መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የመጣል ስሜት » የመጣል ስሜት -2

የትምህርቱ ርዕስ | የመጣል ስሜት -2

የመጣል ስሜት ሕፃን ፣ አዋቂ ፤ ምሁር ያልተማረ ፤ ሀብታም ድሀ ፤ ዝነኛ የተረሳን ብንሆን ሊገጥመን ይችላል ። ይህ ስሜት ሲሰማን ቀድሞ የሚያስደስተን ነገር አሁን የማያስደስተን ይሆናል ። ቤታችንን እንደ መቃብር ፉካ ፣ ንብረታችንን እንደ ወዳደቀና የዛገ ብረት ፣ ዝናችንን ራሳችንን እንዳታለልንበት አረቄ ፣ መወደዳችንን እንደ ተሳሳትንበት መንገድ አድርገን መመልከት እንጀምራለን ። የመጣል ስሜት ማሩን ማምረር ፣ ወተቱን ማጥቆር ይጀምራል ። በጊዜ ካልተገታ ዳርቻውን እያሰፋ ፣ ያለንን ነገር እንዳናይ ጥቁር መጋረጃ ማልበስ ይጀምራል ። ለነገሮች ትርጉም ማጣት ፣ ሁሉንም ነገር ምን ዋጋ አለው ? በሚል በዜሮ ድምር ውስጥ መክተት እንጀምራለን ። ተሻገርሁ ስንል መልሶ ይህ ስሜት ይይዘናል ። አንድ ሰዓት ስድሳ ሰከንዶች ሳይሆን ስድሳ ዓመቶች ያሉት ሁኖ ይረዝምብናል ። እጅግ ቆየሁ ብለን ሰዓታችንን ስናየው የተገፋው ገና አምስት ደቂቃ ብቻ ነው ። ሌሊቱን መፍራት ፣ ቀኑ እንዴት ይጋመሳል ? ብሎ መጨነቅ እንጀምራለን ። የሚፈልጉንን ሰዎች መሸሽ ፣ የማይፈልጉንን ማሳደድ የመጣል ስሜት የሚፈጥርብን አዙሪት ነው ።

የመተው ስሜት በውስጣችን እያደገ ሲመጣ ትላንት የምናልፋቸውን ነገሮች ዛሬ ማለፍ ያስቸግረናል ። ደስታችንም ሩቅ አገር ይቀመጣል ። ማልቀስም መሳቅም ፣ መውደድም መጥላትም እያስፈራን ይመጣል ። የማናውቀው የፍርሃት ስሜት ይከበናል ። የብቸኝነት ብርድ ያንጠረጥረናል ። ምዕራብና ምሥራቅ ተቀራርበው ቢያቅፉን እንመኛለን ። አዎ የመጣል ስሜት ሲቆጣጠረን ልባችን የከዳን ፣ የሕይወት ፍሬን የላላ ይመስለናል ። ድንገት ከፊት ለፊታችን ከሚገጥመን ጋር እንጋጫለን ። ሰዎች ብቻ ሳይሆን ግዑዛን ነገሮችም እያናደዱን ይመጣሉ ። ደስ የማይል ፣ ልብ ላይ የሚንቀዋለል ፣ የሕይወት ማጥወልወል ይገጥመናል ። ፈልገን ማጣታችን ፣ ያዝኩት ስንል ከእጃችን የሚያመልጠን ነገር ይህን ስሜት ይፈጥርብናል ። ስሜት ዕለታዊ ሲሆን ምንም አይደለም ። ኑሮ ሲሆን ግን እንደገና መታየት አለበት ።

የመጣል ስሜት በታላቅ ተቃውሞ ውስጥ በማለፍ የሚፈጥርብን መደፍረስ ነው ። ሕይወታችንን የሰጠናቸው ሕይወታችንን ሲጋፉ ፣ የኖርንላቸው ከማመስገን ወቀሳ ሲያበዙብን ፣ ልጆቻችን እንከናችንን ሲፈልጉ የመጣል ስሜት ይገጥመናል ። በምንሸለምበት ነገር ልብሳችን ሲገፈፍ ፣ በምንኖርበት ዕድሜ ሞት ሲታወጅብን የመጣል ስሜት ይጫጫነናል ። ያሳደግነው ሲነክሰን ፣ የተንከባከብነው እሾህ ሁኖ ካባችንን ሲይዝብን የመጣል ስሜት ውስጥ እንገባለን ። ለአንድ ነገር ሁለት ዋጋ አይከፈልም ። ምድር ከሸለመን ሰማይ በባዶ ይሸኘናል ። ሲያሳድዱአችሁ ደስ ይበላችሁ ያለው ክርስቶስ ፣ ሲያሞግሱአችሁ ወዮላችሁ ብሎናል ። ክርስቶስን የምንመስለው በመገፋት እንጂ በመሸለም አይደለም ።

የመጣል ስሜት ከማይለምዱ ሰዎች ጋር በመኖር የሚከሰት ነው ። ገቡ ሲባሉ ከሚወጡ ፣ ተገኙ ሲባሉ ከሚጠፉ ፣ ቀረቡ ሲባሉ ከሚርቁ ሰዎች ጋር መኖር የሕይወት ዝለት ያመጣል ። አቋም የሌለውን ሰው ተሸክሞ መኖር አቋምም መቆሚያም ያሳጣል ። በውድ የገዛናቸው ፣ በርካሽ የሚሸጡን ጊዜ ጥቂት አይደለም ። ያ የመጣል ስሜት ያመጣል ። ክዳት ለእውነተኛ አፍቃሪ የማይለመድ የሕይወት ቅንቅን ነው ። ዛሬ ነገሥታት ከሚገዙት ሕዝብ ወረት የሚገዛው ይበዛል ። ዘመናዊነት ወረት ነው ። ሰው ማለዋወጥ ሥልጣኔ ተደርጎ የሚታይ ነው ። በቃል ኪዳን አለመጽናት ፣ እንዴት እንኑር ሳይሆን እንዴት እንለያይ ብሎ የመውጫውን በር ሲቆፍሩ ማደር ፣ ሰውን ተጠቅሞ መጣል የጊዜአችን በሽታ ሆኗል ። ስለከዱን ሰዎች ሳይሆን ከእኛ ጋር ስላለው እግዚአብሔር ማሰብ ይገባናል ። ከአባት ከእናታችን በፊት የሚያውቀን ጌታ ዛሬም አለ ። ለቅጽበት ዓይኑን ከእኛ ላይ አንሥቶ የማያውቀው ጌታ ደስታችን ነው ። ሁሉ የራሱን ሥዕል ይሰጠናል ። በጥሩ ዓይኖቹ የሚያየን ክርስቶስ ግን አሟልቶ ያነበናል ። የዓለም አስቀያሚ ብንሆን እንኳ የክርስቶስ ውቦች ነን ። ውብ ልቦች ሁሉን ውብ አድርገው ይመለከታሉ ። በተቀደሰው በኢየሱስ ልብ መኖሪያ አግኝተናል ።

“ሰይጣን ተስፋ የለውም ፣ ግን ተስፋ አይቆርጥም ፤ ሰው ተስፋ አለው ፣ ነገር ግን ተስፋ ይቆርጣል ።” እግዚአብሔርን በሰው ሚዛን ይለካዋል ። ሰዎች አጠገባችን የሉም ማለት እግዚአብሔር ከሰው ጋር አደመ ማለት አይደለም ። እርሱ የራሱ ሚዛን አለው ። በእኛ ላይ ያለውን የራሱን ዓላማ ያያል ። እርሱ አይተወንም ። ሰዎችን ስንለካ ፣ ስንመዝን ፣ ስንመትር መኖር ዋጋ የለውም ። የማይታበል ፍቅር ከእኛ ጋር ነው ። ሊወድቅ ያለውን የሕይወት ምሰሶ እንደገና እናጽናው ። መተው የማያውቀው አምላክ ከእኛ ጋር ነው ። ታሪክ እገሌን ጣለ ብሎ አልጻፈለትም ፣ ክርስቶስ ሰውን መጣል በእኛ አይጀምርም ።

ምስጋና ለማይተው ፍቅርህ ! አሜን !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 23 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም