መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት (41)

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት (41)

25. አትጨቃጨቅ

ሳታቋርጡ አመስግኑ ፣ ሳታቋርጡ ጸልዩ ፣ ሁልጊዜ በጌታ ደስ ይበላችሁ የሚሉ የአዲስ ኪዳን መመሪያዎች ናቸው ። ሳያቋርጡ ፣ ሳይታክቱ ፣ ሁልጊዜ ሊደረጉ የሚገባቸው አምልኮተ እግዚአብሔር ያለባቸው ነገሮች ናቸው ። ቀኑን በሙሉ የሚዘንብ ዝናብ ሥራ አያሠራም ። ቀኑን ጨፍጋጋ ፣ ጎዳናውን ጠባብ ያደርገዋል ። ጭቅጭቅ የማይቆም ድምፅ ቢሆንም ትጋት አይደለም ። ጭቅጭቅ ቀንና ሌሊት ቢደረግም አለመታከት አይደለም ። ጭቅጭቅ ብዙ ዋጋ ቢያስከፍልም ታማኝ ሎሌ አያሰኝም ። ጭቅጭቅ ራስንና ሌሎችን ያለ ዕረፍት ማወክ ነው ። በደስታ ከእንቅልፉ የተነሣውን ሰው በጭቅጭቅ ቀኑን መቀማት ትልቅ ጠላትነት ነው ። ቤት አለኝ ብሎ ለዕረፍት እየገሰገሰ ያለውን ሰው በጭቅጭቅ መቀበል ኑሮውን መቀማት ነው ። በዓለም ላይ የገንዘብ ሌቦች እንዳሉ ሁሉ የሰላማችንም ሌቦች አሉ ። የገንዘብ ሌቦች ብዙ ጊዜ የማናውቃቸው ፣ የማያውቁን ናቸው ። የሰላማችን ሌቦች ግን የምናውቃቸው አጠገባችን ያሉት ሰዎች ናቸው ። በዕለት ጸሎታችን ልናሰማው ከሚገባው ልመና አንዱ “የሁከት ምክንያት ከመሆን አድነኝ” የሚል መሆን አለበት ።

ጭቅጭቅ ደጋግሞ አንድን ነገር መግለጥ ነው ። ልብስን ጨቅጭቀን ስናጥበው ልናነጻው እንችላለን ። ብዙ ጊዜ የሚታጠብ ልብስ ግን ማለቁ አይቀርም ። በመጨቃጨቅ ሰውን ልንለውጠው አንችልም ። ከስህተቱ በላይ የእኛን መጨቃጨቅ እየጠላው ይመጣል ። መጨቅጨቅ ምጣድ የጣዱ ሴቶች በቀዳዳው ንፋስ እንዳይገባ ፣ በር የሚዘጉ ሰዎች ብርድ እንዳይመጣ ትንሽ ሽንቁር እየፈለጉ የሚደፍኑት ነው ። መጨቃጨቅ ነፋስ አይግባብኝ የሚል የአትንኩኝ ባይነት ስሜት ፣ ከሰዎችም ፍጹምነትን የመፈለግ ስቃይ ነው ።

ጭቅጭቅ ያደረ ጠብ ውጤት ነው ። ጭቅጭቅ በንግግር ፣ በጠብ ፣ በበቀል ያለመርካት ውጤት ነው ። ጭቅጭቅ ትላንትን ዛሬ ላይ አምጥቶ መኖር ነው ። ጭቅጭቅ በራስ ስህተት ሳይሆን በሰዎች ስህተት ይቅርታ አልባ መሆን ነው ። ተጨቃጫቂነት ከልጅነት ጀምሮ ያልተገረዘ ጠባይ ነው ። በመጨቃጨቅ የምንፈልገውን የምናገኝ ሲመስለን ጭቅጭቅን እንደ ኃይል መጠቀም እንጀምራለን ። ወላጆችም ስላመኑበትና ስለሚያስፈልገን ሳይሆን ስለጭቅጭቃችን ሲሰጡን መጨቃጨቅን እንደ ሥልጣን እየቆጠርን እንመጣለን ። ጭቅጭቅ ከቅንዓት ውስጥ ይወጣል ። አትኩሮት መፈለግ የብዙ አቅመ ደካማ ሰዎች ጠባይ ነው ። የተረሳሁና ማንም የማያስበኝ ሰው ነኝ ብለው የሚያስቡ በሁሉም ነገር አትኩሮትን ይሻሉ ። አትኩሮትን ለማግኘት አንዱ ዘዴ ጨቅጫቃነት ነው ። መጨቃጨቅ ግን መጠላትንና መረሳትን ፣ እያሉ እንደሌሉ መቆጠርን ያመጣል ። ምናልባት ድንዙዝ ሰዎች አንድ ቃል ስለማያነቃቸው መጨቅጨቅን ሊወድዱት ይችላሉ ። የሚሠራውንና ለምን እንደሚኖር የሚያውቅ ሰው ግን ጭቅጭቅ ሰላሙን ይረብሽበታል ። አዎ ጭቅጭቅ ቤትን ያፈርሳል ። ጭቅጭቅ በፈጠራ ታሪኮች ፣ ቅንዓት በሚሰጠን ሥዕል ፣ በግምት ላይ ሊመሠረት ይችላል ። ብዙ ጉዳይ የሚያስጨንቀው ያ ሰው የእኛን ጭቅጭቅ መሸከም ሲያቅተው ሊለየን ይፈልጋል ። ጭቅጭቅን የፍቅር መግለጫ አድርገው የሚያስቡት ሰዎች ይኖራሉ ። የብዙ ሰዎች ችግር ፍቅራቸውን እንዴት እንደሚገልጡት አለማወቅ ነው ።

ጭቅጭቅ እኝኝ እንደሚል ዝናብ ነውና የመነሣት ፣ የመሥራት አቅምን ይበላል ። ከተጨቃጫቂ ሰው ጋር የሚኖር ሰው ቀኑንም ሌሊቱንም ይከስራል ። ተጨቃጫቂነት ጠባያችን ከሆነ መገንዘብ ያለብን ነገር አለ ። በዚህ ዓለም ላይ ብዙ መናገር እያስናቀ ጥቂት መናገር እያስከበረ ይመጣል ። የምንፈልገውን ማግኘት ያለብን እጅ ጠምዝዘን ፣ ወይም ያውላችሁ ተብለን ሳይሆን በክብር ፣ በደስታ ሊሆን ይገባዋል ። ሰውን አቅል ነሥተን የምንቀበለው ነገር ከቅሚያ የሚተናነስ አይደለም ። ተጨቃጫቂነት ለእኛ የሚያስደስተን ወይም የፍቅር መግለጫ መስሎ ከተሰማን ብዙ ሰዎችን ግን የሚያሳጣን ሊሆን ይችላል ። ተጨቃጫቂነትን ለማስወገድ የምንለምነው አምላክ ያለን ሰዎች መሆናችንን መቀበል አንዱ ነው ። ሰዎችን ብዙ የተለማመጥነውን ያህል እግዚአብሔርን ብንለምነው ለሰዎቹም እንተርፍ ነበር ። አንደበት መክፈቻ ብቻ ሳይሆን መዝጊያም የተበጀለት ዝም ማለት ስላለብንም ነው ። ሁልጊዜ በመናገር ብቻ አጠገባችን ያለውን ሰው ልንለውጠው አንችልም ። በማለፍና ዝም በማለትም ራሱን እንዲያይ እናደርገዋለን ። ሰው እኛ ስላየነው አይለወጥም ፣ ራሱን በትክክል ሲያይ ግን ለመለወጥ ይነሣሣል ። ጭቅጭቅ የተሰባበረ መስተዋት በመሆኑ መልክን አያሳይም ። ሰዎች በእኛ ጭቅጭቅ ውስጥ ሊደበቁ ይችላሉ ።

ጭቅጭቅ እያደገ ሲመጣ ከግለሰብ አልፎ ሕዝብን ወደ መጨቅጨቅ ሊያልፍ ይችላል ። ስብከታቸውን ጭቅጭቅ የሚያደርጉ ሰባኪዎችም የዚህ ያልታረመ ዕድገት ውጤት ናቸው ። አንድን ነገር መደጋገም ፣ በእኔ እውቀት ብቻ መቀበል አለባችሁ ፣ ለምን ? ብላችሁ አትጠይቁ የሚሉ ሰዎች ጭቅጭቅን እንደ መሣሪያ ይጠቀሙታል ። ሁሉም ነገር በፕሮግራም እንደሚደረግ የማይገነዘቡ መጨቃጨቅን ይወዳሉ ። ተጨቃጫቂዎች የጊዜ ሰሌዳን አይቀበሉም ። ራሳቸውን ብቻ ስለሚያዳምጡ እገሌ ሊቸግረው ይችላል ብለው አያምኑም ። እጅ በመጠምዘዝ ስለ መቀበላቸው እንጂ በዚያ ሰው ልብ ውስጥ ስለሚያጡት ክብር አያስቡም ። ጨቅጫቃ አለቆች ከማትረፍ ይከስራሉ ። ጨቅጫቃ አባወራዎች ልማዳቸው ነው እየተባሉ ይናቃሉ ። ጨቅጫቃ አፍቃሪዎች መንገድ ላይ ይከዳሉ ፣ ይቀራሉ ።

አንተ ግን ከጨቅጫቃነት ውጣ ። ሰላም ስትነሣ መጀመሪያ አንተ ሰላም አጥተሃል ። የምትከስረው ሰላምና ያጣኸው ነገር የሚመጣጠን አይደለም። ሰላም ከዋጋ በላይ ነው ። ሰላም ሳለ የሚናቅ ከሄደ በኋላ ግን በውድ ዋጋ የማይገኝ ነው ። አንድ ጊዜ ኮስተር ብለህ ተናገር ። ውሳኔ የሚባል ነገር አለና ወሳኝነትህን አሳይ እንጂ አትጨቃጨቅ ። መወያየት መልካም ነው ። አጉረምራሚነት የአውሬ ጠባይ ፣ ተጨቃጫቂነትም የከንቱ ሰው መገለጫ ነውና አርቀው ። ከእንቅልፍ ስትነቃ መጀመሪያ የምታገኘው ራስህን ነውና ከራስህ ውጭ አንተን የሚረዳህ እግዚአብሔር ብቻ ነው ። ስለዚህ በመጨቃጨቅ ሰዎችን ወተት አዝንቡልኝ አትበል ። ፍቅርህንም በተግባር ግለጠው እንጂ በጭቅጭቅ የሚገለጥ ፍቅር እንደሌለ አስተውል ። ከሁሉ በላይ ለማንም ሰላም ማጣት ምክንያት አትሁን ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሐምሌ 23 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም