መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት 9

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት 9

8- አለባበስህን ጠብቅ

ለልብሳቸው የሚጨነቁ ለልባቸው ግድ የሌላቸው ሰዎች እንዳሉ ሁሉ ፤ ለልባቸው የሚጨነቁ ለልብሳቸው ደግሞ ግዴለሽ የሆኑ ሰዎች አሉ ። ሕይወት ግን ሚዛናዊ ናት ። አስበን መልበስ መልካም ነው ፣ ተጨንቀን መልበስ ግን ራስን ማድከም ነው ። እግዚአብሔር አምላክ አስቀድሞ ለአዳምና ለሔዋን ልብሰ ብርሃን አልብሷቸው ነበር ። ይህ ልብሰ ብርሃን ጸጋ እግዚአብሔር ነበረ ። የዚህ ልብሰ ብርሃን ጠባዩ ልዩ ነው ፤ ብርሃን ሁሉ ዕራቁትን ያሳያል ፣ ይህ ልብሰ ብርሃን ግን ይሸፍናል ። ልብስ ሁሉ ይወይባል ፣ ይነትባል ፣ ያልቃል ። ይህ ልብሰ ብርሃን ግን እየታደሰ ይኖራል ። አዳምና ሔዋን በኃጢአት በወደቁ ጊዜ ይህን ልብሰ ብርሃን ተገፈፉ ። ስለዚህም ዕራቁታቸውን እንደሆኑ አወቁ ፣ ተፋፈሩ ። አዳም በሔዋን ላይ የነበረውን የጸጋ ያያል ፣ ሔዋንም በአዳም ላይ ያለው ጸጋ ታያለች ። የሚያዩት ጸጋን ብቻ ነውና አንዱ በአንዱ ፊት የከበረ ነበር ። ሲመሽ የዋለው ልብስ ይወልቃል ። ልብሰ ብርሃን ግን በምሽት የሚወልቅ አልነበረም ። ልብሰ ብርሃን በአቧራ ፣ በጭቃ የሚቆሽሽ ልብስ አልነበረም ። ንጹሕ ልብስ ነበርና ሌላውንም ንጹሕ አድርጎ ያሳያል ። ልብስ ሁሉ ቅያሪ አለው ፣ አዳምና ሔዋን ግን ይህን ልብስ ለዘመናት ለብሰውት ነበር ።

በኃጢአት በወደቁ ጊዜ እግዚአብሔር የቁርበት ልብስ አደረገላቸው (ዘፍ. 3 ፡ 21) ። ይህ የቁርበት ልብስ ገበሬው የሚለብሰው ሌጦ ፣ ዘመናዊው ሰው የሚለብሰው ሌዘር ልብስ ነው ። መጽሐፍም ስለ አለባበስ ሕግ አለው ። ይህ በብሉይም በሐዲስም የጸና ነው ። ሴቶች በወንድ ልብስ ማጌጥ ፣ ወንዶችም በሴት ልብስ ማጌጥ አይፈቀድላቸውም ። ሴቶች መሸፈን ፣ ወንዶች ራሳቸውን መግለጥ የተፈጥሮና የመንፈሳዊነት ሕግ ነው ። ሴቶች ፀጉራቸውን መቆረጥ ፣ ወንዶች ማሳደግ አልተፈቀደም (1ቆሮ. 11፡14-16)። ስለ አንድ ዕቃ አጠቃቀም የሠራው ፋብሪካ ቢናገር ይበልጥ እናምነዋለን ። ስለሚያምርብንን የፈጠረን እግዚአብሔር ሲናገር በደስታ ልንቀበል ይገባናል። የሚገርመው ወንዱ የሴት ልብስ ቢለብስ ብዙ ውግዘት ይነሣል ፣ ሴት የወንድን ልብስ ስትለብስ ዝም ይባላል ። እግዚአብሔር የመረጠልን ጾታ ክቡር ነው ። እያንዳንዱ ጾታም የራሱ አለባበስ አለው ። በዚህ ዓለም ላይ ሦስት ዓይነት ወገኖች የአለባበስ ሥርዓት አላቸው ። እነርሱም ወንዶች ፣ ሴቶችና የሃይማኖት መሪዎች ናቸው ።

መጽሐፍ እንዲህ ይላል፡- “ሴት የወንድ ልብስ አትልበስ፥ ወንድም የሴት ልብስ አይልበስ ይህን የሚያደርግ በአምላክህ በእግዚአብሔር ዘንድ የተጠላ ነውና።” ይላል (ዘዳ. 22፡4) ። ዳግመኛም፡- “በእግዚአብሔርም መሥዋዕት ቀን አለቆችንና የንጉሥን ልጆች እንግዳ ልብስ የሚለብሱትንም ሁሉ እቀጣለሁ።” (ሶፎ. 1 ፡ 8) ።

ልብስ የባሕል መግለጫ ነው ። በዚህ አንጻር የምንለብሰው ልብስ የምዕራባውያንን ባሕል የሚገልጥ ነው ። ልብስ የሃይማኖት መግለጫም ነው ። በልብሱ አገሩን ፣ ባሕሉን ፣ ሃይማኖቱን እናውቃለን ። ልብስ የጾታ መግለጫ ነው ። የሴት ልብስ ለብሰው አደጋ ያደረሱ ወንዶችን እንሰማለን ። የወንድ ልብስ ለብሰውም አደጋ ያደረሱ ሴቶችን በቅርበት እየሰማሁ ነው ።

በማኅበረሰብ ዘንድ ጤናማ መተማመን እንዲኖር ልብስ ትልቅ አስተዋጽኦ ያደርጋል ። አንድ ሰው አእምሮውን ስቷል ለማለት አንዱ ማስረጃችን ልብሱን ጥሎ መሄዱ ነው ። የሰው ልጅ የግል የሆነ የአካል ክፍል አለው ። እግዚአብሔር ሲፈጥረው ማኅበራዊ ብቻ ሳይሆን ግላዊም አድርጎ ነው ። ይህ ሕግ ሲጣስ ብዙ ጥፋት ይከተላል ። ልብስ የአንድን ሰው ሥነ ልቡናዊ ማንነት ይገልጻል ። በልብሳችን ላይ ልባችን ይታያል ። ልብስ ከሰው ልጅ መሠረታዊ ፍላጎት አንዱ ነው ። አንድ ሰው ባለመልበስ ብቻ ለሞት ሊዳረግ ይችላል ። ብርዳማ በሆኑ አካባቢዎች ልብስ ከሕይወት ጋር የተያያዘ ነው ። የታመሙ ወገኖች በብርድ ምክንያት የበለጠ ኃይል እንዳያባክኑ ሙቀታቸውን በልብስ መጠበቅ አለባቸው ። እግዚአብሔር አምላክ ለልብስ የሚሆኑ ነገሮችን እንደ ጥጥ ያሉትን በመፍጠሩ ልናመሰግነው ይገባናል ። ልብስ የፋብሪካ ውጤት ይመስለናል ። ጥሬ ዕቃው ግን የእግዚአብሔር ነው ፣ የተሠራበት አእምሮም የእርሱ ገንዘብ ነው ። ታዲያ አለባበሳችን ምን መምሰል አለበት ። ይህ ከሕይወት ሥነ ሥርዓት አንዱ ነውና ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 28 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም