቸውን አጥተው እንዲፋንኑና እንዲባልጉ ያደርጋል ።

ከሰዎች ጋር ባለን ግንኙነት በእውነት ሲመለሱ በይቅርታ መቀበል ነው ። አንዳንድ ይቅርታዎች በውስጣቸው ክፋት ሊኖራቸው ይችላልና ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል ። ያልጨረሱትን ክፋት ለመጨረስ በይቅርታ ስም የሚመጡ ፣ እኛን አባብተው ጥቅም ፍለጋ እንደ ድመት የሚመለሱ ይኖራሉ ። እውነተኛ ይቅርታዎችን መቀበል ተገቢ ነው ። እግዚአብሔር ከሰው ጋር የሚኖረው ሰውን ይቅር እያለው ነው ።

ግንኙነትን የሚጎዱ ነገሮች አሉ ። የጋራ ፍቅር አለመኖር የግንኙነት ጸር ነው ። በአንድ ሰው ፍቅር የሚቀጥል ወዳጅነት ፣ የሚቆም ቤት ፣ የሚሠራ ተግባር አይኖርም ። የእኔ ፍቅር ብቻውን በቂ ነው በማለት ወደ ትዳር መግባት ለመውጣት ነው ። ጠላትህን ውደድ በሚል ፍቅር ወደ ትዳር ቢገባ ጉዳቱ የከፋ ነው ። አለመከባበር የግንኙነት አፍራሽ ነው ። ሐሜት ግንኙነትን በብርቱ ይጎዳል ። ስለ ወዳጅህ መልካምነት በሌላ ቦታ ፣ ስለ ጉድለቱ ግን ለራሱ ተናገር ። ጥቅመኛነት ወዳጅህን ለጉዳይህ ብቻ መውደድ አንድ ቀን ለዘላለም እንድትለየው ያደርግሃል ። ሞኝም የሚነቃበት ቀን አለ ። ራስ ወዳድነት የግንኙነት ትልቅ ጸር ነው ። ራስን ብቻ ማዳመጥ ፣ የራስን ፍላጎት ብቻ መከተል ሌጣ ሰው ያደርጋል ። ጨካኝነት የግንኙነት ጎጂ ጠባይ ነው ። ወደቀ ብሎ ወዳጅን መርገጥ ፣ ተራቆተ ብሎ ለዓለም ማሳየት ይህ ከባድ ወንጀል ነው ። አላባብሶ ኑሮ የወዳጅነት ጸር ነው ። ተወው ተይው መባባል ግንኙነትን ይጎዳል ። በሁለት ዓይን መተያየት ፣ በሁለት ጆሮ መስማት የግንኙነት ጸር ነው ። አንዱ ዓይን ስህተትን ሲያይ አንዱ መጨፈን አለበት ። ሰዎች አንድ ጊዜ እንኳ እንዲሳሳቱ መፍቀድ አለብን ። የሃያ የሠላሳ ዘመን ጓደኝነትን በዛሬ ክስተት አፈር ማልበስ አንገት የለሽ መሆን ነው ።….

ይህን የግንኙነት አሳብ ብቀጥለው ደስ ባለኝ ነበር ፣ የአገሬ አንባቢ ስልቹ ነው ። የሚጠቅመውን ትቶ የማይጠቅመውን የሚያስስ ነው ።

 

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሐምሌ 12 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም