መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » የሚወዱህ አሜን ይላሉ

የትምህርቱ ርዕስ | የሚወዱህ አሜን ይላሉ

ከሚያሳቅቀው ጨለማ ወደሚያስደንቀው ብርሃን ፣ ከጨካኝ ገዥ ወደ በጎነትህ ግብር ፣ አዳም ገብሩ ለዲያብሎስ ከተባለበት ባርነት የንጉሥ ካህናት ወደ መሆን ጌትነት የመለስከን ፣ ባሕረ ሞትን አሻግረህ መዝገብ ሕይወትን ያወረስከን የጸጋ ሁሉ አምላክ በዚህ ቀን ምስጋና እናቀርብልሃለን ። ከቆረጡ ጋር ቆርጠህ ፣ ከጨከኑ ጋር ለማዳን የጨከንህ ፣ የማንኖርበትን ቤት ስንሠራ ፣ ወደማንኖርበት ከተማ ስንገሰግስ ሀገረ ሕይወትን ፣ የጽዮን ተራራን ያሳየኸን ፣ ብቅ ጥልቅ ብንልም ዛሬም የምታበረታን አንተ ነህ ። ከቻሉት ጋር ኅብረት ፣ ካልቻሉት ጋር ርቀት የሌለብህ ፣ ሁሉን በፍቅር ዓይንህ የምታይ ፣ በውብ ዓይኖችህ ውብ አድርገህ የምታየን አንተ ነህ ።

በችሎታው የሚረዳህ ፣ ባለው ነገር የሚደግፍህ ማንም የለም ። የሰማዩ ሰማይ ፣ የጠባቂዎች ጠባቂ ፣ የዳኞች ዳኛ ፣ የባለ መብቶች ባለ መብት ፣ ሁሉ ያንተ ሳለ የእኔ እያለ የሚጣላውን ወገን የምታይ ፣ የጀመርከው የሚፈጸምልህ ፣ የፈጸምከው የሚዋብልህ ፣ ያስዋብከው የሚኖርልህ ፣ በበሩ ለገቡ ሰፊ መስክ ፣ ቃልህን ለሚጠብቁ ጽኑ እረኛ ፣ ፍርድህን ፍቅርህ የማይሽረው ፣ ፍቅርህን ፍርድህ የማያስቀረው ፣ የሕዝብ ሁሉ አባት ፣ የዚህ ሁሉ ወፈ ሰማይ መጋቢ ፣ እኛ ስንቆጥረው የበዛብንን የሰው ዘር አንተ እንደ አንድ ልጅ የምታይ ፣ መልቀም ለሚወዱ ጎተራ በረከት የምትሰጥ ፣ ቃርሚያ ለወጡ እርሻውን ባለ ርስት አድርገህ የምትሰጥ ፣ ረጅሙን ጉዞ በአንድ እርምጃ የምታስጀምር ፣ ለይቶ የወደደህን በቃል ኪዳን የምታከብር ፣ ራሱን ለሰጠህ ዘሩን የምትባርክ ፣ ጎረቤት ለሌለው ጎረቤቱ ፣ ከተማው ላደመበት ወገኑ ፣ ወልዶ መሐን ለሆነው እውነተኛ ልጁ ፣ ትዳር ለሌለው የቤቱ ራስ ፣ አቅም ሲደክም ምርኩዝ ፣ ሲመሽ መብራት ፣ ዓይን ሲከዳ መሪ አንተ ነህና የቀኑን ምስጋና ፣ የሰንበትን ዘለላ ላንተ እናቀርባለን ። የሚወዱህ ሁሉ አሜን ይላሉ ። አሜን ያለህም በአማን በረከት ይባረካል ። አሜን ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 24 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም